1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጣና መድረክ

ሰኞ፣ ሚያዝያ 28 2011

የጣና ፎረም እንዴት ተመሰረተ፣ ዓላማውስ ምንድን ነው? በተለይ በአፍሪካ ቀንድ ያለው ተስፋና ተግዳሮት የሚሉ ጉዳዮችን እናነሳልን፡፡ አፍሪካ ከቅኝ ግዛት ከተላቀቀችበት እ.ኤ.አ ከ1960ዎቹ ጀምሮ አፍሪካውያን ራሳቸውን ማስተዳደር ጀምረዋል፡፡ በፖለቲካ፣ በማህበራዊና በኢኮኖሚው ዘርፍ በሁለት እግራቸው ለመቆም ጥረትም አድርገዋል፡፡

https://p.dw.com/p/3I0JO
Äthiopien 8. Tana Forum | Moussa Faki & Präsident Sahle-Work Zewde
ምስል DW/A. Mekonnen

8ኛዉ የጣና መድረክ

አፍሪካን በፖለቲካ፣ በሰላም፣ በደህንነት፣ በኢኮኖሚና በማህበራዊ መስኮች ለማቀራረብና አህጉሯን ካለችበት ችግር ማውጣት ያስችላሉ የተባሉ በርካታ ተቋማትና መድረኮች ተመስርትዋል። በ2012 የተመሰረተው ጣና ከፍተኛ የሰላምና የደህንነት ፎረም (መድረክ) (ጣና ፎረም) አንዱ መድረኩ በተለይ በአህጉሪቱ የሚከሰቱ የሰላም፣ የደህንነትና የአካባቢያዊ ትስስር እጦትን እያጠና፣ ክርክሮችን እያዘጋጀና የሚደረስባቸውን መደምደሚዎችና ጭብጦችን ለውሳኔ ሰጪ አካላትና ለአፍሪካ መሪዎች ያቀርባል፡፡

የጣና ፎረም እንዴት ተመሰረተ፣ ዓላማውስ ምንድን ነው? በተለይ በአፍሪካ ቀንድ ያለው ተስፋና ተግዳሮት የሚሉ ጉዳዮችን እናነሳልን፡፡ አፍሪካ ከቅኝ ግዛት ከተላቀቀችበት እ.ኤ.አ ከ1960ዎቹ ጀምሮ አፍሪካውያን ራሳቸውን ማስተዳደር ጀምረዋል፡፡ በፖለቲካ፣ በማህበራዊና በኢኮኖሚው ዘርፍ በሁለት እግራቸው ለመቆም ጥረትም አድርገዋል፡፡ ሆኖም ግን ግጭት፣ ስደት፣ ሞት፣ መፈናቀልና ድህነት የተጠናወታት አፍሪካ አሁንም ቢሆን ከዚህ አዙሪት የወጣች አትመስልም፡፡

ለዚህ ደግሞ በርካታ ምክንያቶች ቢኖሩም ክርሰቶፈር ኦቻንጃ የተባሉ ናይጀሪያዊ ፀሐፊ በ2012  “ብዙሐን መገናኛና የዴሞክራሲ ትግል በአፍሪካ” በሚል በፃፉት መጽሐፍ እንደገለፁት የአፍሪካ ችግር ስር የሰደደ ነው፡፡ ኦቻንጃ እንደሚሉት አፍሪካ ከቅኝ ግዛት በኋላ  በራሷ ልጆች መተዳደር ስትችል ዲሞክራሲን ታሰፍናለች ቢባልም ከነፃነት በኋላ በነበሩ 20 ዓመታት ውስጥ አፍሪካን ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ከዚህም ከዚያም አናውጧታል፡፡ በሁሉም የአፍሪካ አገሮች በሚባል ደረጃ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራዎች መደረጋቸውን ፀሐፊው ጠቁመዋል፡፡ ያን ተከትሎም ሙስና፣ አድልዎ የስልጣንን  ወንበርን ሙጥኝ አድርጎ በመያዝ የአፍሪካዊያን መለያ ሆኖ የዲሞክራሲን መንገድ ዘግቶታል ብለዋል፡፡
ቻዛን የተባሉ ተንታኝን ጠቅሰው ክርስቶፈር ኦቻንጃ እንደፃፉት ደግሞ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ከ17 በላይ የአፍሪካ አገሮች ርዕሰ ብሔሮች በመፈንቅለ መንግስት ስልጣን የያዙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
አንዳንዶቹ ደግሞ ስልጣንን ሙጥኝ በማለት ከስልጣን መንበራቸው ላይ ሆነው ሞት ሚጠብቁ አንደነበሩ፣ አሁንም እንዳሉ ፀሀፊው ይናገራሉ፡፡ በመሆኑም ተሰፋዎች ቢኖሩም ስር የሰደደውን የአፍሪካን ችግር በቀላሉ ማሸነፍ እንደማይቻል ነው የሚናገሩት፡፡
እነዚህንና ሌሎችንም የአህጉሪቱን ችግሮች እያጠኑ የመፍትሄ ሐሳቦችን ከሚያቀርቡ ተቋማት መካከል ጣና ከፍተኛ የሰላምና የደህንነት ፎረም አንዱ ሲሆን በዋናነት ሰላምን፣ ደህንነትንና አካባቢያዊ ትብብርን ለማጠናከር ታስቦ የተመሰረተ ፎረም ሆኖ እንደተቋቋመ በአሜሪካ የክርስቶፈር ኒውፖርት ዩኒቨርሲቲ ለ25 ዓመታት በታሪክ መምህርነት ያገለገሉትና በጣና ፎረም ላይ ተሳታፊ የነበሩት ፕሮፈሰር ሹመት ሲሻኝ ተናግረዋል፡፡
ፕሮፌሰር ሹመት እንደሚሉት ፎረሙ ከውጤት አኳያ ብዙ የሚጠቀስ ነገር ባይኖረውም ተሰሰፋዎች እንዳሉት ግን አልሸሸጉም፡፡
ጣና ከፍተኛ የሰላምና የደህንነት ፎረም ባለፉት ዓመታት ከመሰብሰብ ውጭ ብዙም ጉልህ ድርሸ አላበረከተም እየተባለ ስሞታ ቢበዛበትም እንደ አፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሳ ፋቂ ማህማት ግን ከጣና ፎረምና ከሌሎችም ውይይቶችና ጭብጦች በመነሳት በተደረገው ስራ ውጤት እየተገኘ እንደሆነ ሰሞኑን በባሕር ዳር በተካሄደው 8ኛው የጣና ፎረም ላይ ባደረጉት ንግግር አመልክተዋል፡፡
ሚስተር ማህማት እንደሚሉት በኤርትራና በኢትዮጵያ መካከል የተደረሰው ስምምነት ከሁለቱ አገሮች ባለፈ ለአካባቢው አገሮች የትብብር መንገድ መክፈት መቻሉን አብራርተዋል፡፡ የኤርትራና ጅቡቲ መቀራረብ፣ በደቡብ ሱዳን ተፋላሚ ወገኖች መካከል ሰላም ለማምጣት እየተደረገ ያለው ጥረትና በቅርቡ ስልጣን የያዘው የሱዳን ጊዚያዊ የሽግግር ካውንስል ሰልጣኑን ለህዝብ አንዲያስረክብ ግፊት መደረጉ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት (IGAD) እና  የአፍሪካ ህብረት በአፍሪካ ቀንድ ሰላም እንዲመጣ የሚደርጉትን ጥረት እንደሚያሳይ ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የተደረሰው የሰላም ስምምነትና የሱዳን ወቅታዊ ሁኔታ ወደ ሰላማዊ መንገድ መሄድ መቻሉ በአፍሪካ ቀንድ ያለው ፖለቲካዊ ቀውስና የነበረው የትብብር ሂደት መሻሻሉን መለከቱት ደግሞ 8ኛውን የጣና ፎረም በንግግር የከፈቱት የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲዊ ሪፖብሊክ ፕረዚደንት ወ/ሮ ሳሀለወርቅ ዘውዴ ናቸው፡፡
ሶማሊያ ባለፉት 20 ዓመታት በቀውስ ውስጥ እንደነበረች የጠቀሱት የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሳ ፋቂ ማህማት ሂደቱ አዝጋሚ ቢሆንም ለውጦች እየመጡ እንደሆነአብራርተዋል፡፡  በሶማሊያ የአፍሪካ ህብረት ጦር (AMISOM) ህይወት ጭምር እየከፈል በሶማሊያ ጉልህ ውጤት አስመዝግቧልም ብለዋል፡፡
ማህማት ይህን ይበሉ እንጂ በጅኦርጅ ዋሽንግተን ዩኒቨርሲቲ የዓለም አቀፍ ጥናቶች ረዳት ፕሮፌሰርና የደህንነት ፖሊሲ ጥናቶች ተባባሪ ዳይሬክተር ፖል ዊሊያምስ አሚሶም በሶማሊያ በሶስት ጉዳዮች ምክንያቶች ውጤታማ አይደለም፡፡የመጀመሪያው የሶማሊያ ፖለቲከኞችና ሊህቃን አገራቸውን እንዴት ማስተዳደር እንዳለባቸው የጋራ ስምምነት የላቸውም፣ ይህ ደግሞ በአገሪቱ ጠንካራ ብሔራዊ የጦር ኃይልና የፖሊስ ሰራዊት መፍጠር አላስቻላቸውም ይላሉ፡፡

Logo Tana High-Level Forum on Security in Africa
Tana Forum
ምስል DW/A. Mekonnen


ሌላው በሶማሊያ ዘላቂ ሰላም እንዳመጣ ያደረገው አሚሶም ወታደር በአገሪቱ ውስጥ ማሰማራቱ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ወታደር በአንድ አገር ውስጥ መረጋጋት ማምጣት አይችልም ይህን ማድረግ ሚችለው ፖሊስ ነው፡፡ የፖሊስ ሰራዊት በአገሪቱ ለማሰማራት ቢታሰብ በሶማሊያ ያለው አስቸጋር ሁኔታን በመፍራት አገራቱ ፖሊስ ወደ ስፍራው ለመላክ ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡
የአቅም ጉዳይ ሌላው ለአሚሶም ፈታኝ ሁኔታ ፈጥሮበታል፣ የተዋጊ ሄሊኮፕተር እጥረት፣ የህክምና ቁሳቁስ አለመሟላት፣ የወታደራዊ ምህንድስናና የደህንነት ሥራዎች ውጤታማ አለመሆንና አጠቃላይ የሎጅስቲክስ አለመሟላት ለአልሸባብ የግንኙነት መረብ መስፋትና ዋና ዋና ጎደናዎችን አንኳ መጠበቅ ተስኖት አሚሶምን በራሱ ካምፕ ብቻ ታጥሮ እንዲኖር አድርጎታል ነው ያሉት፡፡
በመሆኑም መፍትሄው በሶማሊያም ይሁን በሌሎች የምስራቅ አፍሪካ አገሮች ያለውን ችግር ለመፍታት አፍሪካውያን ራሳቸው መስማማትና መተባበር አለባቸው እንደ ፖል ዊሊያም፡፡
በዚህ ጉዳ ላይ በግብጽ የሳዳት ሲቲ ዩኒቨርሲቲ ፕረዚደንት ፕሮፌሰር አሕመድ ባዮኒም ይስማማሉ፡፡ አፍሪካን ካለችበት ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለማላቀቅ በሁሉም ረገድ የቀጠናው አገሮች ተባብረው መስራት ያስፈልጋቸዋል፡፡

ዓለምነው መኮንን

ነጋሽ መሐመድ