1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢንተርኔት መዘጋት ያስከተለዉ ኪሳራ በኢትዮጵያ

ረቡዕ፣ መስከረም 24 2010

ከሳሃራ በታች የሚገኙ የአፍሪካ ሀገራት በተለያዩ ጊዜያት የኢንተርኔት አገልግሎት በመዝጋታቸዉ ሳቢያ ከ237 በላይ ሚሊዮን ዶላር ኪሳራ ደርሶባቸዋል ሲል አንድ ጥናት አመለከተ።ከዚህም ዉስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆነዉ ኪሳራ የደረሰዉ  በኢትዮጵያ መሆኑን  ባለፈዉ ሳምንት መጨረሻ በደቡብ አፍሪካ  ጁዋንስበርግ ከተማ ይፋ የሆነዉ ይህ ጥናት አመልክቷል።

https://p.dw.com/p/2lDeY
Symbolbild Cyberkriminalität
ምስል picture-alliance/dpa/O.Berg

Internet shutdowns in Ethiopia - MP3-Stereo


እንደ ጥናቱ የኢንተርኔት አገልግሎት መዝጋት ከኢኮኖሚ ጉዳቱ ባሻገር የሰብአዊ መብት ጥሰት ጭምር በመሆኑ ሊቆም ይገባል ተብሏል።
ጥናቱን ያካሄደዉ የዓለም ዓቀፉ የኢንፍርሜሽንና የኮሚኒኬሽን ፓሊሲ ትብብር  ለምስራቅና ለደቡባዊ አፍሪካ በምህጻሩ CIPESA እንዳስታወቀዉ ከጎርጎሮሳዉያኑ 2015 ጀምሮ ቢያንስ 12 የአፍሪካ ሀገራት በምርጫ ፣በሀገር ዓቀፍ ፈተናና ህዝባዊ ተቃዉሞ በተቀሰቀሰ  ወቅት የኢንተርኔት አገልግሎት ዘግተዋል። የአፍሪካ መንግስታት ሆን ብለዉ የሚያደርጉት የኢንተርኔት መዝጋት እየጨመረ በመምጣቱ ጥናቱ  መካሄዱን የድርጅቱ ከፍተኛ ተመራማሪና  ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ዋይራጋላ ዋካቢ ለዶቼ ቬለ ገልጸዋል።
«በአፍሪካ የኢንተርኔት መዘጋት  እየጨመረ መምጣቱን ታስተዉላለህ።ከ2015 ዓ/ም ጀምሮ ቢያንስ  12 ከሰሃራ በታች የሚገኙ የአፍሪካ ሀገሮች ኢንተርኔት ዘግተዋል።አንዳንዶቹ ሀገራት ከ 1 ጊዜ በላይ አብዛኛወቹ ደግሞ ለበርካታ ጊዜያት ዘግተዋል።ለምሳሌ ዩጋንዳን፣ቻድን፣ዲ/ኮንጎንና ኢትዮጵያን የመሳሰሉ ሀገራት ስንመለከት 2 ና3 ወይም ከዚያም በላይ iz ዘግተዋል።ስለዚህ የኢንተርኔት መዝጋት ምን ያህል የአፍሪካ ሀገራት ላይ ተፅዕኖ እያመጣ እንዳለ እንገነዘባለን።ለዚህ ነዉ ጥናቱን ያካሄድነዉ።»

ባለፈዉ ሳምንት መጨረሻ በጁዋንስበርግ ከተማ በአፍሪካ ኢንተርኔት  ነጻነት  ላይ  በመከረዉ  ስብሰባ ላይ፤ ይፋ የሆነዉ  ይህ ጥናት  የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጥ የየሐገራቱን ኢኮኖሚ ከመጉዳቱ በላይ መደበኛ አገልግሎቶችን አደናቅፏል ።የሰዉ ልጆችን የእለት ተዕለት ህይወትም አስቸጋሪ ያደርጋል። ከምንም በላይ ደግሞ መረጃ የማግኘት  መብትን ይጋፋል።  
 «በጣም ግልፅ ነዉ።ኢንተርኔትን  መዝጋት የሰዉ ልጆችን መብት ይጋፋል። መረጃ የማግኜትና ሀሳብን በነፃነት መግለጽን የመሳሰሉ መብቶችን ይጥሳል። አገልግሎቱን ማቋረጥ በሀገራት እኮኖሚና በግለሰቦች ኑሮ ላይ የሚያሳድረዉ ተፅዕኖም በዉል እየታወቀ አይደለም።»

Symbolbild Cyberkriminalität
ምስል picture-alliance/dpa/H. Fohringer

እንደ ጥናቱ ላለፉት 3 ዓመታት  ከስሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ  ሀገራት  ኢንተርኔት በትንሹ ለ236 ቀናት ተዘግቷል።በዚህ የተነሳ  ሀገራቱ ከ237 ሚሊዮን  ዶላር በላይ ኪሳራ ደርሶባቸዋል።በቻድ ፣በጋቦንና በኡጋንዳ በምርጫ ጊዜ  በዲሞክራቲክ ኮንጎ፣በቡሩንዲ፣በኢትዮጵያና በቶጎ በህዝባዊ ተቃዉሞና በፈተና ወቅት  አገልግሎቱን ዘግተዋል።
ካሜሩን ዉስጥ ሁለት የእንግሊዝኛ ተናጋሪ ግዛቶች ራስን የማስተዳደር ጥያቄ አንስተዉ በቀሰቀሱት ተቃዉሞ የሀገሪቱ መንግስት ለ 93 ቀናት  አግልግሎቱን በመዝጋቱ ወደ 38 ሚሊዮን ዶላር፤ ኬንያ ደግሞ አገልግሎቱን ሙሉ ለሙሉ በዘጋችበት ወቅት በቀን 6 ነጥብ 3 ሚሊዮን ዶላር አጥታለች።  
ኢትዮጵያ ደግሞ  በክልልና በሀገር ዓቀፍ ደረጃ  ለ36 ቀናት የኢንተርኔት አገልግሎት ተዘግቷል።በእነዚህ ቀናት ሀገሪቱ 123 ሚሊዮን ዶላር አጥታለች።ከሌሎች ሀገራት ጋር ሲነጻጸር ጉዳቱ ከፍተኛ ነዉ። ይህ የሚያሳየዉ  የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ለሀገሪቱ  ኢኮኖሚ የሚያበረክተዉ አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን ነዉ  ሲል  ጥናቱ አመልክቷል።ዶክተር ዋይራጋላ እንደሚሉት ድርጊቱ በመዋዕለ ንዋይ ፍሰትና በንግድ ስራ ላይ  ለሚሰማሩም  መተማመንን  ያሳጣል።
 «ለኢትዮጵያ የጠቀስነዉ 123 ሚሊዮን ዶላር ትልቅ አሃዝ ነዉ።ጉዳቱም ቢሆን በጣም  ከፍተኛ ነዉ።በሀገሪቱ ላይም የረዥም ጊዜ የኢኮኖሚ ተፅዕኖ አለዉ።ስለዚህ ኢንተርኔትን የሚዘጉ ኢትዮጵያን የመሳሰሉ ከሰሃራ በታች የሚገኙ የአፍሪካ ሀገራት ዉጤቱን በደንብ ሊገነዘቡት ይገባል።ኢኮኖሚን ይጎዳል።የመረጃ ቴክኖሎጅ አስተዋፅኦን ይገድባል።ባለወረቶችን በማግኜት ረገድም ተፅዕኖ ያሳድራል።»

የኢንተርኔት አገልግሎቶችን በየሰበቡ መዝጋት የሃገራትን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ከመጉዳቱ ባሻገር የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመሆኑም መንግስታት ጉዳዩን ቆም ብለዉ ሊያስቡበት ይገባል ሲልም የዓለም ዓቀፉ የኢንፍርሜሽንና የኮሚኒኬሽን ፓሊሲ ትብብር  ለምስራቅና ለደቡብ አፍሪካ በምህጻሩ CIPESA  አሳስቧል።

ፀሐይ ጫኔ

ነጋሽ መሀመድ