የሕዳሴ ግድብ የሦስትዮሽ ድርድር
ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ ቅዳሜ እና እሁድ በአዲስ አበባ ያደረጉት የታላቁ የሕዳሴ ግድብ የሦስትዮሽ ድርድር ውጤት አልባ ሆኖ ስለመጠናቀቁ በግብጽ በኩል ተገለፀ። ድርድሩ አዲስ አበባ ውስጥ መጀመሩን ገልጾ የነበረው የኢትዮጵያ መንግሥት እስካሁን በግልጽ ያለው ነገር ባይኖርም የግድቡ ዋና ተደራዳሪ አምባሳደር ስለሺ በቀለ "ኢትዮጵያ የጋራ መፍትሔ ላይ ለመድረስ በበጎ መንፈስ ትሠራለች" ሲሉ በማህበራዊ መገናኛ ዐውታር ገፃቸው ጽፈዋል። ሦስቱ ሀገራቱ ለድርድር ከተቀመጡ ማግስት ውይይታቸው ለምን ስምምነት ያጣል? የአፍሪካ ሕብረትስ ጉዳዩን በአግባቡ እየመራው ነውን የሚለውን በተመለከተ ባለሙያ ጠይቀናል።ለታላቁ የህዳሴ ግድብ የደን ምንጣሮ 4 ወራት የተሻገረው የክፍያ ጥበቃ
የአዲስ አበባው ድርድር ውጤት አልባ ነው መባሉ
ለሁለት ዓመታት ተቋርጦ የቆየው የሕዳሴ ግድብ የሦስትዮሽ ድርድር በውኃ ሙሌት እና አለቃቀቅ ዙሪያ አተኩሮ ግብጽ ካይሮ ላይ በቅርቡ ተደርጎ፣ ያለፈው ሳምንት የመጨረሻ ቀናት ደግሞ አዲስ አበባ ላይ ቀጥሏል። በዚህ መሃል የግድቡ የመጀመርያ ዙር አራተኛ ሙሌት መከናወኑን ኢትዮጵያ ስታስታውቅ ግብጽ ጉዳዩን ለመቃወም ጊዜ አልፈጀባትም። በሦስትዮሽ ድርድሩ በግድቡ የውኃ ሙሌት እና በሚለቀቀው መጠን ሕጋዊ ብቻ ሳይሆን አስገዳጅ ጭምር ስምምነት እንዲፈረም የግብፅ ፍላጎት ነው። ኢትዮጵያ በበኩሏ ይህንን በተመለከተ ለአሳሪ ስምምነት ፈቃደኛ አልሆነችም።
ይህንን በተመለከተ አስተያየታቸውን እንጂ ስማቸውን እንዳንጠቅስ የጠየቁ አንድ የአለም አቀፍ ሕግ እና የዲፕሎማሲ ጉዳዮች ተንታኝ ፍትሐዊ ጥያቄ የያዘው ሀገር ማን ነው የሚለው እንዳለ ሆኖ ኢትዮያም ሆነች ግብጽ ዘላቂ ሀገራዊ ጥቅማቸውን ላለማስነካት በሚያደርጉት ክርክር ድርድራቸው ስምምነት ሲጎድለው ይታያል ብለዋል።የህዳሴ ግድብ አራተኛ ዙር የውኃ ሙሌት ተጠናቋል መባሉ እና አንደምታዉ
የድርድሩ ቁልፍ ጉዳዮች ምንድን ናቸው ?
በግድቡ የውኃ ሙሌት እና አለቃቀቅ ደንቦች እንዲሁም መመሪያዎች ዙሪያ ድርድሩ አዲስ አበባ ላይ መጀመሩን የገለፀው የኢትዮጵያ መንግሥት የድርድሩ ውጤት ወይም መቋጫ ምን እንደሆነ አልገለፀም። የግድብ ዋና ተደራዳሪ አምባሳደር ስለሺ በቀለ "ኢትዮጵያ የጋራ መፍትሔ ላይ ለመድረስ በበጎ መንፈስ ትሰራለች" ሲሉ በትዊተር ጽፈዋል። በውይይቱ መክፈቻ እለትም "በመርሆዎች መግለጫው በተቀመጠው መሰረት በዓባይ ውኃ አጠቃቀም ፍትሐዊ እና ምክንያታዊ አጠቃቀም መርህን ማስፈን ብቸኛው አማራጭ ነው" ማለታቸው ተገልጾ ነበር። በአፍሪካ ሕብረት በአደራዳሪነት ተይዞ የቆየው ይህ ግድብ በተለይ በግብጽ በኩል ፓለቲካዊ ጫና ተደርጎበት ወደ አረብ ሊግ እና ምዕራቡ አለም መወሰዱ ሕብረቱ እንደ የፖለቲካ ማሕበርነቱ በአግባቡ ሚናውን የተወጣ አይደለም ለሚል ወቀሳ ተዳርጓል።ታላቁ የህዳሴ ግድብ አገልግሎት መጀመርና ቀጣዩ ዲፕሎማሲ
የደህንነት መልክ የተሰጠው ግድብ
በግድብ ግንባታ ታሪክ ውስጥ ትልቅ የፖለቲካ ፣ የደህንነት እና የአለም አቀፍ ጫና ምክንያት እንዲሆን የተደረገ ግድብ ቢኖር ይህ የሕዳሴ ግድብ ስለመሆኑም በባለሙያዎች ዘንድ ይነገራል። ግንባታው በኢትዮጵያ በኩል በውኃ ሚኒስቴር የሚመራ እና የቴክኒክ ጉዳይ ተደርጎ የሚታይ ሲሆን በግብጽ በኩል ግን ከፍተኛ የደህንነት እና የፀጥታ ጉዳይ ተደርጎ የተያዘ ብሎም ጉዳዩ በሀገሪቱ የደህንነት መሥሪያ ቤት ቀጥታ የሚመራ መሆኑ ማሳያ ተደርጎ ይጠቀሳል። ዶቼ ቬለ የግድቡን ተደራዳሪዎች ለማካተት ያደረገው ጥረት ለጊዜው አልተሳካም። ግብጽ የመደራደር እና ሀብቱን በእኩልነት የምጠቀም ፍላጎት እንደሌላት ግን ተደጋግሞ ይነገራል።
ሰለሞን ሙጬ
አዜብ ታደሰ
ዮኃንስ ገብረግዚአብሔር