የፀረ-ሽብር ሕጉ ማሻሻያና ሂደቱ
ማክሰኞ፣ የካቲት 5 2011በሀገሪቱ በቅርቡ የተጀመረዉን ለዉጥ ተከትሎ ግን እነዚህን ህጎች ለማሻሻል ወደ ስራ መገባቱ ሲገለፅ ቆይቷል።ለመሆኑ የእነዚህ ህጎች ማሻሻያ ምን ደረጃ ላይ ነዉ ያለዉ?
የኢትዮጵያ መንግስት የሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶችን አፍነዋል ተብለው ከሚወቅስባቸዉ ህጎች መካከል የፀረ-ሽብር ህግ፣መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ህግና የፕሬስ ህጉ ተጠቃሾች ናቸዉ። ሀገሪቱ በቅርቡ የጀመረችዉን ለዉጥ ተከትሎ እነዚህንና ሌሎች «አፋኝ» የተባሉ ህጎችን ለማሻሻልና መሠረታዊ የፍትሕ ሥርዓት ለውጥ ለማካሔድ የሚሠራ "የፍትሕና የሕግ ሥርዓት ማሻሻያ ብሔራዊ ምክር ቤት" ተቋቁሞ ወደስራ መግባቱን መንግስት በተለያዩ ጊዜዎች ሲገልፅ ቆይቷል።በዚህ መሰረት ሰሞኑን የበጎ አድራጎትና ማህበራት አዋጅ ተሻሽሎ የስቪክ ማህበረሰብ ድርጅቶች በሚል ፀድቋል።ለመሆኑ የሌሎቹ ህጎች ማሻሻያ ምን ደረጃ ላይ ነዉ ያለዉ በሚል DW ያነጋገራቸዉ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ዓቃቤ ህግ የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ አቶ ዝናቡ ቱሉ እንደሚሉት ህጎቹ በሚመለከታቸዉ አካላት ዉይይት እየተደረገባቸዉ ነዉ።በተለይ በርካታ የፖለቲካ ሰዎችንና ጋዜጠኞችን ለዕስር መዳረጉ የሚነገርለት የፀረ ሽብር ህግ።
ረቂቅ ህጉ ፤በኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ከመፅደቁ በፊት የሚንስትሮች ምክር ቤትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት አስተያየት እንደሚሰጡበት እየተጠበቀ መሆኑን አመልክተዋል። ሀገሪቱ የደረሰችበትን ፖለቲካዊና ለዉጥ ከግምት ዉስጥ በማስገባት የማሻሻያ ረቂቁ መዘጋጀቱንም አብራርተዋል።
በተጨማሪም የመረጃ ነፃነት አዋጅና የምርጫ ህግን ለመሳሰሉትም በተመሳሳይ ሂደት የማሻሻያ ረቂቅ እየተዘጋጀ መሆኑን አመልክተዉ፤ የተጀመረዉን የፍትህና የዲሞክራሲ ስርዓት ለማጎልበት የሚያግዙ የፀረ ጥላቻ ንግግር አዋጅን የመሳሰሉ ሌሎች አዳዲስ አዋጆችን ለማዉጣት በሂደት ላይ መሆኑን ተናግረዋል።
የሚወጡት ህጎች መሬት ላይ መዉረዳቸዉና ተፈፃሚነታቸዉን የሚከታተል የህግ ማዕቀፍ ለማዉጣት የኢትዮጵያ ጠቅላይ ዓቃቤ ህግ ዝግጅት ላይ መሆኑን ሀላፊዉ ጨምረዉ ገልፀዋል።
ሙሉ ቅንብሩን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነዉ ያድምጡ።
ፀሐይ ጫኔ
ኂሩት መለሰ