ድሬደዋን ነፃ የንግድ ቀጠና የሚያደርገው አዲስ አሰራር
ሰኞ፣ ነሐሴ 2 2014
ድሬደዋን ነፃ የንግድ ቀጠና የሚያደርገውን አዲስ አሰራር ለመተግበር ዝግጅት ማጠናቀቁን የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አስታውቋል። ለተለያዩ መስኮች የቀረጥ ነፃን ጨምሮ የተለያዩ ምቹ ሁኔታዎችን የሚፈቅደው አዲሱ አሰራር በርካታ ጠቀሜታዎች አሉት ተብሏል።
በኢንደስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የስትራቴጂክ ጉዳዮች አማካሪ አቶ ኪያ ተካልኝ በቅርብ ቀናት በይፋ ይጀመራል ላሉት የድሬደዋ ነፃ ንግድ ቀጠና አሰራር ትግበራ ዝግጅት አጠናቀናል ብለዋል።
በሀገሪቱ የመጀመርያ የተባለው እና በድሬደዋ የሚተገበረው ነፃ የንግድ ቀጠና አሰራር በኢንቨስትመንት መስክ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች ምን የተለየ ፋይዳ ያመጣል ለሚለው ጥያቄ አቶ ኪያ ምላሽ ሰጥተዋል።
በኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የስትራቴጂ አማካሪው አቶ ኪያ በቅርብ ጊዜ ወደ ተግባር ይሸጋገራል ያሉት የድሬደዋ ነፃ የንግድ ቀጠና የተለያዩ ጠቀሜታዎች እንዳሉት አስረድተዋል።
በሀገሪቱ የኢንዱስትሪ እድገት የቀደመ ፋና ወጊነቷን ያጣችው ድሬደዋ ዳግም ለኢንደስትሪው ዘርፍ ማደግ ተስፋ ለተጣለበት አዲስ አሰራር ትግበራ ታጭታለች - አማካሪው እንደሚሉት ድሬደዋ የተመረጠችው በተዘጋጀ መስፈርት ነው።
ከሁለት ዓመት በፊት ተመርቆ ስራ የጀመረው የድሬደዋ የኢንዱስትሪያል ፓርክ በውስጡ አስራ አምስት ሼዶች ቤኖረውም በኢንቨስተሮች ተይዞ ወደ ስራ የገባው ከአምስት አይበልጥም። በአጭር ጊዜ ይተገበራል የተባለው አሰራር በእዚህ ረገድ ጥሩ መነቃቃት ይፈጥራል የሚል ተስፋ አሳድራል።
መሳይ ተክሉ
ታምራት ዲንሳ
እሸቴ በቀለ