1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ህወሓት በኢህአዴግ ዉሕደት አቋሙን ለመግለፅ ጉባኤ ሊቀመጥ ነዉ

ሰኞ፣ ኅዳር 15 2012

ህወሓት የኢህአዴግ ውህደት አጀንዳ በስራ አስፈፃሚውና ማእከላይ ኮሚቴ ደረጃ ያልተቀበለው ቢሆንም የመጨረሻ የሚታወቀው በቅርቡ በሚጠራው የህወሓት ጉባኤ ላይ ነው ሲሉ የህወሓት ሊቀ መንበር ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ተናገሩ፡፡ ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል በወቅታዊ ጉዳዮች ዙርያ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

https://p.dw.com/p/3Thbz
Äthiopien Addis Abeba | Debretsion Gebremikial, TPLF
ምስል DW/M. Hailesilasie

ህወሓት ስለዉኅደቱ ዉሳኔ ለመስጠት ጉባዔ ይቀመጣል

የህወሓት ሊቀመንበር ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል እንዳሉት ህወሓት ከሁለት ሳምንት በፊት በተደረገው የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ስብሰባ ላይ የውህድ ፓርቲ ጉዳይ አጀንዳ እንዲሆን አልፈለገም ነበር፡፡ የሀገሪቱ ሰላም፣ ኑሮ ውድነት፣ የሚስተዋለው የሕግ ጥሰትና መጪው ሀገራዊ ምርጫ ጉዳዮች የስብሰባው አጀንዳ እንዲሆኑ በህወሓት በኩል ግፊት መደረጉ የጠቆሙት ዶክተር ደብረፅዮን ይሁንና በአብላጫ ድምፅ ኢህአዴግን የማዋሃድ ጉዳይ ለውይይት እንዲቀርብ ተደርጓል ብለዋል፡፡

ኢህአዴግን ውሁድ ፓርቲ እንዲሆን እየተደረገ ያለው እንቅስቃሴ በርካታ የሕግና የግንባሩ መተዳደሪያ ደንብ ጥሰቶች ያሉበት ያሉት የህወሓት መሪ ዶክተር ደብረፅዮን "አካሄዱ ኢህአዴግን ውሁድ ፓርቲ ማድረግ ሳይሆን በስመ ውህደት አዲስ ፓርቲ የመፍጠር ነው" ብለውታል፡፡

በኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ስብሰባ ላይ የተሳተፉ 7 የህወሓት ስራ አስፈፃሚ አባላት ውህደቱን እንደተቃወሙ የተናገሩት ሊቀ መንበሩ በኢህአዴግ በኩል 6 ተብሎ የተጠቀሰው ስህተት ነበር ብለዋል፡፡

Smart ID in der Region Tigray
ምስል DW/M. Hailesselassie

ከውሳኔው በኋላ ከኢህአዴግ ሊቀ መንበር ዶክተር አብይ አሕመድ ጋር ውይይት ተደርጎ "የውህደት አጀንዳው ደግመን እንድናየው ጥያቄ ቀርቦልን ነበር" የሚሉት ዶክተር ደብረፅዮን በህወሓት በኩል ግን የአቋም ለውጥ እንደሌለ ጠቁመዋል፡፡

እንደ ዶክተር ደብረፅዮን ገለፃ ሂደቱ 'ውህደት' ሳይሆን አዲስ ፓርቲ የማቋቋም ስራ ነው ብለውታል፡፡ በተጨማሪም አጋር ተብለው የሚታወቁት ፓርቲዎች በውህደት አጀንዳው ዙርያ አስቀድመው እንዲፈርሙ መደረጉም ጠቅሰዋል፡፡

የግንባሩ ውህደት ጉዳይ የህወሓት ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴና ማእከላይ ኮሚቴው እንዳልተቀበለው የጠቀሱት የፓርቲው ሊቀ መንበር አጀንዳው የመጨረሻ ውሳኔ የሚያገኘው ግን በህወሓት ጉባኤ መሆኑ ተናግረዋል፡፡ ለዚህም ህወሓት አስቸኳይ ጉባኤ ለማድረግ ውሳኔ ማስተላለፉ ተጠቁሟል፡፡

ሚሊዮን ኃይለሥላሴ 

አዜብ ታደሰ 

ተስፋለም ወልደየስ