1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ደቡብ ሱዳን ዉጊያና የሠላም ጥረት

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 10 2006

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንደሚለዉ ፕሬዝዳት ኪየር የሚወለዱበት የዲንካ እና ማቼር የሚወለዱበት የኑዌር ጎሳዎች መልክ እና ባሕሪ የያዘዉ ዉጊያ ፈጣን መፍትሔ ካላገኘ አደገኛ ነዉ።ደቡብ ሱዳን፥ ነፃነት ያወጀችበትን ሁለተኛ ዓመት-ከመንፈቅ፥ ከረጅም ጦርነት የተላቀቀችበትን ሥምንተኛ ዓመት፥ እነሆ በጦርነት ልታከብር ዉጊያ ጀምራለች።

https://p.dw.com/p/1AdRK
ምስል Adriane Ohanesian/AFP/Getty Images

የደቡብ ሱዳን መንግሥት ጦር እና በመንግሥት ላይ ያመፁት ሐይላት ወታደሮች ባለፈዉ ዕሁድ ርዕሠ-ከተማ ጁባ ዉስጥ የጀመሩት ዉጊያ ወደ ሌሎች የሐገሪቱ አካባቢዎች እየተዛመተ ነዉ።የቀድሞዉ ምክትል ፕሬዝዳት የሪክ ማቼር ታማኞች የተባሉት ሐይላት ዛሬ ቦር የተባለችዉን ከተማ ተቆጣጥረዋል።በሌሎች አካባቢዎችም ዉጊያዉ መቀስቀሱ ተዘግቧል።የዉጪ መንግሥታት ዜጎቻቸዉን ከአዲሲቱ ሐገር እያሰወጡ ነዉ።ለግጭቱ ሠላማዊ መፍትሔ ለማፈላለግ ኢትዮጵያን ጨምሮ አራት የአካባቢዉ ሐገራት ዉጪ ጉዳይ ሚንስትሮቻቸዉን ወደ ጁባ ልከዋል።ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።


አዲሲቱ አፍሪቃዊት ሐገር ነፃነትዋን ካወጀችበት ጊዜ ጀምሮ በርግጥ ዉጊያ ጦርነት ተለይቷት አያዉቅም።የእስካሁኑ ጦርነት ዓለም ፈጥኖ-ጣልቃ ለመግባት፥ አለያም ከዋሽግተን፥ ብራስልስ ብዙ ጊዜ እንደሚሰማዉ ካርቱሞችን ደፍሮ ለማዉገዝ የሚጣደፍበት ነበር።ወይም «የጎሳ ግጭት» ብሎ የሚያቃልለዉ ዓይነት።ያሁኑ ከመጀመሪያዉ ይልቅ-ሁለተኛዉን፥ ከሁለተኛዉ ይበልጥ ደግሞ የፖለቲካ ሽኩቻ፥ የሥልጣን ሽሚያ፥ እና የርስ-በርስን ጦርነት መልክ እና ባሕሪ የተላበሰ ነዉ።

እርግጥነዉ የወቅቱን የአፍሪቃ ሕብረት እና የምሥራቅ አፍሪቃ የልማት በይነ-መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) በእንግሊዝኛ ምሕፃረ-ቃሉ የሊቀመንበርነት ሥልጣን የያዘችዉ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸዉ ረዳ ግጭቱ በመገናኛ ዘዴዎች እንደሚዘገበዉ አይደለም ይላሉ።

ከጁባ፥ ከካምፓላ፥ ከናይሮቢ የሚወጡ ዘገቦች ግን ተቃራኒዉን ነዉ የሚሉት።ዕሁድ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራን ተላብሶ ጁባን እስከ ትናንት ባናወጠዉ ዉጊያ በትንሽ ግምት ከስድስት መቶ በላይ ሰዎች ተገድለዋል።ወደ ሃያ ሺሕ የሚጠጉ አንድም ተሰደዋል፥ አለያም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቅጥር ግቢዎች ሙጥኝ ብሏል።

ዛሬ ርዕሠ-ከተማይቱ ዉጊያዉ ጋብ፥ ቀለል ሲልላት ቦርን ይለብቃት ይዟል።የመንግሥት ጦር ቃል አቀባይ ፊሊፕ አጉዋር ጦራቸዉ ቦር ላይ መሸነፉን ዛሬ ጠዋት አምነዋል።ቃል አቀባዩ እንዳሉት ቦርን የሚቆጣጠረዉ የቀድሞዉ ምክትል ፕሬዝዳት የሪክ ማቻር ታማኞች ናቸዉ።

በ2011 በመንግሥት ላይ አምፀዉ ኋላ ተደራድረዉ የመንግሥት ጦርን ተቀላቅለዉ የነበሩት ሐይለኛ የጦር ጄኔራል ፒተር ጋዴት ማቼርን ደግፈዉ ጆንግሌይ የሠፈረዉን የመንግሥት ጦር ማጥቃት ይዘዋል።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንደሚለዉ ቶሪት የተባለችዉ ከተማም በዉጊያ እየራደች ነዉ።ዩናይትድ ስቴትስ፥ ብሪታንያ እና ሌሎችም ምዕራባዉያን ሐገራት ተፋላሚዎችን ከመሸምገል በፊት ሁሌም-እንደሚያደርጉትን የዜጎቻቸዉን ሕይወት ለማትረፍ ከዚያ ማስወጣቱን አስቀድመዋል።

የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ቃል አቀባይ ጌታቸዉ ረዳ እንዳሉት መንግሥታቸዉ እንደሌሎቹ መንግሥታት ሁሉ ዜጎቹን ባያስወጣም የጥንቃቄ እርምጃ እየወሰደ ነዉ።

ፕሬዝዳት ሳላቪ ኪር እና ኪር ከሥልጣን ያስወገዷቸዉ የቀድሞዉ ምክትል ፕሬዝዳት ሪክ ማቻር እንደጫሩት የሚታሰበዉን እሳት ለማጥፋት «አንድ ሁለት» ማለት የጀመሩት የኢጋድ አባል ሐገራት ናቸዉ።ኢትዮጵያ፥ ኬንያ፥ ጀቡቲ እና ዩጋንዳ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትሮቻቸዉን ወደ ጁባ ልከዋል።

የሚንስትሮቹ ተልዕኮ ሁኔታዉ «እንዳይባባስ መግታት» ከሚል ጥቅል መግለጫ በስተቀር ዝር ዝር ጉዳዩ አልተነገረበትም።መፈንቅለ መንግሥት በማሴር የተወነጀሉት የቀድሞዉ ምክትል ፕሬዝዳት ማቼር ያሉበት ሥፍራ አይታወቅም።በመፈንቅለ መንግሥቱ የተጠረጠሩ አስር የቀድሞ ባለሥልጣናት እና ፖለቲከኞች ታስረዋል።አንዳድ የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት ሚንስትሮቹ ምናልባት ተፋላሚዎችን ለማደራደር ይሞክሩ ይሆናል።አቶ ጌታቸዉ ግን ይሕን ማረጋገጥ አልፈለጉም።


የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንደሚለዉ ፕሬዝዳት ኪየር የሚወለዱበት የዲንካ እና ማቼር የሚወለዱበት የኑዌር ጎሳዎች መልክ እና ባሕሪ የያዘዉ ዉጊያ ፈጣን መፍትሔ ካላገኘ አደገኛ ነዉ።ማም-ምን አለ ምን ደቡብ ሱዳን፥ ነፃነት ያወጀችበትን ሁለተኛ ዓመት-ከመንፈቅ፥ ከረጅም ጦርነት የተላቀቀችበትን ሥምንተኛ ዓመት፥ እነሆ በጦርነት ልታከብር ዉጊያ ጀምራለች።

Südsudan Riek Machar Vizepräsident Archiv 2011
ምስል Stan Honda/AFP/Getty Images
Südsudan Juba Ausschreitungen Präsident Salva Kiir
ምስል Reuters

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ



ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ