1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በዩክሬይን መፍቀሬ ሩሲያ የሠዓት ዕላፊ ገደብ

እሑድ፣ ሚያዝያ 12 2006

በምሥራቅ ዩክሬይን መፍቀሬ ሩሲያውያን ኃይላት በስሎቭያንስክ የሠዓት ዕላፊ ገደብ አወጁ። በአዋጁ መሰረት ማንኛውም ሰው የሠዓት ዕላፊው ገደብ ሳይጠናቀቅ ወደ ውጭ ወጥቶ መንቀሳቀስ አይፈቀድለትም።

https://p.dw.com/p/1BlQr
ምስል Reuters

ከዕኩለ ሌሊት እስከ ንጋቱ 12 ሰዓት ድረስ ማንኛውም ሰው ውጪ መገኘት አይፈቀድለትም ያሉት የመፍቀሬ ሩሲያ ኃይላት የተቆጣጠሩዋቸው ቦታዎች ከንቲባ መሆናቸውን የገለጹት ቭያቼስላቭ ፖኖማሬቭ ናቸው። ከዚህ በተጨማሪ ፖኖማሬቭ «ፋሺስት» ያሏቸውን መከላከል እንዲችሉ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ሰላም አስከባሪ ኃይል ወደ ምሥራቅ ዩክሬይን እንዲልኩላቸው ጥሪ አድርገዋል። ይህ ከመሰማቱ ትንሽ አስቀድሞ እንደ ሩሲያ የመንግስት ቴሌቪዥን ጣቢያ ዘገባ ከሆነ በስሎቭያንስክ -ዶኔስክ አካባቢ «የቀኝ አክራሪ» ታጣቂዎች አምስት ሰዎች ገድለዋል። ከመዲና ኪዬቭ የሀገር ውስጥ ሚኒስቴር እንደተሰማው ደግሞ በሁለት ቡድኖች መካከል በተነሳ ግጭት አንድ ሰው ሲሞት ሌሎች ሦስት ሰዎች ቆስለዋል። የትንሣኤ በዓል በመሆኑ የሀገሪቱ መንግሥት ርምጃ ላለመውሰድ ከትናንት በስትያ ቃል ገብቶ የነበረ ቢሆንም ግጭቱ የተቀሰቀሰ ሊቀሰቀስ ችሏል።

በዓሉን አስመልክቶ የዩክሬይን መንግሥት ሕንፃዎችን የተቆጣጠሩት መፍቀሬ ሩስያውያን ላይ ርምጃ እንደማይወስድ ገልጦ ነበር። መፍቀሬ ሩስያውያኑ ዩክሬይንን የተቆጣጠረውን አዲስ መንግሥት ለአውሮጳ ስጋት የሚሆን የቀኝ አክራሪዎች ስብስብ ሲሉ በተደጋጋሚ መወንጀላቸው ይታወቃል። የኪዬቭ የሀገር ውስጥ ሚንስትር የትንሣኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ አሁን በምሥራቅም ሆነ በምዕራብ ዩክሬይን የሚገኙ በሙሉ ለዕርቀ-ሠላምና ለአንድነት እንዲሰባሰቡ ጥሪ አድርገዋል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ልደት አበበ