1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

22 ተኛዉ የአፍሪቃ ህብረት የመሬዎች ጉባኤ

ሐሙስ፣ ጥር 22 2006

22 ተኛው የአፍሪቃ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ ተጀመረ ። ዛሬ ጠዋት የተከፈተው የዚህ ጉባኤ ይፋ አጀንዳ ግብርናና የምግብ ዋስትና የነበረ ቢሆንም በማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክና በደቡብ ሱዳን የተባባሰው ግጭት ያስከተለው ሰብዓዊ ቀውስ የጉባኤው ትኩረት በሁለቱ ሃገራት ላይ እንዲሆን አድርጓል።

https://p.dw.com/p/1Azfq
Afrika - Beginn des Gipfels der Afrikanische Union
ምስል Getty Images

በጉባኤው መክፈቻ ላይ የአፍሪቃ ህብረት ከሚሽን ሊቀመንበር ንኮሳዛና ድላማኒ ዙማ በሁለቱ ሃገራት የሚካሄዱ ግጭቶች ሰለባ በሆኑ ህዝቦች በተለይም ህፃናትና ሴቶች በደረሰባቸው ችግር የተሰማቸውን ሃዘን ገልፀዋል ። ዙማ በሃገራቱ ዘላቂ ሰላም ለማስፈን ተባብሮ መሥራትና ለተግባራዊነቱም አልሞ መነሳት እንደሚገባ አሳስበዋል።

« ባለፈው ታህሳስ ወር በማረፋቸው ያዘነው ታዋቂው የአፍሪቃ ልጅ ኔልሰን ማንዴላ አንድ ነገር በተግባር ተተርጉሞ እስኪታይ ድረስ የማይቻል ይመስላል ይሉ ነበር ። በርግጥ ራዕይ ሊኖረን ይገባል በተግባር መፈፀምም ይኖርብናል እስከሚተገበር ድረስ ግን የማይቻል ይመስላል።የወቅቱ የአፍሪቃ ህብረት ሊቀመንበርነታቸውን ዛሬ ለሞሪቴንያው ፕሬዝዳንት መሀመድ ኡልድ አብደል አዚዝ ያስረከቡት የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው የክፍለ ዓለሙ ዐብይ ችግር የሆነው ድህነት ዋነኛው የመሪዎቹ አጀንዳ መሆኑን አስታውሰዋል። «ስር የሰደደውን ድህነት ማስወገድ አሁንም ሆነ ወደፊት ቅድሚያ ሰጥተን የምንነጋገርበት ጉዳይ ነው »በዙር የሚደርሰውን የህብረቱንየሊቀመንበርነት ሥልጣን ዛሬ የተረከቡት የሞሪቴንያው ፕሬዝዳንት አብደል አዚዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምን በሊቀመንበርነታቸው ዘመን አፍሪቃ በክፍለ ዓለሙና በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ያላትን ሚና ለማጠናከር አበርክተዋል ባሏቸው አስተዋጽኦዎች አወድሰዋቸዋል። በጉባኤው ላይ 34 የአፍሪቃ መሪዎች ተገኝተዋል ። የሁለት ቀናቱ የመሪዎች ጉባኤ ካበቃ በኋላ ቅዳሜ የአፍሪቃ መሪዎችና ምዕራባውያን ዲፕሎማቶች የሚገኙበት ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ለዘመተው የአፍሪቃ ህብረት ኃይል ገንዘብ ለማሰባሰብ ቃል የሚገባበት ጉባኤ እንደሚካሄድ የአፍሪቃ ህብረት የሰላምና የፀጥታ ምክር ቤት ሃላፊ ኤል ጋሲም ዋኔ አስታውቀዋል።

Afrika - Beginn des Gipfels der Afrikanische Union
ምስል picture-alliance/dpa

ጉባኤዉ በሚካሄድበት በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘዉ ወኪላችን ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ በጉባኤዉ መክፈቻ ላይ ተገኝቶ፤ የመሬዎቹን የመወያያ ነጥቦች በመያዝ ዘገባ ልኮልናል።

ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ

አዜብ ታደሰ

ሂሩት መለሰ