ደማስቆ የሶሪያ መከላከያ ሚኒስትር ተገደሉ
ረቡዕ፣ ሐምሌ 11 2004በመንግሥት መገናኛ ብዙሃን ዘገባ መሰረት ደማስቆ በሚገኘው የብሔራዊ ፀጥታ ምክር ቤት ስብሰባ በማካሄድ ላይ ሳሉ በደረሰው በዚሁ አደጋ የሶሪያ የመከላከያ ሚኒስትር ጀነራል ዳውድ ራጃ ና የፕሬዝዳንቱ አማች አሴፍ ሻውካት ተገድለዋል ። በቦብም ጥቃቱ የሃገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ አል ሻር ና የብሔራዊ ፀጥታ መስሪያ ቤት ሃላፊ ጀነራል ሂሻም ኢክቲያር ከቆሰሉት መካከል ይገኙበታል ። ከአደጋው በኋላ የሶሪያ መንግሥት ባወጣው መግለጫ አሸባሪነትን መዋጋቱን እንደሚቀጥል አስታወቋል ። በዛሬው አደጋ የተገደሉት ጀነራል ራጃ ከ,መከላከያ ሚኒስትር ሥልጣናቸው በተጨማሪ የጦር ኃይሎች ምክትል አዛዥ እንዲሁም የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሊቀመንበርም ነበሩ ።
ሻውካት ደግሞ ምክትል መከላከያ ሚኒስትርና የቀድሞ የስለላ መስሪያ ቤት ሃላፊ ነበሩ ። የሶሪያ አማፅያን ትግሉ ከሶሪያ ክፍለ ግዛቶች ወደ መዲናይቱ ደማስቆ መሸጋገሩን ትናንት አስታውቀው ነበር , ይህ በእንዲህ እንዳለ የሶሪያውን የርስ በርስ ግጭት ለማስቆም የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሃፊ ባን ኪሙን ዲፕሎማሲያዊ ጥረታቸውን ቀጥለዋል ። ባን ኪሙን ዛሪ ከቻይና መንግሥት መሪዎች ጋር በጉዳዮ ላይ ለመምከር ቻይና ነበሩ ። ባን እንዳሉት ቻይና ግጭቱን በማስቆም ረገድ ወሳኝ ድርሻ አላት ።
« ቻይና በጣም ጠቃሚ ሚና ልትጫወት ትችላለች ። እዚህ ከተገኘሁበት ምክንያት አንዱ ይህ ነው ። ይህን ጉዳይ ከቻይና መንግሥት መሪዎች ከቻይና ፕሬዝዳንት ከሁጅንታው ና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዩንግ ዴችና እንዲሁም ከሌሎችም ባለሥልጣናት ጋር እመክርበታለሁ ። የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት አንዳንድ እርምጃዎችን ወስዷል ። ሆኖም የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት በከፍተኛ ደረጃ እንዲተባበር ይጠበቃል ። ምክር ቤቱ ደም መፋሰሱ እንዲቆም ወሳኝ እርምጃ መውሰድ ይኖርበታል »
ሂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ