1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሐረር ለጎዳና ተዳዳሪዎች ሥልጠና

ዓርብ፣ የካቲት 13 2012

የሀረሪ ክልላዊ መስተዳድር ለረጅም ዓመታት በሐረር ጎዳናዎች መሪር ሕይወታቸውን ሲገፉ የነበሩ ከ300 በላይ ታዳጊ ህፃናት እና አዋቃዊዎችን በመሰብሰብ ወደ ሀረር ፖሊስ ማሰልጠኛ ተቋም አስገብቷል። እነዚህ ዜጎች ከተለያዩ ሱሶች ከማገገም ባለፈ በቀጣይ ሕይወታቸውን በተለያዩ የሥራ መስኮች ላይ ተሰማርተው እንዲመሩ ኹኔታዎች ይመቻችላቸዋል ተብሏል።

https://p.dw.com/p/3Y86l
Äthiopien Nasir Yuyyaa Hassan
ምስል DW/M. Teklu

በአንድ ወር ቆይታ ከሱስ ማላቀቅ እና በሞያ ስራ ላይ ማደራጀት ስራ ይሰራል

የሀረሪ ክልላዊ መስተዳድር ለረጅም ዓመታት በሐረር ጎዳናዎች መሪር ሕይወታቸውን ሲገፉ የነበሩ ከ300 በላይ ታዳጊ ህፃናት እና አዋቃዊዎችን ከጎዳና በመሰብሰብ ወደ ሀረር ፖሊስ ማሰልጠኛ ተቋም አስገብቷል። እነዚህ ዜጎች በማሰልጠኛው ይኖራቸዋል በተባለው የአንድ ወር ቆይታ በጎዳና ሳሉ ከገቡባቸው የተለያዩ ሱሶች ከማገገም ባለፈ በቀጣይ ሕይወታቸውን በተለያዩ የሥራ መስኮች ላይ ተሰማርተው እንዲመሩ ኹኔታዎች ይመቻችላቸዋል ሲል የክልሉ ሰላም እና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ዐስታውቋል። እነኝሁ በማሰልጠኛ የሚገኙ ዜጎችም በማሰልጠኛው ስለሚከታተሉት ስልጠና አስተያየት ሰተዋል። የድሬዳዋው ወኪላችን መሳይ ተክሉ አነጋግሯቸዋል። 

የሀረሪ  ክልላዊ መስተዳድር በከተማዋ በጎዳና ይኖሩ የነበሩ ከሶስት መቶ በላይ ዜጎችን ከጎዳና በማንሳት ከሱስ እንዲያገግሙ እና ሥራ ሰርተው ኑሮን መምራት እንዲችሉ የሚግዝ ስልጠና በሀረር ፖሊስ ማሰልጠኛ ተቋም እየሰጠ ነው። የሀረሪ ክልል የሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ አቶ ናስር ዩያ ለዶይቸ ቬለ (DW) በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት በተቋሙ ከገቡት ውስጥ የተወሰኑት ከቤተሰቦቻቸው ጋር መቀላቀላቸውን ተናግረዋል። 

ለረዥም ዓመታት በሀረር ጎዳናዎች ሕይወትን ሲመሩ የቆዩት በርካታ ዜጎች የማስቲሽ ሽታን በአፍንጫ ከማሽተት ጀምሮ በተለያዩ ሱሶች የተያዙ መሆን ለኅብረተሰቡ ስጋት መሆኑ ሲገለጥ ቆይቷል። የሀረሪ ክልል የሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ አቶ ናስር አሁን የተሰራው ሥራ ከወንጀል በተጨማሪ እንደ ዜጋ በተገቢው መልኩ ሊቀረፁ የሚገባቸው ዜጎች እንዲቀረፁ የሚያስችል ነው ብለዋል። በአንድ ወር ቆይታ ከሱስ ማላቀቅ እና በሞያ ስራ ላይ ማደራጀት ስራ ይሰራል ብለዋል።

የክልሉ መንግስት ከአንድ ሳምንት ቀደም ሲል ከጎዳና ላይ ሰብስቦ ወደ ማሰልጠኛ  ያስገባቸው እነዚህ ዜጎች በተለያየ ምክንያት ከተለያየ አካባቢ መተው በሀረር ጎዳና ላይ የቀሩ መሆናቸውን ገልፀዋል። በሀር ፖሊስ ማሰልጠኛ ተቋም ከሚገኙት እነዚህ ዜጎች መካከል አንዱ በሰጠው አስተያየት በማዕከሉ እየተሰጠ ያለው ስልጠና ጠቃሚ እና በቀጣይ የተለየ ህይወት ለመምራት የሚረዳ መሆኑን ጠቅሷል። የሀረሪ ክልል የሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ አቶ ናስር ዩያ ከማዕከሉ ቆይታ  በኃላ በክልሉ በተለያየ ዘርፍ አደራጅተው ድጋፍ በመስጠት ወደ ስራ ለማስገባት እየሰሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።

መሳይ ተክሉ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ኂሩት መለሰ