ከአካባቢ ምርጫ በፊት የሕዝብ ቆጠራ እንዲካሄድ መጠየቁ
ሰኞ፣ ሰኔ 13 2014ማስታወቂያ
በቀጣዩ ዐመት እንደሚደረግ ከሚጠበቀው የአካባቢ ምርጫ አስቀድሞ በተደጋጋሚ የተራዘመው የሕዝብና ቤት ቆጠራ እንዲከናወን ተጠየቀ። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ምርጫው ከመደረጉ በፊት የሕዝብ እና ቤት ቆጠራው መካሃድ እንዳለበት አቋም መያዙን ተናግሯል።
የምክር ቤቱ ሰብሳቢ ዶክተር ራሄል ባፌ ባለፉት ዐመታት « ካድሬዎች ይሾማሉ በዚያ መንገድ ሕዝቡ ሲተዳደር ነበር። አሁን ሕዝብ በራሱ እንደራሴ መተዳደር ስላለበት በሥራው መሳተፍ እንዳለብን ታምኗል» ብለዋል። የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ መሪ በበኩላቸው አምስት ዐመት ሙሉ ሥራቸው ምርጫ እና ለምርጫ የሚበቁ ሰዎችን ማዘጋጀት መሆኑን ገልፀው «አሁን ካለው የአገሪተ ነባራዊ ሁኔታ አንፃር ለመራጭም ለተመራጭም ብዙ ተስፋ ሰጪ አይደለም» በማለት የሰላምና ፀጥታ ችግሮች የሂደቱ እንቅፋት እንደሚሆኑ ጠቅሰዋል።
ለሦስት ጊዜ የተራዘመው የኢትዮጵያ ሕዝብና ቤቶች ቆጠራ በዚህ ዐመት ይደረጋል ተብሎ ተነግሮ የነበረ ቢሆንም እስካሁን አልተከናወነም። ይህም በበጀት ድልድልም ሆነ በምርጫ ሂደትና ውጤቱ ሊያስገኘው ከሚጠበቀው ጥቅም አንፃር አሉታዊ ተጽእኖ የሚያሳርፍ ስለመሆኑ ይነገራል።
ሰሎሞን ሙጬ
ሸዋዬ ለገሠ
ነጋሽ መሐመድ