ኢትዮጵያዊ ሐኪም በጀርመን
ማክሰኞ፣ መጋቢት 10 2005ጀርመን ተምረው ጀርመን የሚሰሩና የሚኖሩ ሐኪም ናቸው ። ከመደበኛው የህክምና ትምህርት በተጨማሪ ልዩ ሥልጠና በመውሰድ በተካኑባቸው ከ 5 በላይ በሚሆኑ የህክምና ዘርፎች ያገለግላሉ ።
ወደ 30 አመት ለሚጠጋ ጊዜ ጀርመን ውስጥ በሀኪምነት ሰርተዋል ። ለ 15 አመታት በሆስፒታል ፣ ከዚያም ለ12 አመታት በግል ክሊኒካቸው ከዛሬ ሁለት አመት ወዲህ ደግሞ እንደገና ወደ ሆስፒታል ተመልሰው እየሰሩ ነው ።
እንግዳችን ዶክተር ንጉሴ በቀለ ህክምና ከልጅነታቸው አንስቶ የሚመኙት ሞያ ነበር ።
ፍላጎታቸውን ለማሳካትም ከፍተኛ ውጤት አምጥተው በገቡበት በቀድሞው አጠራሩ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ ከዚያም ቀደም ሲል ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በተከታተሉበት በአዲስ አበባው ሽመልስ ሃብቴ ትምህርት ቤት የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪ ነበሩ ። ሆኖም ህክምና ለማጥናት´
አቅደው የዛሬ 41 አመት በገቡበት በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ አልቆዩም ። በወቅቱ በነበረው የተማሪዎች ንቅናቄ ምክንያት የመጀመሪያ አመት ትምህርታቸውን አቋርጠው ከሃገር ወጡ ። የሄዱትም እስራኤል ነበር ።
እስራኤልን እንደጠበቁት ስላላገኙት ጀርመን መጡ ። የዛሬ 39 አመት በመጡባት በጀርመን የልጅነት ምኞታቸውን ለማሳካት ያደረጉት ጥረት ሰመረላቸው ። የጀርመንኛ ቋንቋ ተምረው ህክምና ለማጥናት የሚያስፈልገውን የመመዘኛ ፈተና ካለፉ በኋላ በምዕራብ ጀርመኗ ዱስልዶርፍ ከተማ ህክምና ማጥናት ጀመሩ ። ከአንድ ሴሚስተር በኋላ በተዛወሩበት በኮሎኝ ዩኒቨርስቲ እጎአ በ 1984 የህክምና ትምህርታቸውን አጠናቀቁ ። ከመደበኛው የህክምና ትምህርት በተጨማሪ ከ 5 በላይ በሚሆኑ የህክምና ዘርፎችም ልዩ ሥልጠና ወስደዋል ።
ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ሥራ የጀመሩት በተማሩበት ከተማ ነበር ።
ዶክተር ንጉሴ ከ 15 አመታት የሆስፒታል ልምድ በኋላ የራሳቸውን ክሊኒክ ከፈቱ ።
ዜጎችና ነዋሪዎች የጤና ዋስትና በሚያገኙባት በጀርመን የሚሰጠው ህክምና ከሌሎች አገራት ጋር ሲነፃጸር ደረጃው ከፍተኛ መሆኑን ነው የሚናገሩት ። የካበተ የህክምና ልምድ ያላቸው ዶክተር ንጉሴ እዚህ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ይህን እድል በአግባቡ እንዲጠቀሙበትም ይመክራሉ ።
ድምፅ ዶክተር ንጉሴ የተለያዪ የጀርመን የህክምና ማህበራት አባል ናቸው ከመካከላቸው የጀርመን አጠቃላይ ሐኪሞች የአጥንትና የመገጣጠሚያ አካላት ሀኪሞች እንዲሁም የስፖርት ህክምና ማህበር ይገኙበታል ። ዶክተር ንጉሴ ባለትዳርና ከመጀመሪያዋ ጀርመናዊት ባለቤታቸው የወለዷቸው የ4 ልጆች አባት ናቸው ።
የአሁኗ ባለቤታቸው ደግሞ ኢትዮጵያ ነው ያሉት ። ወደፊት ጡረታ ሲወጡ ኢትዮጵያ ገብተው ወገናቸውን በሙያቸው የማገልገል እቅድ አላቸው .
ሂሩት መለሰ
ተክሌ የኋላ