1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአውሮጳ ህ. የስደተኞች ፖሊሲ

ቅዳሜ፣ የካቲት 3 2004

2011 ዓም በአውሮጳ የስደተኞች ፖሊሲ ታሪክ ውስጥ እጅግ ብዙ ስደተኞች የሞቱበት ዓመት መሆኑን ፕሮ አዙል የተባለው የስደተኞች ጉዳይ ተከታታይ ድርጅት ያወጣው መግለጫ አስታወቀ። በድርጅቱ ግምት ወደ አንድ ሺህ ስድስት መቶ የሚጠጉ ስደረኞች በሜድትሬንያን ባህር በኩል አውሮጳ ለመግባት ሲሞክሩ ሕይወታቸው አልፎዋል።

https://p.dw.com/p/141za
ምስል picture-alliance/dpa

የጀርመን ሀገር አስተዳደር ሚንስቴር ባለፈው ታህሳስ ወር ባካሄደው ጉባዔው ልዩ ከለላ ለሚያስፈልጋቸው ስደተኞች እአአ ከ2012 እስከ 2014 ዓም ድረስ ሦስት መቶ ሰፈራ ቦታዎችን ለማዘጋጀት ወስኖዋል። የፕሮ አዙል ባልደረባ  ካርል ኮፕ እንዳስታወቁት-እነዚህ የሰፈራ ቦታዎች ወደ ትውልድ ሀገራቸው ሊመለሱ ለማይችሉ፡ አሁን ተገን ባገኙባቸው ጣቢያዎችም ሁኔታው እጅግ አስከፊ በመሆኑ መቆየት ለማይችሉ ስደተኞች ማስቀመጫ ቦታዎች ናቸው።

«ጀርመን ሀገር ይህን መሰሉን ውሳኔ ማሳለፋችን የሚሞገስ ቢሆንም፡ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ይህን ሰብዓዊ ቀውስ በተመለከተ ርምጃ መውሰድ የጀመረው እጅግ ዘግይቶ መሆኑን መግለጽ አስፈላጊ ነው። »ይህ ዕድል ከሚሰጣቸው ስደተኞቹ መካከል ብዙዎቹ ከቱኒዝያ የሹሹ መጠለያ ጣቢያ ያሉ ናቸው።

Italien Lampedusa Immigranten aus Nordafrika
ምስል AP

በሹሹ መጠለያ ጣቢያ ካሉት ስደተኞች መካከል ዩኤንኤችሲአር እስካሁን ሦስት ሺዎቹን ተቀብሎዋል። ብዙዎቹ ስራ ፍለጋ ከሰሀራ በስተደቡብ በከሚገኙ አፍሪቃውያት ሀገሮች ወደ ሊቢያ የሄዱ ናቸው። ግን በሊቢያ የርስበርሱ ጥርነት ሲፈነዳ ለሁለተኛ ጊዜ በመሸሽ ሊቢያን ከቱኒዝያ ጋ በሚያዋስነው ድንበር በተሰሩ መጠለያ ጣቢያዎች መኖር ጀምረዋል። ይሁንና እነዚህ ስደረኞች ባካባቢው ካሉ ጎሳዎች ጥቃት እንደሚሰነዘርባቸው ዩኤንኤችሲአር አስታውቋል። ስደተኞቹ አሁን በሌላ ሦስተኛ ሀገር የመኖሪያ ፈቃድ የሚግኘት ተስፋ አድርገዋል።

የሀገር አስተዳደር ሚንስቴር ባወጣው ዘገባ መሠረት፡ ወደ ጀርመን የሚመጡትን ስደተኞች ጉዞ የሚያደራጅ አንድ የልዑካን ቡድን በቅርቡ ወደ ቱኒዝያ ይሄዳል። ይህ መልካም ቢሆንም፡ ይላሉ የፕሮ አዙል ባልደረባ ካርል ኮፕ፡ ከሌሎች የአውሮጳ ህብረት ሀገሮች ጋ ስትነጻጸር ጀርመን ስደተኞቹን መልሶ የማስፈሩን ተግባር የጀመረችው እጅግ ዘግይታ እንደሆነ ይሰማቸዋል።

« በአውሮጳ ህብረት ካሉት ሀገሮች ሁሉ ጀርመን ትልቅዋና ሀብታሟ ሀገር ናት። እና ጀርመን ስደተኞቹን ለመቀበል ዝግጁ መሆንዋን ለመግለጽ እስካሁን መዘግየቷ አሳዛኝ ነው።  »እንደ ካርል ኮፕ አመለካከትም፡ ጀርመን ያዘጋጀችው የሰፈራ ቦታም ቁጥር ብዛት ያን ያህል አይደለም።   «ጀርመን ተጨማሪ ርዳታ ማቅረብና ተጨማሪ ትብብር ማሳየት ይገባታል። ወደፊት በሰፈራው ጉዳይ ላይ በሚደረገው ውይይትም ላይ የጀርመን ዝግጁነት ከፍ ያለ እንዲሆን እንፈልጋለን»   በሄሰን ፌዴራዊ ክፍለ ሀገር ምክር ቤት የአረንጓዴዎቹ ፓርቲ የስደተኞች ጉዳይ ተመልካች ዘርፍ ቃል አቀባይ ሚውርቪን ኧዝቱርክ የሀገር አስተዳደሩን ሚንስቴር ውሳኔ በደስታ ተቀብለውታል። ይሁን እንጂ፡ በመላ አውሮጳ አንድ ኃላፊነት የታከለበት የስደተኞች ፖሊሲ ቢወጣ የተሻለ እንደሚሆን ከመጠቆም ወደኋላ አላሉም።

Flüchtlinge Griechenland NO FLASH
ምስል picture-alliance/dpa

«እዚህ ላይ መቀየር ያለበት ጉዳይ አለ ብዬ አምናለሁ። ምክንያቱም፡ እንደሚታየው፡ አውሮጳ ድንበሮችዋን የመዝጋቱን ፖሊሲ የመከተል አዝማሚያ እያሳየች ነው። ስደተኞችን እና የሰብዓዊ ጥያቄዎችን በሚመለከቱ ጥያቄዎች ላይ ማንም በኃላፊነት እንዳይጠየቅ ሲሸሽ መታየቱ የሚያሳዝን ነው። »

ከቱኒዝያ የሹሹ መጠለያ ጣቢያ ስደተኞችን ለመቀበል የወሰኑ ሀገሮች ቁጥር አሁን፡ ጀርመንን ጨምሮ ወደ ዘጠኝ ከፍ ብሎዋል። በዩኤን ኤች ሲ አር ዘገባ መሠረት፡ አስችኳዩ ከለላ ከሚያስፈልጋቸው  ሦስት ሺህ ስደተኞች መካከል እስካሁን ሰባት መቶ ሠላሳ ብቻ ናቸው ወደ አውሮጳ የመጡት። በዓለም አቀፍ ደረጃ ስደተኞቹን ለመቀበል ዝግጁ የሆኑ ሀገሮች ሰማንያ ሺህ የሰፈራ ቦታዎችን ዝግጁ እንደሚያደርጉ ተሰምቶዋል። ይሁን እንጂ፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ አስቸኳዩ ከለላ የሚያስፈልጋችው ስደተኞች ቁጥር በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ውስጥ በአሥር እጥፍ ጨምሮ ወደ ስምንት መቶ ሺህ ከፍ እንደሚል ይገመታል።

አርያም ተክሌ

መስፍን መኮንን

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ