1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ያለነፃነት እና ክስ አምስት ዓመት

ማክሰኞ፣ ኅዳር 28 2008

ዊክሊክስ የተሰኘዉ አጋላጭ ድረገጽ መሥራች ጁሊያን አሳንዥ ክስ ሳይመሠረትበት ነፃነቱን እንዳጣ አምስተኛ ዓመቱን ያዘ። በጎርጎሪዮሳዊዉ 2010ዓ,ም ልክ በትናንትናዉ ዕለት ነበር አሳንዥ ስዊድን ዉስጥ ክስ የቀረበበት። ከሁለት ዓመታት በኋላም የለንደን ፖሊስ አሳልፎ ለስዊድን እንዳይሰጠዉ እዚያ በሚገኘዉ በኤኳዶር ኤምባሲ ዉስጥ ገብቶ ከለላ አገኘ።

https://p.dw.com/p/1HJS9
Wikileaks-Gründer Julian Assange
ምስል Getty Images/AFP/F. Coffrini

[No title]

ከዚያን ጊዜ አንስቶም ጉዳዩ እንደተንጠለጠ እሱም ከተደበቀበት ሳይወጣ ለዚህ ጊዜ ደረሰ።

ዊክሊክስ ዛሬም ሥራዉን ቀጥሏል። ባለፈዉ ሳምንት ሐሙስ ምሥጢር አጋላጩ ድረገጽ በዩናይትድ ስቴትስ፣ በአዉሮጳ ኅብረት እና በሌሎች 22 ሃገራት መካከል በአገልግሎት ላይ ለማካሄድ ስለታቀደ የንግድ ስምምነት ድብቅ መረጃ ይፋ አድርጓል። የዊክሊክስ መሥራች እና ቃል አቀባይ ጁሊያን አሳንዥ ያለነፃነት እና ክስ አምስት ዓመት ይህን ጨምሮ በቅርቡ የፓስፊክ ተሻጋሪ ጉድኝትን፤ እና ባለፈዉ ሰኔ ወር ደግሞ የሳዉድ አረቢያ የዲፕሎማቲክ አገልግሎትን በሚመለከት 60,000 የመረጃ ልዉዉጦችን እዚያዉ ተገን ባገኘበት ለንደን በሚገኘዉ የኤኳዶር ኤምባሲ ዉስጥ ሆኖ ተከታትሏል። ከጎርጎሪዮሳዊዉ 2012 የሰኔ ወር አንስቶ እያንዳንዷን ዕለት አሳንዥ ያሳለፈዉ በዚህ ኤምባሲ ሕንፃ ዉስጥ ነዉ። አዉስትራሊያዊዉ በጥቅሉ ነፃነቱን ካጣ አምስት ዓመታት ተቆጥረዋል። ከስዊድን ፍርድ ቤት ዓለም አቀፍ የእስራት ማዘዣ ተቆርጦበታል። የክሱ መንስኤም ሁለት ሴቶች በአንድ ቀን ከእሱ ጋር በወዳጅነት ወሲብ መፈጸማቸዉን ለፖሊስ በማሳወቅ አሳንዥ ተመርምሮ HIV በደሙ ዉስጥ እንዳለና እንደሌለ እንዲመረመር ማለታቸዉ ነዉ። ጉዳዩ ለስቶክሆልም አቃቤ ሕግ ይቀርብ እና ጉዳዩን የተመለከቱት አቃቢተ ሕግ ለጥርጣሬ የሚያደር በቂ ነገር በማጣታቸዉ ይጥሉታል። ከዚያም ሌላ አቃቤ ሕግ ከጎንተንበርግ ከተማ ጉዳዩን ዳግም እንደአዲስ ያነሳሉ። ለዓመታትም ጉዳዩ በመጀመሪያ የምርመራ ሂደት ላይ ይቆማል። እስከዛሬም የቀረበ ክስ የለም። ስለጉዳዩ የሚነሳ ነገር ካለም ስዊድን በግለሰቡ ላይ ይፋ ያደረገችዉ የእስር ማዘዣ ብቻ ነዉ። በዚያም ላይ ስዊድን አሳንዥን ለዩናይትድ ስቴትስ አሳልፋ እንደማትሰጥ ዋስትና ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነችም። ይህ ያሰጋዉ አሳንዥ ጥገኝነት ባገኘበት የኤኳዶር ኤምባሲ መቀመጥ ግድ ሆኖበታል። ዊኪሊክስ በጎርጎሪዮሳዊዉ 2010ዓ,ም ስለአፍጋኒስታን እና ኢራቅ ጦርነቶች ዕለታዊ ማስታወሻዎችን፤ በተለይም ደግሞ የአሜሪካን ኤምባሲ የመረጃ ልዉዉጦችን በማጋለጡ የዋሽንግተን የአጸፋ ምላሽ ጠንካራ ነበር። አሳንዥ እንዲገደል የተስማሙ የሀገሪቱ ፖለቲከኞች ነበሩ። የአሜሪካን መንግሥት ቁጣና ትኩረትም በምሥጢር አጋላጩ ድረገጽ ላይ ብቻ ሳይሆን ገመናዉን ባቀበለዉ አካል ላይም ነዉ። በዚህ ምክንያትም ወደዚያ ተላልፎ እንዳይሰጥ ሊያደርጉ ይችላሉ የተባሉ የሕጋዊ ሂደቶችን ሁሉ ከሞከረ በኋላ አሳንዥ ኤኳዶር ኤምባሲ ተጠግቶ ከተቀመጠ ሶስተኛ ዓመቱን ያዘ። ደራሲ እና ጋዜጠኛ ቻርለስ ግላስ የፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ መንግሥት ከቀድሞዎቹ በበለጠ በርካታ ጋዜጠኞች ላይ ክስ መመሥረቱን ያስረዳል።

London Assange Ecuadorianische Botschaft 18.8.2014
አሳንዥ ከኤኳዶር ኤምባሲ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጥ ጎርጎሪዮሳዊዉ 2014ምስል picture-alliance/dpa
Symbolbild Wikileaks
ምስል picture-alliance/dpa/J. Büttner

«የኦባማ አስተዳደር ያለፉት መንግሥታት ባጠቃላይ ካደረጉት ይበልጥ በርካታ ጋዜጠኞችን ከሷል። በ1917 የተደነገገዉን የስለላ ሕግ ማለትም በወቅቱ የነበሩት ለዘብተኛ ፕሬዝደንትዉድሮዉ ዊልሰን በጦነርት ወቅት የሚወሰድ ርምጃ በሚል ሰላይን ሳይሆን ጋዜጠኛን መክሰስ የሚለዉን ሲጠቀም ቆይቷል። የኦባማ አስተዳደር በመላዉ ዓለም የሚፈፅመዉ የቁም ስቅል፤ ግድያ፤ እንዲሁም ተጠርጣሪዎችን ከአንድ ሀገር ይዞ ወደሌላ መዉሰድ እንዲጋለጥ አይፈልግም። ይህን ማጋለጥ ደግሞ የነፃ ፕረስ ሥራ ነዉ።»

የግላስን አስተያየት ለጋዜጠኞች የሚሟገተዉ የድንበር የለሽ ጋዜጠኞች የቦርድ አባል ማቲያስ ሽፒልካምፕም ይጋሩታል።

«እዉነታዉን ስንመለከት ምሥጢር አጋላጮቹ ላይ የሚቀርበዉ ክስ ተጠናክሯል፤ ከዚህ በፊት ባልተለመደ ሁኔታም ጠንካራ ክትትል እየተደረገባቸዉ ነዉ። ይህም በግልፅ ሊተች የሚገባዉ ነዉ።»

ሽፒልካም አክለዉም ዩናይትድ ስቴትስ ዊክሊክስ ሌሎች አጋላጭ መረጃዎችን ይፋ እንዳያደርግ የተለያዩ የማደናቀፍ ሙከራዎች ማድረጓም የፕረስ ነፃነትን የሚገድብ ነዉ በማለት ይተቻሉ። ከእርምጃዎቹ መካከል አማዞን ለዊክሊክስ የኢንተርኔት መስመር እንዳይሰጠዉ ማስፈራራት እና ፔይፓል ለምሥጢር አጋላጩ ድረገጽ ገንዘብ እንዳያሰባስብ ማገድንም ጠቅሰዋል። ዊኪሊክስ የሰዎችን ህይወት ለአደጋ አጋልጧል የሚለዉን የዋሽንግተንን ክስም ያጣጥላሉ። ይህ ሁሉ ምናልባት በአሳንዥ የስዊድን የፍርድ ቤት ጉዳይ ላይ ተፅዕኖ ይኖረዉ ይሆን? የወንጀል ሕግ ምሁር የሆኑት ኒኮላዎስ ጋሴዝ የፍርድ ሂደቱ ሚዛናዊነት ጥያቄ ላይ ወድቋል ይላሉ።

London Botschaft Ecuador Polizeibewachung
የብሪታንያ ፖሊስ በኤኳዶር ኤምባሲ ደጃፍምስል picture-alliance/empics/D. Lipinski

«የስዊድን የፍትህ አካል በሌሎች የተለያዩ አጋጣሚዎች በርካታ የቪድዮ ምርመራዎችን እና ከሀገር ዉጭ ያሉ ምስክሮችን አነጋግሮ ያዉቃል፤ ባለፈዉ ዓመት ብቻም 44 ጊዜ ይህን አድርጓል ብዬ አስባለሁ። አሳንዥን በተለመለከተ ግን አንዲት አስተያየት ሳይሰነዝር ለረዥም ዓመታት ዝም ማለቱ ያልተለመደ ነዉ። እናም በዚህ ሁኔታ እንደምናዉቀዉ አንድ ይፋዊ ጉዳይ እንዲሁ እንዲተዉ አድርጓል።»

አካሄዱም እሳቸዉ እንደሚሉት ጉዳዩን ወደፍርድ ቤት ማድረስ የሚችል አቅም ያለዉ አቃቤ ሕግ ያለ እንዳይመስል አድርጎታል።

ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ