የውጭ ዜጎች በጀርመን
ዓርብ፣ ታኅሣሥ 16 2002ማስታወቂያ
ከአስራ ስድስቱ የጀርመን ፌደራል ክፍላተ ሀገር ፣ ምዕራባዊው የኖርድ ራይን ቬስት ፋይልያ ፌደራዊ ክፍለ ሀገር በህዝብ ብዛት ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛል ። የዚህ ክፍለ ሀገር ህዝቡ ቁጥር አስራ ሰባት ሚሊዮን ይደርሳል ። ይኽው ክፍለ ሀገር ከሌሎቹ ክፍላተ ሀገር ጋር ሲነፃፀር የበርካታ የውጭ ዜጎች መኖሪያ ነው ። ከበርሊን ከሀምቡርግ እና ከሙንሽን ቀጥሎ በትልቅነት አራተኛውን ደረጃ ከምትይዘው ከኮሎኝ ከተማ ነዋሪ ሲሶው የውጭ ዜጋ ነው ። በዚህች ከተማ ከሚኖሩ የውጭ ዜጎች አብዛኛዎቹ ከህብረተሰቡ ጋር ያልተቀራረቡ የተገለሉና በዝቅተኛ ስራዎችም የተሰማሩ ናቸው ። ይህን ለመለወጥም በከተማዋ ማዘጋጃ ቤት ስር የውጭ ዜጎች ከህብረተሰቡ ጋር ተቀራርበው የሚኖሩበትን መንገድ የሚያመቻች ምክር ቤት ከተመሰረተ አምስት ዓመት ተቆጥሯል ። የዚህ ምክር ቤት አባላት የመጀመሪያው ምርጫ የዛሬ አምስት ዓመት በህዳር ወር የተደረገ ሲሆን ሁለተኛው ምርጫ ደግሞ እ.ጎ.አ በ2010 መጀመሪያ ላይ ይካሄዳል ። በዚህ ምርጫ ከሚወዳደሩት ውስጥ በትውልድ ኢትዮጵያዊ በዜግነት ጀርመናዊ የሆነው የኮሎኝ ከተማ ነዋሪ ወጣት እስጢፋኖስ ሳሙኤል አንዱ ነው ።