1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

መድኃኒቱን በጥንቃቄ መከታተል የሚያሻው የTB ህክምና

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 19 2013

TB በየዓመቱ በመላው ዓለም ወደ ሰባት ሚሊየን ገደማ ሕዝብ የሚፈጅ በሽታ መሆኑን የዓለም የጤና ድርጅት በቅርቡ ይፋ ያደረገው መረጃ ያሳያል። ኢትዮጵያ ውስጥ በአሁኑ ወቅት ከመቶ ሺህ ሰዎች መካከል 19ኙ በTB ሕይወታቸውን እንደሚያልፍ ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ የህክምና ባለሙያዎች ይናገራሉ።

https://p.dw.com/p/3sbLs
Tuberkulose in Indien Krankenhaus in Howrah Medikamente Tabletten Medizin
ምስል picture-alliance

የTB ምልክቶችና ህክምናው

Tuberkulose in Indien Krankenhaus in Howrah Medikamente Tabletten Medizin
ምስል picture-alliance

TB ሳንባን ብቻ የሚጎዳ የሚመስላቸው፤ አጠራሩም የሳንባ ነቀርሳ ነው፤ የሚሉ ጥቂት አይደሉም። በፌስቡክ ገጻችን ላይም ይኽንኑ አስተያየት የጻፉ መኖራቸንም አስተውለናል። ባለፈው ሳምንት በፌደራል ጤና ሚኒስቴር መድኃኒት የተላመደ TB ከፍተኛ አማካሪ የሆኑት ዶክተር አንዳርጋቸው ኩምሳ፤ TB ሳንባን ብቻ የሚያጠቃ ሳይሆን በርካታ የሰውነት ክፍሎችን የሚጎዳ የጤና ችግር መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።

በአሁኑ ጊዜ ከሦስት ሺህ በላይ የሚሆኑ ሀኪም ቤቶችና የጤና ተቋማት የግሎችን ጨምሮ በቂ ስልጠና በወሰዱ ባለሙያዎች አማካኝነት ለመደበኛው የTB በሽታ ህክምና እየሰጡ መሆናቸውንም አመልክተዋል። መድኃኒት የተላመደውን TB የሚያክሙ ወደ 67 የሚሆኑ የህክምና ተቋማት መኖራቸውንም ገልጸዋል። የTB መድኃኒቶች የጎንዮሽ ጉዳት እንዳላቸው ያመለከቱት ዶክተር አንዳርጋቸው ታማሚዎች ተገቢውን የሀኪም ክትትል ሊያደርጉ እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። መድኃኒት በመውሰዱ ሂደት በሚያጋጥሙ የተለያዩ የጤና ቀውሶች ምክንያትም የTB መድኃኒት ሊቋረጥ እንደማይገባ፤ ይልቁንም ወደ ሀኪም በመሄድ ተገቢውን ምክርና ርዳታ ማግኘት እንደሚቻልም አስገንዝበዋል።

በአሁኑ ወቅት የሁሉም ሰው በሚባል ደረጃ ትኩረት ዓለምን ያስጨነቀው የኮሮና ተሐዋሲ ላይ ነው ማለት ይቻላል። ኮቪድ 19 ኢትዮጵያም ውስጥ የታማሚዎች እና በዚህ መዘዝም ሕይወታቸው የሚያልፈው ቁጥር እየተበራከቱ መሄዱ ይነገራል። TBም ሆነ ኮቪድ 19 ሳንባን የሚያጠቁ በሽታዎች መሆናቸውን ያመለከቱት ዶክተር አንዳርጋቸው የሚኖረው ሳል እና ይዞታው እንደሚለያይ፤ ሆኖም በምርመራ መጣራት እንዳለበትም አሳስበዋል። በፌደራል ጤና ሚኒስቴር መድኃኒት የተላመደ TB ከፍተኛ አማካሪ የሆኑት ዶክተር አንዳርጋቸው ኩምሳ ህክምናውን የጀመሩ ታማሚዎች ያለመታከት ለ ስድስት ወራት የሚሰጣቸውን መድኃኒት ተከታትለው በመውሰድ በሽታውን ለማጥፋት የሚደረገውን ጥረት እንዲያግዙም ምክራቸውን ለግሰዋል።

ሸዋዬ ለገሠ

ነጋሽ መሐመድ