1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ልጆችን ስለ ወሲብ መቼ እና ምን ማስተማር ያሻል?

ዓርብ፣ ጥር 18 2010

ከሰሀራ በስተደቡብ የሚኖረዉ የአፍሪቃ ሕዝብ  77 ከመቶው ከ 35 ዓመት በታች ይሆናል ተብሎ እንደሚገመት ከዚህ በፊት ገልጸናል። በዚህ ወጣቱ በሚያመዝንበት ማህበረሰብ ውስጥ ግን ስለ ወሲብ ማውራት እንብዛም አይደፈርም። ለምን አፍሪቃውያን ወላጆች ልጆቻቸውን ስለዚህ ጉዳይ ማስተማር እንደሚከብዳቸው ኬንያንና ዮጋንዳን እንደምሳሌ በመውሰድ እንቃኛለን።

https://p.dw.com/p/2rLba
Addis Abeba Äthiopien Alltag Jugend
ምስል picture alliance/S. Reboredo

ልጆችን መቼ ነው ስለ ወሲብ ማስተማር የሚገባው? ምንስ ነው ማወቅ ያለባቸው? ይህ እንደየሀገሩ ባህል እና አመለካከት ይለያያል። አንድ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት የኬንያ መንግሥት በየትምህርት ቤቶች የሚሰጠውን ሁሉን አቀፍ የወሲብ ትምህርት መለስ ብሎ እንዲቃኝ ፊርማ እያሰባሰበ ነዉ። ፊርማውን የፈረሙት 4000 የሚጠጉ ሰዎች ስለዚህ ጉዳይ  ማውራቱ የሚያሳስት እና አፍሪቃዊ አይደለም ብለው ያወግዛሉ። ሀቁ ኬንያ ውስጥ ባለፈው ዓመት ብቻ ከ 300 000 በላይ እድሜያቸው ከ 18 ዓመት በታች የሆኑ ተማሪዎች በእርግዝና ምክንያት ትምህርታቸውን ለማቋረጥ ተገደዋል። ብዙ ወላጆች ጉዳዩን አንስተው ከልጆቻቸው ጋር ለማውራት ስለማይደፍሩም ልጆቻቸው ያላቸው አማራጭ መረጃ ከኢንተርኔት አልያም ከጓደኞቻቸው ማፈላለግ እንደሆነ ይገልፃሉ። የ 23 ዓመቷ ክሪስቲና እንደምትለው ወላጆች ስለዚህ ርዕስ ለማውራት ስለሚያፍሩ ነው።« እናቴ ስለ ወሲብ አውርታኝ አታውቅም። ከዛም በ 17 ዓመቴ አረገዝኩ። እርጉዝ መሆኔን ስነግራት ለምን ኮንዶም እንዳልተጠቀምኩ ጠየቀችኝ።  ኮንዶም የማገኝበት መንገድ ከየት ታዉቃለች ብለሽ እ ትጠብቂ ነበር አልኳት። »

በዚህ በጎርጎሮሲያዊው ዓመት የዩንቨርስቲ ትምህርቷን መከታተል የምትጀምረው ክሪስቲና ከወላጆቿ ጋር ነው  የምትኖረው። የልጇ አባትም ልጇን እንደሚንከባከብ እና ብዙም ችግር እንደሌለባት ትናገራለች። ዛሬ ላይ መለስ ብላ ስታስበው ግን ወላጆቿ ስለ ወሲብ አስተምረዋት ወይም ነግረዋት ቢሆን ኖሮ ትምህርቷን እስክትጨርስ ድረስ አታረግዝም ነበር።« በወጣትነት እድሜዬ የበለጠ ባውቅ ኖሮ እያልኩ እመኝ ነበር። ዛሬ ላይ በተመሳሳይ ሁኔታ ያሉ ልጆችን ስመለከት ቀደም ብለው ሊነገራቸው ይገባል ብዬ አስባለሁ። ምክንያቱም አንዳንድ ልጃገረዶች ገና በ 9 ዓመታቸው የወር አበባ ይታያቸዋል።»

Kenia Anti AIDS Kampagne Kondome Jugendliche
ምስል Getty Images/AFP/S. Maina

የኬንያ የጤና ሚኒስቴር ባደረገው  ጥናት  በርካታ ልጃገረዶች ክብረ ንፅሕናቸዉን ያጡበት አማካይ እድሜ 13 ዓመት ነው።  ባለፈው ዓመት ከ 300 000 በላይ እድሜያቸው ከ 10-19 ዓመት የሆኑ ልጃ ገረዶች ላልተፈለገ እርግዝና ተዳርገዋል። ምንም እንኳን ብዙዎች ስለዚህ ርዕስ ማውራት ባይደፍሩም « ሲትዝን ጎ» የተሰኘ አንድ የመብት ተሟጋች ድርጅት የኬንያ መንግሥት ስለ ወሲባዊ ግንኙነት የቀረፀው ትምህርት ጠቃሚ አይደለም ሲል ፊርማ ያሰባስባል። የዚህ ዘመቻ አስተባባሪ የሆኑት አነ ኪኮ መንግሥት ስለ ወሲባዊ ግንኙነት ማስተማሩ ልጆቹን ልቅ እንዲሆኑ እንጂ እንዲቆጠቡ አልረዳም።«  ይህንን ስርዓት የማንቀበልበት ምክንያት ይህ ከውጭ ወደ አፍሪቃ በተለይም ኬንያ የመጣ ስርዓት በመሆኑ ነው። የዩናይትድ ስቴትስ ነው። ከዛም ብሪታንያ ውስጥ ተግባራዊ ሆነ፤ ቀጥሎም ራሳቸውን አደግን ብለው የሚጠሩት ሀገራት ላይ ይተገበር ጀመር።  ይህ ስርዓት ልጆች ከተወለዱ ጀምሮ ለወሲባዊ ግንኙነት የተፈጠሩ እንደሆነ የሚያስተምር ነው። ከአምስት ዓመታቸው ጀምሮ በአካላቸው ማድረግ እንደሚችሉትን ሁሉ እንዲያደርጉ የሚያበረታታ ነው።»

እንደ ኬንያ መንግሥት ከሆነ ሁሉን አቀፍ የወሲብ ትምህርት የሚሰጠው ልጆች አግባብ የሆነ እድሜ ላይ ሲደርሱ ነው።  ይህም በቂ እውቀት እንዲቀስሙ ይረድቷቸዋል። ለአካለ መጠን የደረሱ ወጣቶችን ጉዳይ የሚመለከት የጥናት ተቋም ዋና ስራ አስኪያጅ የሆኑት አልበርት ኦቢዩ እንደሚሉት ትምህርት እና መፅሀፍ ቅዱስ ለየብቻቸው መታየት የለባቸውም።« ሌላው ደግሞ ይህ ባህል እና ሐይማኖታችንን የሚቃወም ሀሳብ ነው የሚለው ነው። ሁላችንም ለእምነታችን የተገዛን ቢሆን ኖሮ ስለ ወሲብ ማውራት ባላስፈለገ ነበር። ለአቅመ ሄዋን ያልደረሱ ልጆች ባላረገዙ ፣ የፆታ ጥቃቶች ባልተፈፀሙም ነበር። ስለዚህ ለእነዚህ ጉዳዮች ተጨባጭ ምላሽ ያስፈልገናል። እኛ የምንለው እና የምናስተምረው መፅሀፍ ቅዱስ ከሚያስተምረው ጋር ወጥ የሆነ ይመስለኛል።»

Kenia Schüler bei Abschlussprüfung für
ምስል DW/Shisia Wasilwa

የአፍሪቃ የህዝብ እና ጤና ጥናት ማዕከል እኢአ በ2016 ዓም ባደረገው ጥናት መሠረት ኬንያውያን ወጣቶች ስለ ኮንዶም፣ የእርግዝና መከላከያ ኪኒኖች እና መርፌዎች አጠቃቀም በትምህርት ቤት መማር ይሻሉ። ከዚህም በተጨማሪ በግብረ ስጋ ግንኙነት ስለሚተላለፉ በሽታዎች  እና እነዚህንም እንዴት መከላከል እንደሚቻል ዋወቅ ይሻሉ።« እኛ ሀገር ያለው ችግር አካባቢያዊ እንደሆኑ አካባቢያዊ መፍትሄ ይሻሉ። ለአቅመ ሄዋን ያልደረሱ ልጆች እርግዝና ፣ የስነ ተዋልዶ አካል መተልተል ሌላው የውጪው ዓለም ክፍል ያስገደደን አይደለም ይህ ልንሸሸገው የማንችለው የራሳችን ችግር ነው። »

ቁጥብነት ዩጋንዳ ውስጥ ትልቅ ርዕስ ነው። በተለይ ወጣቶችን እና ወሲባዊ ግንኙነትን በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ። የዩጋንዳ መንግሥት ወጣቶች ትዳር እስኪመሰርቱ ድረስ ወሲብ ከመፈፀም እንዲቆጠቡ ያበረታታል። ይሁንና ይህ መልዕክት በወጣቱ ዘንድ ችላ የተባለ ይመስላል። የዶይቸ ቬለው ፍራንክ ይጋ ወጣት ዩጋንዳውያን መንግሥት የሚሰብከውን እንዴት እንደሚቀበሉት አጠያይቆ ነበር። « ዛሬ ወንዶች ድንግል የሆነች ልጅ አይደለም የሚፈልጉት። ልምዱ ያላቸውን ነው የሚፈልጉት። ድንግልን ይህን እና ያንን ማስተማር ያስፈልጋል፤ ሌላኛዋ ግን ሁሉም ነገር የገባት ናት በሚል ነው።»

« ቁጥብነት መጥፎ አይደለም። አሁን ተቆጥቤ ነው ያለሁት ፤ ጥያቄው ግን እስከመቼ የሚለው ነው?» ይላሉ ቫኒ እና አኖልድ የተባሉት የዮንቨርስቲ ተማሪዎች። በዩጋንዳ መዲና ካምፓላ በሚገኝ ቪክቶሪ የተሰኘ ቤተክርስትያን ውስጥ ግን ቄሱ ቁጥብነትን በግልፅ ይሰብካሉ።« መፅሀፍ ቅዱስ በግልፅ ለወጣት ሴት እና ወንዶች ራሳቸውን እንዲቆጣጠሩ እና በስሜታዊ ፍላጎት እንዳይመሩ ይገልፃል። ወሲባዊ ስሜታቸውን መቆጣጠር የማይችሉ ከሆነ ደግሞ ትዳር እንዲመሰርቱ ይመክራል። መልዕክቴ ግልፅ የሆነ ይመስለኛል እንደ መፅሀፍ ቅዱስ ከሆነ ወሲባዊ ግንኙነት ትዳር ለመሰረቱ ብቻ ነው።»

Angola Jugendliche & Kinder in Luanda, Boa Vista Slum
ምስል Getty Images/AFP/S. de Sakutin

ከቤተክርስትያን ውጪ ለልጆች ስለ ወሲብ ለማወቅ ከባድ ነው። በባህሉ መሠረት ልጆችን ስለ ወሲብ እንዲያስተምሩ የሚፈቀድላቸው ወላጆች ሳይሆኑ በአባት በኩል ያሉ አክስቶች ብቻ ናቸው። ጡረታ ላይ ያሉት መምህር አሌክስ ዋንዴባ ወላጆች ልጆቻቸውን ከማስተማር ማመንታታቸው ወጣቶች ከወሲብ እንዳይቆጠቡ እና ስህተት እንዲሰሩ ምክንያት ነው ብለው ያምናሉ።

«  አንዳንድ ጊዜ ወላጆች የሚገባቸውን ሚና አይፈፅሙም። አብዛኞቹ ወላጆች ስለዚህ ጉዳይ ከልጆቻቸው ጋር ለማውራት ይፈራሉ። ይሄ የአፍሪቃውያን አስተሳሰብ ደግሞ አለ።ወላጆች ወሲብን የሚመለከት ጉዳይን አስመልክቶ ለማውራት ግልጽ አይደሉም። ልጆች መንገዱን ሲያገኙ ደግሞ አዲስ ነገር መሞከር ይፈልጋሉ። ስለዚህ ወሲብ ከመፈፀም ለመቆጠብ ከባድ ያደርግባቸዋል።» ይህ አመለካከትም በሙባራ ዮንቨርስቲም ይስተዋላል።« ዩንቨርስቲ ስገባ እና ስለ ቁጥብነት ሳወራ ጅል ይሉኝ ነገር። አንዳንዶች ራስሽን ከቆጠብሽ ሰውነትሽ ጤነኛ አይደለም ማለት ነው ይሉኝ ነበር። ያን ጊዜ ቁጥብ መሆኑን ለመተው ወሰንኩ።»

እንደ አኮል አማዚማ ያሉ አንዳንድ ዩጋንዳውያን መምህራን ደግሞ ወጣቱ ፍላጎት እያደረበት እንዲቆጠብ መገፋፋቱ ይበልጥ አደገኛ ለሆነ ችግር ሊጋልጥ ይችላል።

« በ 16 እና በ 24 , 25 ዓመት መካለል ያለው ዕድሜ ለወጣቱ እጅግ አደገኛው ጊዜ ነው። ጀብድ መስራት ይፈልጋሉ። ብዙ የአካል ለውጦች የሚያዩበት ጊዜ ነው ። እና ወሲብ ከመፈፀም እንዲቆጠቡ መንገሩ የማይሆን ነገርን እንደመንገር ማለት ነው። 78 ከመቶው ዩጋንዳዊ እድሜው ከ 30 ዓመት በታች ነው። ከነዚህ መካከል የተወሰነ ከመቶው እንኳን የህይወቱን አቅጣጫ ከሳተ ወይም ትምርቱን ለማቋረጥ ከተገደደ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ እና የማህበራዊ ሁኔታው ላይ ከፍተኛ ጫና ያሳድራል። በሌላ በኩል ደግሞ በርካታ ወጣት የሚያወግዘው የመንግሥት አቋም ዳግም መፈተሽን ይሻል።

እናንተስ ልጆችን ስለ ወሲብ መቼ እና ምን ማስተማር ያሻል ትላላችሁ? የወላጅ እና የትምህርት ቤት ሚናስ ምን ሊሆን ይገባል? ሀሳባችሁን አጋሩን።

ሮዳ ኦዲአምቦ/ ፍራንክ ይጋ /ልደት አበበ