ጀርመን የህዝብ ቁጥርና የውጭ ዜጎች
ማክሰኞ፣ ጥር 21 2005የጨመረው መንግሥት በሚሰጠወ ማበረታቻ ብዙ ህፃናት ተወልደው ሳይሆን በአመቱ በርካታ የውጭ ዜጎች ወደ ጀርመን በመግባታቸው ነው ።
ከ29 ቀናት በፊት በተሰናበትነው በጎርጎሮሳውያኑ 2012 አም የጀርመን ህዝብ ቁጥር መጨመሩን የሃገሪቱ የስታትስቲክስ መሥሪያ ቤት አስታውቋል ። የህዝብ ቁጥር እድገት ወደፊት መቀነስ አሳሳቢ በሆነበት በጀርመን የህዝብ ቁጥር ማደግ እሰየው ቢያሰኝም ቁጥሩ የጨመረበት ምክንያት ግን ማነጋገሩ አልቀረም ። የዛሬው አውሮፓና ጀርመን ዝግጅታችን ትኩረት ነው ። ለዝግጅቱ ሂሩት መለሰ
የህዝብ ቁጥር እድገት ማሽቆልቆል በሚያሰጋት በጀርመን ዜጎች ልጆች እንዲወልዱ መንግሥት ልዩ ልዩ ማበረታቻዎችን ይሰጣል ። ህብረተሰቡ ልጆች እንዲወልድ በየጊዜው ከሚሻሻለው የወሊድ ፈቃድ በተጨማሪ ለእናቶችና አባቶች ልዩ ልዩ ድጎማዎችም ይደረጋሉ ። ያም ሆኖ ጀርመናውያን ልጆች እንዲወልዱ የሚደረገው ጥረት እምብዛም ውጤት አላመጣም ። አሁንም በጀርመን የሚወለዱ ህፃናት ቁጥር አነስተኛ ሲሆን የወደፊቱ ማህበራዊና ኤኮኖሚያዊ መዘዙ ደግሞ ከወዲሁ በእጅጉ እያሳሰበ ነው ። ይሁንና በአዲሱ የጎርጎሮሳውያኑ 2013 አ.ም መግቢያ ላይ እንደተሰማው ደግሞ የጀርመን ህዝብ ቁጥር እጎአ በ2012 አ.ም ጨምሯል ። የሃገሪቱ የስታትስቲክስ ፅህፈት ቤት እንዳስታወቀው የዝህብ ቁጥር የጨመረው መንግሥት በሚሰጠወ ማበረታቻ ብዙ ህፃናት ተወልደው ሳይሆን በአመቱ በርካታ የውጭ
ዜጎች ወደ ጀርመን በመግባታቸው ነው ። እንደ መስሪያ ቤቱ ጀርመን በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ከተለያየ የአለም ክፍል የሚሰደዱ ሰዎችን የምትስብ ሃገር ሆናለች ። በተሰናበተው የጎርጎሮሳውያኑ 2012 ወደ ጀርመን የገባው የውጭ ዜጋ ቁጥር 300 ሺህ ነው እንደ መሥሪያ ቤቱ ። አብዛኛዎቹ የመጡትም የአውሮፓ ህብረት አባል ከሆኑ የደቡብና የምሥራቅ አውሮፓ ሃገሮች ነው ። የሰፈሩትም እንደ ኮሎኝ ፍንክፈርትና ሙኒክ በመሳሰሉ ከተሞች ነው ። አምና ወደ ጀርመን ከተሰደዱት አውሮፓውያን ፣ ሃገሮቻቸው በኢኮኖሚ ቀውስ ክፉኛ የተጎዱት የግሪክ የስፓኝና የቡልጋርያ ዜጎች ያመዝናሉ ። ስራአጥነት በተስፋፋባቸው በእነዚህ ሃገሮች በቅርብ ጊዜ ውስጥ ለውጥ ይመጣል የሚል ተስፋ በመደብዘዙ በርካቶች ሃገራቸውን ለቀው በመሰደድ ላይ ናቸው ። ይሁንና ብዙዎቹ ጓግተው ጀርመን ቢመጡም ለአብዛኛዎቹ ጀርመን እንደቋመጡላት እጇቿን ዘርግታ የምትጠብቃቸው ሃገር ሆና ስለማያገኟት ቅር እንደሚሰኙ የበርሊኑ የስነ ህዝብና የልማት ተቋም ባልደረባ ሽቴፋን ክሮህኔርት ያስረዳሉ ። በዚህ የተነሳም ጀርመን አንዳንድ የአሠራርም ሆነ የመለካከት ለውጥ ማድረግ ይኖርባቸዋል ይላሉ ክሮህኔርት ።
«ጀርመን ባለፉት ጊዜያት የውጭ ተወላጆች ወደ ግዛቷ እንዳይገቡ ማገድ ቢቻላት በወደደች ነበር። አሁን ግን ወደ ጀርመን የገቡት ሰዎች ለኤኮኖሚያችን ተፈላጊዎች መሆናቸውን ተገንዝበናል። ኤኮኖሚው በሙያ የሠለጠኑ ፈላስያንን ይሻል። ይህም ማለት፤ ወደ ጀርመን ለሚገቡ የውጭ ተወላጆች፤ በሙያ መሠልጠናቸውን አምኖ ለመቀበል ሁኔታዎችን ማሻሻል ተገቢ ይሆናል። በሙያ የሠለጠኑት የውጭ ተወላጆች ፤ ከቤተሰቦቻቸው ጋር በጀርመን የመኖሪያ ፈቃድ አግኝተው መኖር ይቻላቸው ዘንድ ፣ በጀርመን የአመለካከትም ሆነ በዚህ ረገድ የአስተሳሰብ ለውጥ በመንጸባረቅ ላይ ነው። »
የውጭ ዜጎችን ከሚመለከቱ ህጎች ጋር ከተያያዙ ጉዳዮች በተጨማሪ የውጭ ዜጎች ጉዳያቸውን ለማስፈፀም በሚሄዱባቸው መሥሪያ ቤቶች እንዳይጉላሉም ቀልጠፍ ያለ አሠራር ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ ክሮንኽሬት ያሳስባሉ ። በአሁኑ ጊዜ ወደ ጀርመን በብዛት የሚመጡት ከፍተኛ እውቀት ያላቸው ፣ ጀርመን ውስጥ በሚፈለግ ሞያ የሰለጠኑ የውጭ ዜጎች ናቸው ። መሃንዲሶች ፣ ምሁራን እንዲሁም የሌሎች ተፈላጊ ሞያዎች ባለቤቶች ወደ ጀርመን እንዲመጡ ይበረታታሉ ። ሆኖም እንደ ክሮንኽርት በነዚህ ላይ ብቻ ማተኮሩ ተገቢ አይደለም ። ጀርመን ከዚህም በተለየ ሞያ የሰለጠኑ ሰዎችም ያስፈልጓታል ።
«ጀርመን፣ ኢንጂኔሮች ብቻ አይደሉም የሚያስፈልጓት። በህክምናው ዘርፍ ፤ በተለይ በጤና አጠባበቅ ረገድ ፣ ለምሳሌ ያህል ፣ በከፍተኛ ደረጃ የሠለጠኑ ባለሙያዎች በማያስፈልጉበት ቦታ ፤ ለህሙማን ክብካቤ ብቻ ማድረግ የሚችሉ ረዳቶች ያስፈልጋሉ። የቋንቋ ችሎታ ያላቸው በሌሎች ቦታዎች ነው መመደብ የሚኖርባቸው። ይህ ደግሞ መለስተኛ ሥልጠና ያገኙ የውጭ ተወላጆች ከጀርመን ኅብረተሰብ ጋር ተቀራርበው ተጋባብተው እንዲኖሩ ማለፊያ ዕድል የሚሰጥ ነው። »
የውጭ ዜጎች ከህብረተሰቡ ጋር ተቀራርበው እና ተዋህደው ለመኖር ያስችላቸዋል ተብሎ የታመነበትን የቋንቋ መርሃ ግብር የጀርመን መንግሥት ለውጭ ዜጎች እንዲሰጥ አድርጓል ። በዚህ መርሃ ግብር ለውጭ ዜጎች የጀርመንኛ ቋንቋን ፣ የሃገሪቱን የአስተተዳደር ስርዓት ና ባህል ያካተተ ትምሕርት እንዲከታተሉ ይደረጋል ። ይሁንና አሬና ሊንጉዋ የተባለው የቋንቋ ትምህርት ቤት ስራ አስኪያጅ ጉንተር ሃይንከር በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ጀርመን ለሚመጡ በከፍተኛ ደረጃ ለሠለጠኑ ባለሞያዎች የተለየ የቋንቋ መርሃ ግብር እንደሚያስፈልጋቸው ነው ከልምድ የሚናገሩት ።
«በከፍተኛ ደረጃ በሙያ ለሰለጠኑ ሰዎች ክፍት የሥራ ቦታዎችም አይታጡም፤---እንበል በኢንጂኔሪንግ፤ በሂሳብ ፤ በተፈጥሮ ሳይንስ -የምርምር ዘርፍ ረገድ ለሚመራመሩ ፤ እንዲሁም ለሀኪሞች፤ ነርሶች የሽማግሌዎችና አሮጊቶች ተንከባካቢዎች፤ ወይም በምግብ አሠራር ለሠለጠኑ ባለሙያዎች ቦታ ይኖራል። ታዲያ በጀርመንኛ ቋንቋ ትምህርት የገፉ ሆነው እንዲገኙ ይጠበቅባቸዋል። እርግጥ ነው፤ አንድ ሀኪም የሚጠቀምበት ጀርመንኛ ቋንቋ ዓይነት የተፈጥሮ ሳይንሳዊ ምርምር ከሚያካሂድ ባለሙያ የተለየ መሆኑ እሙን ነው። የምግብ አሠራር ያጠናውና የሚሠራው ባለሙያ፣ የቋንቋ አጠቃቀምም ከዚህ ይለያል።»
ለምሳሌ የጤናውን ዘርፍ በመሳሰሉ የስራ መስኮች የሚሰማሩ ባለሞያዎች ከፍ ያለ መካከለኛ የጀርመንኛ ቋንቋ እውቀት ስራ ለማግኘት ግዴታ ነው ። ያ ማለት ግን ለሥራ ወደ ጀርመን የሚመጡ የውጭ ዜጎች በሙሉ ጀርመንኛ የማወቅ ግዴታ አለባቸው ማለት አይደለም ። ወደ ጀርመን የሚፈልሱ የውጭ ዜጎች ቁጥር በመጨመሩ የቋንቋ ተማሪዎችም ቁጥር እጅግ አድጓል ። ከበርሊን የስነ ህዝብና ልማት ጉዳይ ተቋም ሽቴፋን ክሮኽነርት እንደተናገሩት አሁን ወደ ጀርመን በብዛት ከፈለሱት ህዝቦች መካከል ስፓኞች ይገኙበታል ። ከአመታት በፊት ስፓኝ ብዙዎች ለሥራ የሚሰደዱባት ሃገር ነበረች ። ዛሬ ግን ሁኔታው የተገላቢጦሽ ሆኗል ። ይህ እጣ ጀርመንንም ሊያሰጋት እንደሚችል ነው ክሮህኔርት የሚናገሩት ።
«እስፓኝም ፤ እ ጎ አ በ 2005 በብዛት የገቡ የውጭ ተወላጆችን ፣ ተቀብላ፤ በግንባታው ኢንዱስትሪ እንዲሠማሩ አድረጋ እንደነበረ አይዘነጋም። አሁን ግን ሥራ በማጣት ረገድ የመጀመሪያዎቹ ነው የሆኑት ። ሌላ ሥራ የማግኘት ዕድላቸውም ተመናምኗል።በእስፓኝ የደረሰው አደጋ በጀርመንም መከሠቱ አይቀሬ ነው የሚመስለው። አሁን የኤኮኖሚው ዕድገት እመርታ ባለማሳየቱ ፤ የተደቀነው ችግር ፤ በማኅበራዊ ኑሮ ረገድ ፣ ፈልሰው የገቡ የውጭ ተወላጆችን ይበልጥ እንደሚጎንጥ ፍንጭ መስጠቱ አልቀረም ። »
እስካሁን ግን ጀርመን የውጭ ዜጎች በብዛት የሚፈልሱባት ሃገር መሆኗ እንደቀጠለ ነው ። የወደፊቱን ደግሞ ወደፊት የምናየው ይሆናል ።
ሂሩት መለሠ
ሸዋዮ ለገሠ