1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኢትዮጵያ ኤቦላን የመከላከል ጥረትና የሕዝብ አስተያየት

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 27 2006

በያዝነዉ ዓመት የካቲት ወር በምዕራብ አፍሪቃ ጊኒ ከተከሰተ አንስቶ ወደተለያዩ የአካባቢዉ ሃገራት በመዛመት ከአንድ ሺህ አምስት መቶ በላይ ሰዎችን ህይወት መቅጠፉ የሚነገርለትን የኤቦላ ተኀዋሲ ለመከላከል የተለያዩ ሃገራት የየራሳቸዉን ጥረት እያደረጉ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1D5Wt
Ebola Seuche Afrika Helfer
ምስል D.Faget /AFP/Getty Images

ኤቦላ ካለፈዉ ሳምንት ወዲህ ምሥራቅ አፍሪቃ ኮንጎ ዉስጥ ተገኝቷል የገደላቸዉ ሰዎች ቁጥርም እየጨመረ ነዉ። የዓለም የጤና ድርጅት ዘገባ እንደሚለዉ ዴሞክራቲክ ኮንጎም ተቀስቅሶ የገደላቸዉ ወደ31 ደርሰዋል። የድርጅቱ የኮንጎ ወኪል እንደሚሉት የበሽታዉ ስርጭት ከዋና ከተማ ኪንሻሳ በስተሰሜን 800 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ አካባቢ የተወሰነ ነዉ። ከኮንጎ ሌላ፤ ከአራቱ የምዕራብ አፍሪቃ ሃገራት ጊኒ፣ ላይቤሪያ፣ ሴራሊዮን እና ናይጀሪያ ጎንም ሴኔጋል አሁን ተጨምራለች። እናም በሽታዉ በአፍሪቃ ስድስት ሃገራትን አዳርሷል።

የኤቦላ ተኀዋሲ ከዚህ ቀደም ሲከሰት ብዙም ነፍስ ሳይቀጥፍ በቶሎ በቁጥጥር ሥር ይዉል እንደነበር ነዉ መረጃዎች የሚያመለክቱት። የዘንድሮዉ ወረርሽኝ ግን በሰዉ ህይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ከማድረስ አልፎ በበሽታዉ የተጎዱ አካባቢዎችን ለኤኮኖሚ ቀዉስ ጭምር መዳረጉ ተገልጿል።

ከበሽታዉ ሊያድን ይችላል ተብሎ በሙከራ ላይ የሚገኝ አንድ መድኃኒት ተኀዋሲዉ እንዲይዛቸዉ በተደረጉ ዝንጀሮዎች ላይ ተሞክሮ መሥራቱን አንድ ጥናት አመልክቷል። አሁንም ግን ኤቦላ የሚገድላቸዉ ሰዎች ቁጥር መጨመሩ እየተነገረ ነዉ። ዛሬ ከሞኖሮቪያ የወጣ መግለጫ እንደሚያመለክተዉ ኤቦላ የኤኮኖሚና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አሳርፏል። በተለይ እንደላይቤሪያ ላሉ ገና ጦርነት ለማገገም በሚጥሩ ሃገራት ችግሩ ጉልበት አሽመድማጅ እንደሆነ ነዉ የተገለጸዉ። ወደምዕራብ አፍሪቃ ሃገራት በረራ መሰረዙም ሆነ ድንበሮችን መዝጋቱ ከአዎንታዊ ዉጤቱ አሉታዊዉ ማመዘኑም ተመልክቷል። ሕዝቡ የኤቦላ ተኀዋሲን እንዲከላከል በተላለፈዉ የአፍሪቃ መንግሥታትና ዓለም ዓቀፍ ተቋማት የተባበረ ርብርብ አስፈላጊ መሆኑ ተጠቅሷል። በዚህ ጥሪ ላይም ታዋቂ ማለትም የቀድሞዉ የታንዛኒያ ፕሬዝደንት ምካፓ፣ የቀድሞዉ የናይጀሪያ መሪ ኦባሳንጆ፤ የኔልሰን ማንዴላ ባለቤት ግራሺያ ማሼል፤ እንዲሁም ሱኔጋላዊዉ ዘፋኝ ዩሱንዱር ጭምር ፊርማቸዉን አኑረዋል። ጥሪያቸዉም የኤቦላ ተኃዋሲ ስርጭት የሚገታበት መንገድ እንዲጠናከር ነዉ። በሽታዉ ከተከሰተባቸዉ ቀጥሎ በርካታ ተጓዦችን የሚያስተናግዱ ሃገራትም የጥንቃቄ ርምጃዎችን መዉሰድ ከጀመሩ ሳምንታት ተቆጥረዋል። ከእነዚህም ግንባር ቀደሞቹ ኢትዮጵያና ኬንያ ናቸዉ።

Ebola Seuche Afrika Helfer
ምስል D.Faget /AFP/Getty Images

ኤቦላን ለመከላከል ኢትዮጵያ ዉስጥ በየአካባቢዉ ስለሚከናወኑ ተግባራት አስተያየታችሁን የላካችሁልን በርካቶች ናችሁ። ብዙዎቹ እንቅስቃሴዉ አላረካንም ቢሉም ተገቢዉ ሁሉ እየተደረገ መሆኑን ያመለከቱም ጥቂት አይባሉም።ኤቦላን ለመከላከል የሚደረጉ ጥረቶችን በሚመለከት የዕለቱ ጤናና አካባቢ ዝግጅት ከተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የአድማጮችን አስተያየት አካቷል።

ዝርዝሩን ከድምፅ መረጃዉ ያድምጡ

ሸዋዬ ለገሠ

አርያም ተክሌ