1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ለአንባቢያን «የመጽሐፍት ካፌ»

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 24 2012

ማሩ ጌጡ ይባላል። ትውልዱና እድገቱ በባሕር ዳር ከተማ ነው፡፡ የ32 ኣመቱ ወጣት ማሩ ባለትዳር ነው፡፡ የመንግስት ቋሚ ሥራ የለውም። በግሉ የመኖሪያ ቤት ኤሌክትሪክ መስመር ዝርጋታና የውኃ ቧንቧ ስራዎችን በመሥራት ነው የሚተዳደረው።

https://p.dw.com/p/3Ve2X
Äthiopien "Book Cafe" von Maru Getu
ምስል DW/A. Mekonnen

በተለይ የቆዩ መጻሕፍትን አባስቧል

ማሩ ከልጅነቱ ጀምሮ የማንበብ ፍላጎት እንዳለው ይናገራል፡፡ ከ1500 በላይ መጽሐፍትን ማንበቡንም ከዶይቼ ቬሌ ጋር በነበረው ቆታ አመልክቷል፡፡ እየቀነሰ የመጣውን የማንበብ ልምድ ለመመለስና እስካሁን ያነበባቸውን መጽሐፍት በማጠራቀም “የመጽሐፍት ካፌ” በመክፈት ማንኛውም ሰው በነፃ እንዲያነብብ  ሁኔታዎችን አመቻችቷል፡፡

ወጣት ማሩ እንደሚለው አንባቢ ትውልድ እየጠፋ ነው በመሆኑም ይህን ለመመለስ የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ይህን ሥራ እንደጀመረው አመልክቷል፡፡ አሁን የንባብ ቦታ የሆነው አካባቢ እጅግ ቆሻሻ የበዛበት እንደነበር የሚናገረው ወጣት ማሩ  አሁን አካባቢውን ለመጽህፍት ማንበቢያነት ብቻ ሳይሆን በራሱ ወጪ በማጽዳትና አትክልቶችን በመትል ማራኪ አድርጎታል፡፡

በመጽሐፍት ካፌው ውስጥ ሲያነብቡ ካገኘኋቸው ወጣቶች መካከል ወጣት መዝገቡ ማናዬ አንደገለፀልኝ የወጣት ማሩ ተግባር ለብዙዎቹ አርአያ መሆኑን አመልክቶ  በተለያዩ ሱሶች ተጠምደው ሚውሉ ወጣቶች በእንደዚህ ያሉ ቦታዎች ቢውሉ በእውቀት እንደሚታነፁና ከሱሳቸው አንደሚላቀቁ ተናግሯል፡፡

Äthiopien "Book Cafe" von Maru Getu
ምስል DW/A. Mekonnen

እንግሊዝኛ መጽሐፍትን በብዛት እንደሚያነብብ የገለጸልኝ ወጣት ዮጋሳን ያሲን እዚህ በመዋሉ ከነበረበት ሱስ እየተላቀቀ ነው፡፡ ማንበብ ምሉዕ ደርጋል የሚለው ዮጋሳን የወታቱ የማንበብ ልምድ ገና አልተመለሰም ሲል አስተያየት ሰጥቷል፡፡

ወጣት ማሩ እንደችግር ያነሳው መጽሀፍቶቹን በየቀኑ ወደ ቤት ማመላለስ ለመጽሐፍቱ እንግልት፣ እንደዚሁም በዝናብ ወቅት ለብልሽት እየዳረጋቸው በመሆኑ የሚመለከተው አካል በዚህ ረገድ እገዛ እንዲያደርግለት ጠይቋል፡፡

መጽሐፍትን በቤታቸው ያከማቹ ሰዎችም በውሰት ወይም በስጦታ እንዲያበረክቱለትና ትውልዱን አንባቢ እናድርገው ሲል ጠይቋል፡፡

ዓለምነው መኮንን 

ማንተጋፍቶት ስለሺ