1. Inhalt
  2. Navigation
  3. Weitere Inhalte
  4. Metanavigation
  5. Suche
  6. Choose from 30 Languages
ማስታወቂያ
ማስታወቂያ
ማስታወቂያ

ዜና | 27.05.2023 | 22:00

ዋሽንግተን፤ አሜሪካ በሶማሊያ የአልሸባብ ይዞታ ላይ የአየር ጥቃት ሰነዘረች

አሜሪካ በሶማሊያ የአልሸባብ ይዞታ ላይ የአየር ጥቃት ሰነዘረች። አሜሪካ በትናንት ቅዳሜው የአየር ጥቃት ታጣቂ ቡድኑ ከአፍሪቃ ህብረት የሰላም አስከባሪ የጦር ሰፈር አቅራቢያ የዘረፋቸውን የጦር መሳሪያዎች ማውደማቸውን የአሜሪካ አፍሪቃ የጋራ ወታደራዊ ዕዝ ዐስታውቋል። ነገር ግን ዕዙ በታጣቂ ቡድን ተወሰዱ የተባሉ የጦር መሳሪያዎች አይነት እና ብዛት እንዲሁም መቼ ስለመወሰዳቸው በዝርዝር ያለው ነገር የለም። የአየር ጥቃቱ ከሶማሊያ የፌዴራል ጦር እና የአፍሪቃ ሕብረት የሰላም አስከባሪ ኃይል ጋር በመጣመር ባለፈው ዓርብ ቡሎ ማሬር በተሰኘች መንደር መፈጸሙን የጋራ ዕዙ በመግለጫው አመልክቷል። ከመዲናዋ ሞቃዲሾ 120 ኪሎ ሜትሮች ርቃ በምትገኘው መንደሯ የአፍሪቃ ህብረት ሰላም አስከባሪ ኃይል ውስጥ የታቀፉ ዩጋንዳውያን ወታደሮች የጦር ሰፈር የሚገኝበት ሲሆን ባለፈው ዓርብ አልሸባብ ድንገት በፈጸመው ጥቃት ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ የህብረቱ ወታደሮች መገደላቸውን ተዘግቧል። የአልሸባብ ታጣቂ ቡድን በተሽከርካሪ ላይ በተጠመደ ቦምብ በማፈንዳት እንዲሁም ድንገተኛ የእሩምታ ተኩስ በመክፈት ጥቃቱን መፈጸሙን የአካባቢውን ነዋሪዎች እና የሶማሊያ ወታደራዊ አዛዦችን ጠቅሶ የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል። በሶማሊያ ከኢትዮጵያ ፣ ኬንያ ፣ ጂቡቲ ፣ ዩጋንዳ እና ቡሩንዲ የተውጣጡ ከ20 ሺ በላይ የህብረቱ የሰላም አስከባሪ ኃይሎች ተሰማርተው ይገኛሉ።

ካምፓላ፤ በሶማሊያው ጥቃት ወታደሮቿ መገደላቸውን ዩጋንዳ አረጋገጠች

የሶማሊያው ታጣቂ ቡድን አልሸባብ ባለፈው ዓርብ ፈጽሞት በነበረው ጥቃት ወታደሮቿ መገደላቸውን ዩጋንዳ አስታውቃለች። የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ትናንት እንዳሉት ታጣቂ ቡድኑ በአፍሪቃ ህብረት ይዞታ ላይ ጥቃት መሰንዘሩን ተከትሎ የዩጋንዳ ሰላም አስከባሪ ወታደሮች መገደላቸው ተረጋግጧል። ነገር ግን ፕሬዚዳንቱ በጥቃቱ ምን ያህል ዩጋንዳውያን ወታደሮች ስለመገደላቸውም ሆነ ስለ ደረሰ ጉዳት በዝርዝር አልገለጹም። «በጥቃቱ ለተገደሉት ቤተሰቦች እና ለመላው ሀገሪቱ መጽናናት እመኛለሁ » ያሉት ሙሴቬኒ በወታደሮቻቸው ላይ ስለተፈጸመው የጥቃት ሁኔታ የሚያጣራ ቡድን ማቋቋማቸውን ገልጸዋል። ዩጋንዳውያን የሰላም አስከባሪ ወታደሮች ሰፍረውበት በነበረ የጦር ሰፈር ላይ ጥቃት ያደረሱት የአልሸባብ ታጣቂዎች ከ800 በላይ እንደሚሆኑ እና በወቅቱ ዩጋንዳውያን ወታደሮች የጦር ሰፈሩን ለቀው ለመውጣት መገደዳቸውን ሮይተርስ የዜና ምንጭ አትቷል። አልሸባብ በዕለቱ ባወጣው መግለጫ በተሽከርካሪ ላይ በተጠመደ ቦምብ ባደረሰው ጥቃት በጦር ሰፈሩ የነበሩ 137 ወታደሮች መገደላቸውን አመልክቶ ነበር። ስለደረሰው ጉዳት ግን ከሶማሊያ መንግስትም ሆነ ከአፍሪቃ ህብረት የሰላም አስከባሪ ኃይል ማረጋገጫ አልተሰጠበትም ። የሶማሊያ የሰላም አስከባሪ ኃይል ተልዕኮ ከጎርጎርሳውያኑ 2007 ጀምሮ ገቢራዊ ሲደረግ ማዕከላዊ መንግስትን ከታጣቂዎች መከላከልን ዓላማው አድርጎ ነበር ።

ዱባይ፤ ሁለቱ የሱዳን ተፋላሚ ኃይሎች የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያራዝሙ ተጠየቁ

ዩናይትድስቴትስ እና ሳኡዲ አረቢያ ሁለቱ የሱዳን ተፋላሚ ኃይሎች ነገ የሚያበቃውን የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያራዝሙ ጠየቁ። የሱዳን ብሔራዊ ጦር እና አር ኤስ ኤፍ የተሰኘው ልዩ ኃይል የሰላም ንግግራቸውን እንዲገፉበትም ሁለቱ ሃገራት በጋራ ባወጡት መግለጫ አሳስበዋል። ሁለቱ ተፋላሚዎች ከአንድ ወር በላይ ያስቆጠረውን ደም አፋሳሽ ጦርነት በሳዑዲ አረቢያ እና ዩናይትድ ስቴትስ አሸማጋይነት የተኩስ አቁም ለማድረግ ባለፈው ሳምንት ነበር ከስምምነት የደረሱት ። ነገር ግን ስምምነቱ ከተደረሰ በኋላም ቢሆን መዲናዋ ካርቱምን ጨምሮ በአንዳንድ ከተሞች ግጭቶች ቀጥለው እንደነበር ነዋሪዎችን ዋቢ አድርገው ከየአካባቢው ይወጡ የነበሩ ዘገባዎች ያመለክታሉ። የተኩስ አቁም ስምምነቱ በሀገሩው ሰዓት አቆጣጠር ነገ ምሽት 3 ሰዓት ከ45 ደቂቃ ላይ ይጠናቀቃል። ምንም እንኳ የተኩስ አቁም ስምምነቱ ከገቢራዊነቱ አንጻር ፍጹማዊ ባይሆንም «ለሱዳናውያን የሰብአዊ ረድኤት ለማድረስ አይነተኛ ሚና አለው » ሲል የሁለት ሃገራት የጋራ መግለጫ አመልክቷል። ስድስት ሳምንታት ባስቆጠረው የሱዳኑ የእርስ በእርስ ጦርነት ከአንድ ሺ በላይ ሰዎች ሲገደሉ ፤ ሌሎች በሺዎች የሚቀጠሩ ቆስለዋል ፤ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል።

አንካራ ፤ ሁለተኛው ዙር ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዛሬ ድምጽ ሲሰጥ ዋለ፤ ጥቃትም ተፈጽሟል

በቱርክ ሁለተኛው ዙር ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዛሬ ድምጽ ሲሰጥ ውሎ አሁን ቆጠራ ተጀምሯል። ውጤቱ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ይፋ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል። በዛሬው የድምጽ አሰጣጥ በኢስታንቡል እና በደቡባዊ ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍል አንድ የምርጫ ጣቢያ ላይ በደረሰ ጥቃት ጉዳት መድረሱም ተሰምቷል። በንግድ ከተማዋ ኢስታምቡል የሪፐብሊካን ህዝባዊ ፓርቲ አባል የሆኑት የህግ አውጭው አባል አሊ ሴከር በድምጽ አሰጣጥ ወቅት ያልተለመደ እንቅስቃሴ መመልከታቸውን ካመለከቱ በኋላ «በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች ጥቃት አድርሰውብናል» ሲሉ ለሀገር ውስጥ የመገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል። ከዚህኛው ጥቃት አስቀድሞ በደቡባዊ ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍል በሚገኝ አንድ የምርጫ ጣቢያ በታዛቢዎች ላይ ድብደባ መፈጸሙ እና የእጅ ስልኮቻቸው መሰባበሩን የፓርላማ አባል የሆኑት ኦዝጉል ኦዚል በትዊተር ጽፈዋል። የምርጫ ውጤቱ በፍጥነት ይፋ ይደረጋል ተብሎም እየተጠበቀ ነው። ከሁለት ሳምንት በፊት ተደርጎ በነበረው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ከሁለት አስርት አመታት በላይ ቱርክን በፕሬዚዳንትነት የመሩት ጣይብ ኤርዶሃን እና ተፎካካሪያቸው አሕሜት ክሊግዳሮግሉ ከ50 ሲደመር አንድ በመቶ በላይ አብላጫ ድምጽ ማግኘት አለመቻላቸውን ተከትሎ ምርጫው ወደ ሁለተኛ ዙር እንዲሻገር አስገድዷል። በመጀመሪያው ዙር ኤርዶሃን የ49,52 ድምጽ ማግኘት ሲችሉ ተቀናቃኛቸው ክሊግዳሮግሉ 44,88 በመቶ ድምጽ አግኝተዋል። በወቅቱ በምርጫው ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃ አግኝተው የነበሩት ሁለቱ ዕጩዎች ሁለቱን ተቀናቃኞች ወደ መደገፋቸውን አስቀድመው አስታውቀዋል። በመጀመሪያው ዙር ምርጫ 5,17 በመቶ ድምጽ ያገኙት ብሔርተኛው ሲናን ኦጋን ለኤርዶሃን አጋርነታቸውን መግለጻቸው በዛሬው የምርጫ ውጤት ላይ ልዩነት ሳያስከትል እንደማይቀርም የቅድመ ውጤት ትንበያዎች አመልክተዋል።

ሩስያ በዩክሬን ላይ መጠነ ሰፊ የአየር ጥቃት ፈጸመች

ሩስያ በዩክሬን ላይ ወረራ ከፈጸመችበት ጊዜ አንስቶ ብርቱ ነው የተባለ የአየር ጥቃት በመዲናዋ ኪቭ ላይ መፈጸሟን ወታደራዊ ባለስልጣናቷ ዐስታወቁ። በጥቃቱ ሁለት ሰዎች ሲገደሉ ሌሎች ሶስት ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል። ከትናንት ቅዳሜ ምሽት ጀምሮ ሩስያ ከሰነዘረቻቸው 54 የድሮን ጥቃቶች አርባዎቹ በኪዬቭ ላይ ያነጣጠሩ ነበር ተብሏል። «ክብረ ወሰን የያዘ በተባለው የድሮን ጥቃት በጠቅላላው 54 ጥቃቶች ተመዝግበዋል» ሲል የዩክሬን አየር ኃይል በቴሌግራም ገጹ ላይ አስነብቧል። የዩክሬን አየር ኃይል «የመጀመሪያ ደረጃ» ባለው ሪፖርት ደግሞ የዩክሬን የአየር መቃወሚያ ስረዓት ከ40 በላይ የሩስያ ድሮኖችን ማውደሙን ገልጿል። ድሮኖቹ ከተመቱ በኋላ ስብርባሪዎቹ በሰላማዊ ሰዎች መኖሪያ ቤቶች ላይ በመውደቃቸው አንድ ሰው ሲሞት በሌላ አንድ ሰው ላይ ደግሞ ጉዳት አድርሰዋል። ሩስያ በኪዬቭ ላይ በአንድ ወር ውስጥ ብቻ ለአስራ አራተኛ ጊዜ የአየር ጥቃት መሰንዘሯን የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል። ሞስኮ በአየር ጥቃቱ በማዕከላዊ የሀገሪቱ ክፍል በሚገኙ ወሳኝ ናቸው በተባሉ የመሰረተ ልማቶችን ጨምሮ በተለይ የኪዬቭ ግዛትን ኢላማ ማድረጓን ዘገባው አመልክቷል።