1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቃለመጠይቅ።ድርድሩ ተሰረዘ፤ ጦርነቱ ቀጠለ።ከዚያስ?

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 1 2015

የድርድሩ መሰረዝ አነጋግሮ ሳያበቃ የኢትዮጵያ መንግስት፣የኤርትራና የሕወሓት ኃይሎች ኢትዮጵያና ኤርትራን በሚያዋስነዉ ድንበር የገጠሙት ጦርነት መፋፋሙ ተዘግቧል።ሕወሓት የትግራይ ሕዝብ ለጦርነቱ እንዲከት ባለፈዉ ዕሁድ ጠይቋል።ድርድር ሲጠበቅ የዉጊያ ዜና መሰማቱ ተፋላሚ ኃይላት ጠባቸዉን በድርድር ለመፍታት «አይፈልጉም» የሚል ሥጋትና ጥርጣሬ አጭሯል

https://p.dw.com/p/4I2hu
Kombobild | Uhuru Kenyatta, Olusegun Obasanjo, Phumzile Mlambo-Ngcuka


የኢትዮጵያ መንግስትና ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ባለፈዉ ሳምንት ማብቂያ ያደርጉታል ተብሎ የነበረዉ ድርድር ላልተወሰነ ጊዜ ተላልፏል።ሁለት ዓመት ሊደፍን ሳምንታት የቀሩትን ጦርነት ለማስቆም ይረዳል የሚል ተስፋ የተጣለበት ድርድር ለመሰረዙ ሁለቱ ተፋላሚ ኃይላት በግልፅ ያሳወቁት ነገር የለም።ይሁንና የሕወሓቱ ቃል አቀባይ ጌታቸዉ ረዳ ቀጠሮዉ ፓርቲ (ዳንኪራ) አይደለም በማለት ማሽሟጠጣቸዉ ተጠቅሷል።ስለጉዳዩ በቅርብ እናዉቃለን የሚሉ ዲፕሎማቶች እንደሚሉት ግን ድርድሩ የተሰረዘዉ «በሎጂስትክስ ችግር» ምክንያት ነዉ።

በአደራዳሪነት ከተመረጡት ሶስት የቀድሞ ፖለቲከኞች በቅርቡ ከስልጣን በጡረታ የተገለሉት የቀድሞዉ የኬንያ ፕሬዝደንት ኡሁሩ ኬንያታ፣ የድርድሩ መሰረዝ ከመሰማቱ በፊት «በቀጠሮ መደራረብ ምክንያት» ቢያንስ በመጀመሪያዉ ዙር ድርድር ላይ መገኘት እንደማይችሉ አስታዉቀዉ ነበር።ኬንያታ ወደፊት የሚደረገዉን ድርድር ለመሸምገልም የድርድሩ መነሻና መድረሻ፣የሥርዓቱና የሒደቱ እንዴትነት እንዲብራራላቸዉ የአፍሪቃ ሕብረትን  ጠይቀዋል።   

አቶ አዳርጋቸዉ ፅጌ፣ ፖለቲከኛና የፖለቲካ ተንታኝ
አቶ አዳርጋቸዉ ፅጌ፣ ፖለቲከኛና የፖለቲካ ተንታኝምስል Andargachew Tsige

የአፍሪቃ ሕብረት፣ ሌሎቹ አደራዳሪዎችና ተደራዳሪዎች ራሳቸዉ ስለ ድርድሩ መሰረዝ፣ ስለሚቀጥልበት ጊዜና ሁኔታ በግልፅ የተናገሩት አለመኖሩ መገናኛ ዘዴዎችን፣ ታዛቢና የፖለቲካ ተንታኞችን ግራ አጋብቷል።

የድርድሩ መሰረዝ አነጋግሮ ሳያበቃ የኢትዮጵያ መንግስት፣ የኤርትራና የሕወሓት ኃይሎች ኢትዮጵያና ኤርትራን በሚያዋስነዉ ድንበር የገጠሙት ጦርነት መፋፋሙ ተዘግቧል።ሕወሓት መላዉ የትግራይ ሕዝብ ለጦርነቱ እንዲከት ባለፈዉ ዕሁድ ጠይቋልም።ድርድር ሲጠበቅ የዉጊያ ዜና መሰማቱ ተፋላሚ ኃይላት ጠባቸዉን በድርድር ለመፍታት «አይፈልጉም» የሚል ሥጋትና ጥርጣሬ አጭሯል።ባለፉት ሐምሳ ዓመታት ግድም የነበሩና ያሉ የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ልዩነታቸዉን በድርድር የፈቱበት ፖለቲካዊ ዳራ መኖር አለመኖሩም እያጠያየቀ ነዉ።

Äthiopien Yared Tibebu
አቶ ያሬድ ጥበቡ፣ የቀድሞ ፖለቲከኛና የፖለቲካ ተንታኝምስል Government Communication Affairs Office/Kewot Woreda

የተሰረዘዉን ድርድር፣ የተፋላሚዎችን ዓላማና የድርድርን ባሕል አንስተን ከሁለት የቀድሞ ፖለቲከኞች፣ ታጋዮችና የፖለቲካ ተንታኞች ከአቶ አንዳርጋቸዉ ፅጌና ከአቶ ያሬድ ጥበቡ ጋር አጫጭር ቃለ መጠይቅ አድርገናል።በቅደም ተከተል የተያያዙትን ማገናኛዎች (ሊንኮችን) በመጫን ሙሉ ቃለ መጠይቁን አድምጡ።

ነጋሽ መሐመድ

 

 

 

 

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ