1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
የምግብ ዋስትናኢትዮጵያ

በኢትዮጵያ በሰብአዊ ቀውስ ለተጎዱ የአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት 80 ሚሊዮን ዶላር ርዳታ መደበ

ቅዳሜ፣ መጋቢት 7 2016

በኢትዮጵያ በሰብአዊ ቀውስ ለተጎዱ ዜጎች የአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የ80 ሚሊዮን ዶላር ተጨማሪ ርዳታ ይፋ አደረገ። በተመ መረጃ መሠረት በግጭት፣ የከባቢ አየር ለውጥ ተጽዕኖና የጸጥታ ችግር ሳቢያ 21 ሚሊዮን ኢትዮጵውያን ርዳታ ይፈልጋሉ። በአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የሰብአዊ ርዳታ ቢሮ አስተዳዳሪ ረዳት ሶናሊ ኮርዴ የተቸገሩ አካባቢዎችን ጎብኝተዋል

https://p.dw.com/p/4dnpw
በአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የሰብአዊ ርዳታ ቢሮ አስተዳዳሪ ረዳት ሶናሊ ኮርዴ
በአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የሰብአዊ ርዳታ ቢሮ አስተዳዳሪ ረዳት ሶናሊ ኮርዴ በትግራይ እና በአፋር ክልሎች የተቸገሩ አካባቢዎችን ጎብኝተዋል።ምስል Seyoum Getu/DW

በኢትዮጵያ በሰብአዊ ቀውስ ለተጎዱ የአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት 80 ሚሊዮን ዶላር ርዳታ መደበ

የአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID) ረዳት የቢሮ አስተዳዳሪ ሶናሊ ኮርዴ በአዲስ አበባ፣ ትግራይ እና አፋር ክልሎች አደረኩ ባሉት የውስን ቀናት ቆይታ አሜሪካ የኢትዮጵያ ህዝብን ለመርዳት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጥ ነው ሲሉ ነው መግለጫቸውን የጀመሩት፡፡ ጉብኝታቸው በመላው አገሪቱ የሚስተዋሉትን የአስቸኳይ ምግብ እርዳታን ለማዳረስ ያለመ እንደሆነም ነው የጠቆሙት፡፡ 

ከዚህ በፊት የአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID) ከሌሎች ዓለማቀፍ ረጂ ድርጅቶች ጋር በመሆን በኢትዮጵያ አጋጥሟል የተባለውን የእርዳታ ምግብን ላልተገባ ዓለማ የማዋል ተግባርን በመኮነን ድጋፉን መግታቱ ይታወሳል፡፡

 ድርቅ በአፋር ክልል ያስከተለው አደጋ

ይሁንና ከባለፈው ጎርጎሳውያን ዓመት 2023 መጨረሻ ወዲህ የእርዳተው ዳግም መጀመርን ተከትሎ ዩናይትድ ስቴትስ ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን በባለፈው ጥር ወር ብቻ 2.4 ሚሊየን ኢትዮጵያውያንን ተደራሽ ያደረገ ድጋፍ ማድረጓ ነው የተገለጸው፡፡ የአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID) ረዳት የቢሮ አስተዳዳሪ ሶናሊ ኮርዴ በአሁኑ ጉብኝታቸውም ይህንኑን የእርዳታ ተደራሽነት ማሳለጥ ላይ ያተኮረ ጉብኝት ስለማድረጋቸው ነው በዛሬው መገለጫቸው ያመለከቱት፡፡ 

የኃላፊዋ የአፋርና ትግራይ ክልሎች ጉብኝት

“በአፋር በነበረኝ ቆይታ በበራህሌ ወረዳ ያለውን የምግብ ማከፋፈያ ማዕከል ጎብኝቻለሁ፡፡ በዚያ የአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID)፣ የዓለም ምግብ ፕሮግራም (WFP) እና ማህበረሰቡ ቅድሚያ ልንሰጣቸው የምንፈልገውን ለከፋ ጉዳት የተዳረጉትን ሰዎች በትብብር የመለየት ተግባር እያከናወኑ ነው፡፡ በዚህም በያንዳንዱ አባወራ የልየታ ስራ ተከናውኖ እርዳታው በትክክል ለተቸገሩት እንደሚደርስ ተመልክቻለሁ” ነው ያሉት፡፡

በአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የሰብአዊ ርዳታ ቢሮ አስተዳዳሪ ረዳት ሶናሊ ኮርዴ እና በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ
አሜሪካ በኢትዮጵያ ለተቸገሩ ተጨማሪ 80 ሚሊዮን ዶላር መመደቧን በአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የሰብአዊ ርዳታ ቢሮ አስተዳዳሪ ረዳት ሶናሊ ኮርዴ እና በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ዛሬ ቅዳሜ በአዲስ አበባ ይፋ አድርገዋል። ምስል Seyoum Getu/DW

ኃላፊዋ ጉብኝታቸውን ያደረጉበት ሌላው ክልል ትግራይ ነው፡፡ በዚህ ክልል በተለይም በጦርነት እና ድርቅ እጅግ የተጎዳውን አቤርጌሌ አከባቢ መጎብኘታቸውን ጠቅሰው፤ ረጂ ተቋማት ከታህሳስ ወር ወዲህ በዚህ አከባቢ ለአራተኛ ዙር የምግብ እርዳታ ማከፋፈል መፈጸማቸውን እንዳረጋገጡ አስረድተዋል፡፡ “እንዲሁም በትግራይ ህጻናትን እና እናቶችን የሚረዱ ሆስፒታሎችን ጎብኝቻለሁ፡፡

ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ በአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID) እና ጎል በዚህ በእጅጉ ለምግብ እጥረት ለተዳረጉ ከ3 ሺህ በላይ ሰዎች ድጋፍ ተደርጓል፡፡ በዚያና በመላው አገሪቱ ጀብዱ የሰሩትን የሰብዓዊ ድጋፍ ሰራተኞችን ማድነቅ እፈልጋለሁ፡፡ በተለይም እንደ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ያሉ ረጂ ድርጅቶች በእጅጉ ለአደጋ የተጋለጡትን ተደራሽ ለማድረግ የሚሰሩት ስራ እውቅና የሚሰጠው ነው” ብለዋል፡፡

ለረሃብ የተጋለጡ ህጻናት በትግራይ

ኃለፊዋ በጉብኝታቸው እጅግ አስከፊ ያሉት የድርቅ እና ግጭት ተጠቂዎችን መመልከታቸውንም አንስተዋል። “በጉብኝቴ ወቅት በአይኔ እና በልቦናዬ የተመለከትኩት ብኖር በእጅጉ የተጎዱና እርዳታ የሚሻቸውን ሰዎች በህብረተሰቡ ውስጥ መኖራቸውን ነው፡፡ እነዚህ ማህበረሰቦች ከዓመታት የግጭት ተጽእኖ ለመውጣት ጥረት በሚያደርጉብት ወቅት ያጋጠማቸው ድርቅ ደግሞ ለሌላ መከራ ዳርጎአቸው ተመልክቻለሁ፡፡ በመላው አገሪቱም ተመሳሳ ፍላጎቶች መኖራቸውን ከሰብኣዊ ድጋፍ ባለሙያዎች ብረዳም በአገሪቱ የተስፋፋው ግጭት እርዳተው የሚሻቸው ጋ መድረስን ከባድ ማድረጉን ተገንዝብዬያለሁ” ብለዋልም፡፡

ሰብአዊ ርዳ ሲከፋፈል
በተባበሩት መንግሥታት መረጃ መሠረት በጎርጎሮሳዊው 2024 በግጭት፣ የከባቢ አየር ለውጥ ተጽዕኖ እና የጸጥታ ችግር ሳቢያ 21 ሚሊዮን ኢትዮጵውያን ርዳታ ይፈልጋሉ።ምስል Ben Curtis/AP/picture alliance

የአሜሪካ ተጨማሪ ድጋፍ 

የአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID) ከሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር ከሚያደርጉት የእርዳታ አቅርቦት በተሻለ ድጋፉ ያስፈልጋል ያሉት ኃላፊዋ፤ ዛሬ ይፋ ያደረጉት የ80 ሚሊየን ዶላር ተጨማሪ እርዳታ ያስፈለገም ለዚሁ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ በዚህም የገንዘብ ድጋፍ ለአደጋ እጅግ ተጋላጭ የሆኑ የማህበረሰብ አካላትን እንደሚረዱ፣ ግብርና እና የስነምግብ ስራዎችም እንደሚደገፉ ተጠቁሟል፡፡ በድጋፉ ከ5 ዓመት በታች የሆኑ 1.5 ሚሊየን ህጻናት፣ ከ600 ሺህ በላይ በእርግዝና ላይ ያሉ እናቶች እና ህክምና የሚያሻቸው እናቶች እንደሚደገፉ ተብራርቷልም፡፡

የአሜሪካ ባለሥልጣናት የመቐለ ጉብኝትና ውይይት  

በተጨማሪም የአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID) በኢትዮጵያ 8 ክልሎች 4.5 ሚሊየን ህዝብ የእርዳታው ተደራሽ ለማድግ ወጥኖ እንደሚሰራም ነው የተነገረው፡፡ 

ግጭት፣ ድርቅ እና የጎርፍ አደጋዎች ደጋግሞ የሚጎበኟትን ኢትዮጵያ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎቿ ለከፋ ሰብዓዊ ድጋፍ ስለመዳረጋቸው የሰብአዊ ተቋማት ተደጋጋሚ መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡ የአሜሪካ ህዝብ ተራድኦ ድርጅት (USAID) ረዳት የቢሮ አስተዳዳሪ ሶናሊ ኮርዴ ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ መግለጫ ሲሰጡ አብሯቸው የተገኙት በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት ሰብዓዊ ቀውስ እየፈጠረ ያለውን ግጭት ለማርገብ አሜሪካ አበክራ ትሰራለች ነው ያሉት።

ሥዩም ጌቱ 
እሸቴ በቀለ