" አንድ ሆነን እንነሳ ነገንም እንገንባ "
ረቡዕ፣ ጥቅምት 21 2011በዝግጅቱ ላይ ወደ 25 ጥያቄዎች ለጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር ዐብይ እንደሚያቀርብ ይጠበቃል። ለወደፊት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ጉዞ ወሳኝ የሆኑና በአዉሮጳ ዉስጥ የሚኖሩ በርካታ ኢትዮጵያዉያን ምሁራን እና የፖለቲካ አዋቂዎች በአዉሮጳ በመኖራቸዉ ተነግሮአል። ይሁንና ከጠቅላይ ሚንስትሩ ጋር ፊት ለፊት መወያየት ባለመቻላቸዉ ብዙዎችን አስኮርፎአል። የፓሪስ ፈረንሳይና የበርሊን ጀርመን ጉብኝት በዋናነት በሁለት አገሮች የሚደረግ መንግስታዊ ጉዳይ መሆኑን የፍራንክፉርት ጉብኝት አስተባባሪ ድያቆን ዳንኤል ክብረት ለDW ተናግረዋል። ይሁን እንጅ በነገ እለት በፍራንክፉርት ከኢትዮጵያዉያንና ትዉልድ ኢትዮጵያዊያን ጋር ለመገናኘት ተጨማሪ ቀን መያዙን ድያቆን ዳንኤል ገልፀዋል።
በነገዉ ሥነ-ስረዓት ላይ ታዳሚዎች ምን ማድረግ እንዳለባቸዉም እንደ ማሳሳብያ የሚከተሉትን ነጥቦች ዝርዝረዋል፤
- የፍተሻዉን ጊዜ በጣም ለማሳጠር ትልልቅ ሻንጣዎችን ይዞ ከመምጣት ታዳሚዎች መቆጠብ ይኖርባቸዋል።
- ቀጠሮዉን አክብሮ በግዜ መገኘት አስፈላጊ ነዉ።
- ሕጻናትና ልጆችን የያዙ ቤተሴቦች የሕጻናት መቀመጫ ጋሪዎቻቸዉን የሚያስቀምጡበት ቦታ ተዘጋጅቶአል። ቦታዉ ግን ይህን ያህል ብዙ አልያም ሰፊ አለመሆኑም ተመልክቶአል።
- ከሕፃናት ምግብ በስተቀር ምግብ ይዞ ወደ ስታድዮም መግባት አይቻልም። በአንጻሩ ምግብ መጠጥ መሸጫ ቦታ በቂ ተዘጋጅቶአል።
በነገው የፍራንክፈርት የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዓብይ የአቀባበል ሥነ-ሥር ዓት ላይ ከሚገመተው በላይ በአስር ሺዎች የሚቆጥሩ ኢትዮጵያውያን ከመላው አዉሮጳ እንደሚታደሙ ለማወቅ ተችሏል። በዚህ መድረክ ታዳሚዎች ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚያቀርቧቸውን ጥያቄዎች ጨምሮ ልዩ ልዩ ቀስቃሽ እና አዝናኝ ዝግጅቶችም እንደሚኖሩ አስተባባሪዎቹ ገልጸውልናል። በመኪና ከተለያዩ የአዉሮጳ ከተሞች የሚመጡ እንግዶች እንዳይቸገሩም ከ 10 ሺህ በላይ የመኪና ማቆሚያ ስፍራዎች የተዘጋጁ ሲሆን እዛው ጀርመን የተወለዱ እና ያደጉ ከ 200 በላይ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶችም በራሳቸው አነሳሽነት ከፍራንክፈርት አውሮፕላን ማረፊያ ጀምሮ ወደ ስታዲየሙ አቅጣጫ የሚያመሩ የአውቶቡስ እና የባቡር መስመሮችን ለዝግጅቱ ታዳሚዎች በመጠቆም የበኩላችውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ታውቋል። መስማት ለተሳናቸው ወገኖችም የዝግጅቱን ሂደት በምልክት ቋንቋ የሚያብራሩ አስተርጓሚዎች ተመድበዋል። አቶ ዘለዓለም ደበበ የኮሚቴው የሚድያ እና ሕዝብ ግንኙነት አስተባባሪ አጠቃላይ ለነገው ዝግጅት በጀርመን ነዋሪ የሆኑ ኢትዮጵያውያን እንግዶቻቸውን በክብር ለመቀበል ከፍተኛ ርብርብ እያደረጉ መሆናቸውን ነው የነገሩን።
በመላው አዉሮጳ ነዋሪ የሆኑ ኢትዮጵያውያን በአገሪቱ ለተጀመረው ሁለንትናዊ ለለውጡ ያላቸውን አጋርነት በነቂስ ወተው እንዲያሳዩ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ እና የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዓብይ አህመድ አቀባበል ዓብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ ጥሪ አቅርበዋል።
በአዉሮጳ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ታሪክ የመጀመሪያ ይሆናል በተባለው እና የልዩነት እንዲሁም የጥላቻው ግንብ ፈርሶ በፍቅር እና በአንድነት የለውጥ ስሜት በዲያስፖራ የሚኖሩ ወገኖች በሚሰባሰበቡት ታላቅ ሕዝባዊ ጉባኤ ከ25ሺ በላይ ከመላው አዉሮጳ የተውጣጡ ኢትየጵያውያን ከጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ጋር በመወያየት በሀገራቸው የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እና ሁለንተናዊ ልማት ላይ በሚሳተፉበት መንገድ ላይ እንደሚመክሩ ታውቋል።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ