1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ግብፅ፤ አል ሲሲ ቃለ መሃላ ፈፀሙ

እሑድ፣ ሰኔ 1 2006

የቀድሞው የግብፅ ጦር ዋና አዛዥ አብደል ፋታህ አል ሲሲ አዲሱ የግብፅ ፕሬዚዳንት ሆነው ዛሬ ቃለ መህላ ፈፀሙ። ከአረብ የፀደይ አብዮት ሶስት ዓመት በኋላ እና የረዥም ዓመታት የሀገሪቱ መሪ ከሆስኒ ሙባረክ በኋላ ዳግም ከሀገሪቱ ጦር በመሪነት ሲሰየም ይህ የመጀመሪያው ነው።

https://p.dw.com/p/1CEa1
Ägypten Abdel-Fattah al-Sisi Vereidigung 08.06.2014
ምስል Reuters

በግንቦት ወር በተካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ አል ሲሲ 97 በመቶ ድምፅ በማግኘት አሸናፊ ሆነዋል። አዲሱ ፕሬዚዳንት በሀገሪቱ መረጋጋት አስፍነው እንደ ወትሮው የውጭ ሀገር ጎብኚዎችን ወደ ሀገሪቱ ይመጣሉ ብለው በርካታ ግብፃዊያን ተስፋ ያደርጋሉ። ተንታኞች ግን እንደሚሉት ዳግም በሀገሪቱ ብጥብጥ እንዳይነሳ ያሰጋል። ይህም ከአንድ ዓመት በፊት የቀድሞው ፕሬዚዳንት መሀመድ ሙርሲ ከስልጣን እንዲወርዱ አል ሲሲ ሚና በመጫወታቸው ነው። ከዚያን ጊዜ አንስቶ ከ40 000 በላይ የተቃውሞ ሰልፈኞች ታስረዋል።
ግብፅ ዉስጥ በተደረገዉ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ-ከምርጫዉ በፊት በሰፊዉ እንደታወቀዉ የቀድሞዉ የጦር ሐይሎች ማርሻል አብዱል ፈታህ አል ሲሲ እንደሚያሸንፉ ግልፅ ነበር። ምርጫዉ ከሁለት ሳምንት ግድም በፊት ነበር እንዲደረግ የታቀደዉ ይሁንና የምርጫ ጣቢዎች ኦና ሆነዉ በመዋላቸዉ ባለፈዉ ሳምንት ረቡዕ ተጨማሪ የምርጫ ቀን ሆኖ ዉሏል። አል ሲሲ የሾሟቸዉ የጊዚያዊ መንግሥቱ ባለሥልጣናት ቀንም ጨምረዉ፤ ድምፁን የማይሰጠዉንም ሕዝብ ለመቅጣት አስፈራርተዉም መምረጥ ከሚችለዉ ሕዝብ ድምፅ የሰጠዉ አርባ ስድስት በመቶዉ ብቻ ነዉ።ያም ሆኖ የዜና ምንጮች እንዳሉት የቀድሞዉ የጦር ጄኔራል በመፈንቅለ መንግሥት በተዘዋዋሪ የያዙትን ሥልጣን በቀጥታ ለመቆጣጠር ምርጫ ተደረገ መባሉ ራሱ በቂ ነዉ።
በምርጫዉ ሂደት የአል ሲሲ ተቀናቃኞች የሆኑት ሙሥሊም አክራሪዎች ብቻ ሳይሆኑ፣ ለግብፅ ችግር የመፍትሔ ሀሳብ የላቸውም የሚለው ሰፊው የሀገሪቱ ሕዝብም አል ሲሲ በተከተሉት አመራር ምን ያህል አለመደሰቱን ያሳየ መሆኑን የተቃዋሚ ወገኖች እና የፖለቲካ ታዛቢዎች መግለጻቸዉ ይታወቃል። የአስመራጩ ኮሚሽን ኃላፊ ለ«ኤም ቢ ሲ ምስር » ቴሌቪዥን እንዳስታወቁት፣ በሀገሪቱ የመምረጥ መብት ካለው 54 ሚልዮን ሐዝብ መካከል እስካሁን ድምፁን የሰጠው 35% ብቻ ነው። ይኸው ቁጥር ከ11 ወራት በፊት ከሥልጣን የተወገዱት ፕሬዚደንት መሀመድ ሙርሲ እአአ በ2012 ዓም ባሸነፉበት ፕሬዚደንታዊ ምርጫ ከወጣው 52 ከመቶ መራጭ ሕዝብ ጋ ሲነፃፀር በጣም ዝቅተኛ ነው።

አዜብ ታደሰ
ልደት አበበ

Ägypten Feier Abdel-Fattah al-Sisi Vereidigung 08.06.2014
ምስል picture-alliance/dpa