1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ሳይንስአፍሪቃ

ለካንሰር የሚያጋልጠው አደገኛ ኬሚካል በኢትዮጵያ 

ረቡዕ፣ ጥር 19 2013

«ዲዲቲ»  በመባል የሚጠራው ፀረ-ተባይ ኬሚካል  ለተባይ ማጥፊያ ውጤታማነቱ  የተረጋገጠ ቢሆንም፤ መርዛማነቱ በነፍሳት ብቻ የተወሰነ  ባለመሆኑ ጥቅምላይ እንዳይውል ከታገደ ከ50 ዓመታት በላይ ሆኖታል።ያም ሆኖ  በአንዳንድ ሀገራት በህጋዊም ይሁን  በሕገ-ወጥ መንገድ ጥቅም ላይ ይውላል ፡፡ከነዚህም መካከል ኢትዮጵያ አንዷ ነች። 

https://p.dw.com/p/3oTqK
Insektizid DDT gegen Malaria-Erreger versprüht
ምስል picture-alliance/dpa

ዲዲቲ ከፍተኛ የጤና ጠንቅ ያስከትላል

DDT ፤ወይም  /Dichlorodiphenyltrichloroethane/ ፤ በመባል የሚታወቀው  ሰው ሰራሽ  መርዛማ ንጥረ ነገር   የወባ ትንኝንና  የተለያዩ ሰብሎችን የሚያጠፉ ነፍሳትን  ለመከላከል ሲያገለግል ቆይቷል። ይህ ፀረ-ተባይ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሠራው በጎርጎሪያኑ 1874 ዓ/ም ሲሆን፤«ክሎሮቤንዚን»የተባለና በውስጡ «ሰልፈሪክ አሲድ» የያዘ  ንጥረ ነገርን ከሌላ  «ክሎራል» ከተባለ  ንጥረ ጋር በመቀየጥ የተዘጋጀ ነው።ይሁን እንጅ ይህ ውህድ የፀረ-ተባይነት ባህሪው የታወቀው  በጎርጎሪያኑ በ1939 ዓ/ም በስዊዘርላንዳዊው ኬሚስት ፖል ሄርማን ሙለር  አማካኝነት ነበር፡፡ ሆኖም በጎርጎሪያኑ ከ1960ዎቹ ጀምሮ በሰውና በእንስሳት እንዲሁም በአካባቢ ላይ በሚያመጣው የጎንዮሽ ጉዳት የተነሳ ግልጋሎቱ የተገደበ እንዲሆን ተደርጓል።ያም ሆኖ ኢትዮጵያን ጨምሮ በአንዳንድ  ሀገራት በህገ-ወጥ መንገድ አሁንም ድረስ ጥቅም ላይ ይውላል። 

ባለሙያዎቹ እንደሚሉት ዲቲቲ «ኦርጋኖክሎራይድ» በመባል ከሚጠራው የተባይ ማጥፊያ ክፍል የሚመደብና በቤተ ሙከራ ውስጥ የተሰራ  ሰው ሠራሽ   ቀለም አልቫ  ከፊል-ጠጣር  ንጥረ ነገር  ነው። ይህ ውህድ ለመቅለጥ 109 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ  ሙቀት የሚፈልግና ዝቅተኛ የመቅለጥ ባህሪ ያለው ሲሆን፤በፈሳሽ  ወይም በዱቄት መልክ ጥቅም ላይ የሚውል ነው።ዲዲቲ   በቀላሉ  የሚሟሟው  በውሃ ሳይሆን በቅባትና በዘይት ነክ ፈሳሾች በመሆኑ በዚህ  ባህሪው ታዲያ ለዲዲቲ የተጋለጡ ሰዎችና እንስሳት  ሕብረ ሕዋሳት ውስጥ  በቀላሉ መርዛማ ስብ  ሊከማች ይችላል።ይህ ክምችት ለረዥም ጊዜ የሚዘልቅ በመሆኑ ጉዳቱም የዚያኑ ያህል ነው።ይላሉ የመድሃኒት ጥናት ባለሙያና በኦሃዮ ስቴት ዩንቨርሲቲ የግሎባል ዋርሚንግ ኢንሸቲቭ የምስራቅ አፍሪቃ ዳይሬክተር የሆኑት ዶክተር ጌትነት ይመር ።እሳቸው እንደሚሉት ፤ኬሚካሉ በተለይ በአፈር ውስጥ ከሰላሳ ዓመታት በላይ የመቆየት ባህሪ ዓለው።

«ይህ ኬሚካል መጠነ ሰፊ ግልጋሎት ሲሰጥ ነበር።ቀደም ባሉት ጊዚያት የኖቬል ሽልማት እስከማስገኜት የደረሰ ኬሚካል ነው።ኬሚካሉ «በፋርማኮሎጅ» ስናወራው «ሃፍሶሊዩብል»/በከፊል ከሚሟሙ/ ውህዶች ውስጥ አንዱ ነው።ለየት የሚያደርገው ኅብረተሰቡ ማወቅ ያለበት።ይህ ኬሚካል ከሌሎች በተለዬ መልኩ በተለይ መሬት ላይ ከተቀመጠ ከአንድ አመት እስከ 30 ዓመት መቆየት የሚችል ኬሚካል ነው። » ካሉ በኃላ «በአንድ ወቅት ለዲዲቲ የተጋለጡ ሰውችም ደማቸው ውስጥ 30 ዓመት ሊቆይ ይችላል።በአግባቡ ካልተጠቀምንበት ሰውንም እንስሳንም አካባቢንም የሚጎዳ ኬሚካል ነው።»ብለዋል።

ዲዲቲ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ጀምሮ በነፍሳት አማካኝነት የሚመጡ እንደ ወባ እና ታይፈስ ከመሳሰሉ ሽታዎች ሰላማዊ ሰዎችን እና ወታደሮችን ለመጠበቅ  ጥቅም ላይ ውሏል።ከጦርነቱ በኋላም አርሶ አደሮች የሰብል ምርቶቻቸውን የሚያጠፉ ተባዮችን በመቆጣጠር ረገድ ዲዲቲ ውጤታማ መሆኑን በማየታቸው  አጠቃቀሙ ሊስፋፋ ችሏል።ለዚህ ስራውም ፖል ሄርማን ሙለር  በ1948 ዓ/ም በፊዚዮሎጅ ወይም በህክምና የኖቤል ሽልማትን አግኝቷል። ይሁን እንጅ መርዛማነቱ በነፍሳት ላይ ብቻ የተወሰነ ባለመሆኑ ዶክተር ጌትነት  እንደሚሉት፤ይህ መርዛማ ኬሚካል በሰዎች ላይ የጉበት ካንሰርን ፣ የነርቭ ሥርዓት ማወክን ፣  የአካል ጉዳቶችን እና ሌሎች የስነ-ተዋልዶ ጤና ችግሮችን የመሳሰሉ ፡ከባድ የጤና ጠንቆችን ያስከትላል። 

DDT Aerosol als Insektenspray
ምስል AP

«ቀጥታም ባይሆን በተዘዋዋሪ ዘረ-መልና ላይ በተለይም ከወንድ የዘር ማመንጫ ጋር በተገናኘ ሰፊ ችግር ያስከትላል።ችግሮቹም መውለድ ካለመቻል ጀምሮ ፣ውርጃ ፣ህፃናት ያለጌዚያቸው እንዲወለዱ ማድረግ፣የቆሽት ካንሰርና የጉበት ካንሰር እንደሚያስከትል መረጃዎች ያሳያሉ።»ነው ያሉት ዶክተር ጌትነት።

በመሆኑም፤ይህ ፀረ-ተባይ ኬሚካል በሰዎች፣በእንስሳትና በአካባቢ ላይ ሚያደርሰው ጉዳት  እያደገ በመምጣቱ አጠቃቀሙ  ከተገደበ ከ50 ዓመታት በላይ ሆኖታል። ከ19 60 ዎቹ ጀምሮ  በርካታ ሀገሮች  ኬሚካሉን ማገድ ወይም አጠቃቀሙን መገደብ የጀመሩ ሲሆን፤በጎርጎሪያኑ 1970 ዓ/ም ሃንጋሪ ፣ ኖርዌይ እና ስዊድን በ 1972 ዓ/ም ደግሞ ዩስ አሜሪካ ዲዲቲን አግደዋል፡፡በ2004 ዓ/ም ደግሞ 170 ሀገራት ዲዲቲ ከቁጥጥር ውጭ ለሆነ የወባ ወረርሽኝ ካልሆነ በስተቀር ጥቅም ላይ እንዳይውል በስዊድን ስቶኮሆልም ተስማምተዋል።

በኢትዮጵያም ከአስር ዓመት በፊት በጎርጎሪያኑ 2011 ዓ/ም ጀምሮ ዲዲቲ ጥቅም ላይ እንዳይውል መታገዱን በኢትዮጵያ የአካባቢ፣ የደንና  አየር ንብረት ለውጥ ኮሚሽን  የአካባቢ ህግ ተከታይነት ዳይሬክተር ጀነራል ተወካይ የሆኑት አቶ ግርማ ገመቹ ይገልፃሉ።

  «በ2011 ዓ/ም ነው ይህንን መጠቀም ያቆምነው ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ተከማችቶ ወደ ወደ 383 በሚሆኑ መጋዝኖች ነው እንዲቀመጥ የተደረገው።»ባለፉት ሁለት ዓመታት ቆጠራ የማድረግና መልሶ የማሸግ ወይም«ሴፍ ጋርዲንግ»ይባላል እዚያ ደረጃ ደርሷል።ስለዚህ በአጠቃላይ ወደ 1400 ቶን ይሆናል ብለን ነበር።ሲቆጠር ወደ 1300 ቶን «ዲዲቲ» ነው ያለው።»ካሉ በኃላ፤ ይህንን የማስወገድስራ እየተሰራ ነው ብለዋል።

ያም ሆኖ  ይህ ፀረ-ተባይ ኬሚካል ከሌሎቹ ጋር ሲነፃፀር በዋጋ ደረጃ ርካሽ   በመሆኑና በግንዛቤ ችግር የተነሳ በህንድና ከስሃራ በታች ሉ የአፍሪቃ ሀገራት እስካሁን ድረስ ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። በኢትዮጵያም  በቅርቡ በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ለሁለተኛ ዲግሪ ማሙያ የተሰራ  አንድ ጥናት እንደሚያሳየው  ይህንን አደገኛ  ፀረ-ተባይ ኬሚካል በአንዳንድ አካባቢዎች  በማሳ ላይ በተለይም ጫት የሚያመርቱ አርሶ አደሮች ይጠቀሙበታል።በጥናቱ እንደሚያሳየው ከተሰበሰበው የጫት ናሙና ውስጥ 80 በመቶ የሚሆነው  በውስጡ ዲዲቲን የያዘ ነው።

አቶ ግርማ  እንደሚሉት ዲዲቲ ከውጭ ማስገባትም ይሁን በሀገር ውስጥ ማምረት የተከለከለ በመሆኑ በጥናቱ የታየው፤ችግር በመጋዘን ተከማችተው ከሚገኙ ብዙ ሺህ ቶን ኬሚካል ጋር የተያዘዘ ሊሆን ይችላል ይላሉ። 

 «በተለያዩ የውይይት መድረኮች ላይ እንደዚህ አይነት አዝማሚያዎች እንዳሉ እንሰማለን።እያደረግን ያለነው እነዚህ መጋዝኖች በአግባቡ እንዲጠበቁ፤አሁን ባለን መረጃ ዲዲቲ ከውጭ አይገባም በሀገር ውስጥም አይመረትም።ምናልባት በመጋዘን ያለው ዲዲቲ ካልጠፋ በስተቀር ወይም ሌላ ተገቢ ያልሆነ ነገር ካልተደረገበት በስተቀር።ስለዚህ እነዚህን አዝማሚያዎች እንሰማለን።አንዳንድ አካባቢ ፋብሪካ ተቃጠለ ይባላል።ወይም ጠፋ የሚል ነገር ይመጣል።»ካሉ በኃላ፤ ነገር ግን የተጨበጠ ነገር አለመገኘቱን ገልፀዋል።ያም ሆኖ ከሚታዩት አዝማሚያዎች በመነሳት በጥናቱ የተነሳው ችግር የለም ማለት እንዳልሆነ አስረድተዋል።

በመጋዘን የሚገኘውን ኬሚካል  በሀገር ውስጥ አቅምና ቴክኖሎጅ ማስወገድ የማይቻል  በመሆኑ ፤ችግሩን ለመፍታትም ኮሚሽኑ በየመጋዝኖቹ የሚገኙ ኬሚካሉችን ወደ ውጭ በመላክ ለማስወገድ  ስራ መጀመሩም ተገልጿል።

እስከዚያው ግን  ይህ ውህድ ለጤና አደገኛ መሆኑን ኅብረተሰቡ በመገንዘብ ጥቅም ላይ ከማዋል ይቆጠብ። ብለዋል ሀላፊው አቶ ግርማ ገመቹ።

ዶክተር ጌትነት ይመር በበኩላቸው ዲዲቲ የሚያመጣው ጠንቅ ለትውልድ የሚሻገር በመሆኑ የሚመለከታቸው አካላት  ጥብቅ ቁጥጥር እንዲያደርጉ አሳስበዋል።

ፀሀይ ጫኔ

አዜብ ታደሰ