1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የባሕር ዳር እና መቐለ ነጋዴዎች የሰላም ጥሪ

ሐሙስ፣ ግንቦት 8 2011

ከባሕር ዳር እና ሌሎች የአማራ ክልል አካባቢዎች የተውጣጡ ነጋዴዎች ወደ ትግራይ ክልል መቐለ በመጓዝ ከከተሟዋ ነጋዴዎች ጋር በሰላም ጉዳይ መከሩ፡፡ የሁለቱ ክልል ነጋዴዎች የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን ለማጠናከርም የበኩላቸው እንደሚወጡ ገልፀዋል፡፡

https://p.dw.com/p/3IcdK
Äthiopien Stadtansicht Mekele
ምስል DW/M. Hailessilasie

የባህርዳር እና መቐለ ነጋዴዎች የሰላም ጥሪ

በአማራ እና ትግራይ ክልሎች የሚታዩ የፀጥታ ችግሮች የንግድ እንቅስቃሴው እንደጎዳው የሁለቱ ክልሎች የንግድ ማኅበረሰብ ተናግረዋል። ነጋዴዎቹ ለሚፈጠሩ ችግሮች መንግሥት አፋጣኝ መፍትሔ በመስጠት የሚያጋጥማቸውን እንግልት መቀነስ ይገባዋል ብለዋል። 

በባሕር ዳር ከተማ እንዲሁም ሌሎች የአማራ ክልል አካባቢዎች የሚገኙ ነጋዴዎች ያቀፈው የባሕር ዳር ንግድና ዘርፍ ማሕበራት ምክር ቤት አመራሮችና አባላት ከአቻቸው የመቐለ ንግድና ዘርፍ ማሕበራት ምክር ቤት ባደረጉት ውይይት በንግድ ሥራ በተጨማሪ በህዝብ ለህዝብ መቀራረብ ዙርያ መነጋገራቸው የመቐለ ንግድና ዘርፍ ማሕበራት ቦርድ አባል አቶ በሪሁ ሀፍቱ ገልፀውልናል። 

የባሕር ዳር ከተማ ንግድና ዘርፍ ማሕበራት ምክር ቤትፕሬዝዳንት አቶ መንገሻ በላይ በበኩላቸው ከዚህ በፊትም የንግድ ማሕበረሰቡ ለሰላም የተለያዩ ጥረቶች ሲያደርግ መቆየቱ ተናግረዋል። በትግራይና አማራ ንግድ እንቅስቃሴ ላይ የሚያጋጥሙ መሰናክሎች መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ ሊፈታው ይገባል ያሉት ነጋዴዎቹ የእነርሱን አርአያነት የፖለቲካ አመራሮች እንዲከተሉ አሳስበዋል። ለችግሮች ዘላቂ መፍትሔ ለማበጀት የፖለቲካ አመራሮቹ መወያየት አለባቸው ብለዋል። 

በአማራና ትግራይ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ተፈጥረው በነበሩ የፀጥታ ችግሮች ምክንያት በንግድ እንቅስቃሴ ላይ ተፅእኖ ሲፈጥር መቆየቱ ይታወሳል። በተለይም ትግራይ ከተቀረው የኢትዮጵያ ክፍል የሚያገናኙ መንገዶች በተደጋጋሚ መዘጋታቸው የቅርብ ግዜ ትውስታ ነው። በዚህም ነጋዴዎች ሥራቸው ለመከወን እየተቸሩ መቆየታቸው በተደጋጋሚ ይጠቅሳሉ። 

ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ። 

ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ

ተስፋለም ወልደየስ 

ኂሩት መለሰ