1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጠቅላይ ሚኒስትሩ የእራት ግብዣ ከእስር የተፈቱ ጋዜጠኞች የትግራይ ተቃዋሚ ፓርቲ ጥያቄ

ዓርብ፣ ጥር 13 2014

ወዳጄ ... የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከብርሃን በበለጠ ፍጥነት ነው የሚለዋወጠው። "ዘላቂ ወዳጅ እንጂ ዘላቂ ጠላት ብሎ ነገር የለም!" የሚሏት ፈሊጥ በጦቢያ የትርምስ ፖለቲካ ውስጥ ስር የሰደደች መርህ ናት። እናም ይህንን ዜና ጠብቀህ ካልነበር አንተ በእውነት የዋህ ነህ።

https://p.dw.com/p/45vkS
Social Media Apps | WhatsApp Facebook Twitter Instagram
ምስል Nasir Kachroo/ZUMA Press/imago images

የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ቅኝት

የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ቅኝት የጠቅላይ ሚኒስትሩ የእራት ግብዣ፤ የትግራይ ተቃዋሚዎች ጥያቄ እና የጋዜጠኞች መፈታት በሚል አስተያየቶችን አሰባስቦአል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ  ወደ ሀገርቤት አካል በሆነው በታላቁ ቤተ-መንግሥት የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት  ላይ ያደረጉት ንግግር በመጀመርያ አስተያየቶችን ያሰባሰብንበት ነጥብ ነዉ። ጠቅላይ ሚኒስትር ካነስዋቸዉ ሃሳቦች መካከል የምንወስናቸው ውሳኔዎች ኢትዮጵያን ያስቀደመ፤ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ሊረዳ ይገባል የሚለዉ ከተናገሩዋቸዉ ሃሳቦች መካከል ይገኛል።

ናርዶስ ሰብስቤ የተባሉ የፌስቡክ ተከታታይ፤ ትላንትም፣ ዛሬም ነገም አብረንህ ነን። ብዙ ግራ የሚገቡኝ ነገሮች አሉ። በእርግጥ አንተ ያለህበትን አንዱንም ነገር እኔ አላውቅም አንድ ነገር ግን የማልጠራጠረው ኢትዮጵያን መውደድህንና ኢትዮጵያን ወደ ብልፅግና ለማምጣት ቀንና ለሊት መድከምህን ነው። በአደባባይ ስሙን ስትጠራ ያላፈርክበት እግዚአብሔር የልብህን መሻት ይስጥህ።  የእጅህንም ስራ ይባርክልህ።  እንደ ሰለሞን ይሄን ህዝብ የምትመራበትን ጥበብና እውቀት በፊቱ የምትቆምበትን ሞገስ ይስጥህ፤ ሲሉ በምርቃት ይደመድማሉ።

ይንገስ አላምረዉ የተባሉ ሌላዉ የፊስ ቡክ ተከታታይ በጻፉት አስተያየት፤ መሬት ላይ እየተፈፀመ ያለውን በዓይናችሁ የምታዩትን ብቻ እመኑ። ባለፉት ሦስት ዓመት ብቻ በአገሪቱ እጅግ ዘግናኝ የሆኑ በደሎች ደረሰዎል ሊቆምም አልቻለም ።ጭራሽ ምንም እዳልተፈፀም ሰው በአዳራሽ ይዎሻል። ስለዚህ በዓይን የማየዉን ብቻ ነዉ የማምነዉ። የምሰማዉን አለምንም በቃ መባል አለበት ሲሉ በቃል አጋኖ አስተያየታቸዉን ደምድመዋል። ዜድ ላቭ የተባሉ የፌስቡክ ተከታታይ ዶ/ር አብይ ይለያል መሪም አስተማሪም ተዋጊም መካሪም የኢትዮጵያን ህልውና እየጠበቀ ነው በአዲስ አስተሳሰብና አመራር እንጂ በአረጀ ወይንም በጨረጨሰ አመለካከት ሀገር እንደማይመራ እና እንደማይለወጥ እያሳያን በምላስ ብቻ ሳይሆን በተግባርም እየተገበረልን ያለ ድንቅና ታታሪ መሪያችን አብቹ አንተ መሪዬ ስለሆንክ ያነተ ተመሪ ስለሆንኩ በጣም ደስተኛ ነኝ በርታልን ህልምህም እንደሚሳካ እርግጠኛ ነኝ ብለዋል።

ዶ/ር ዐቢይ እኔም በእስረኞች መፈታት በጣም ልቤ አዝኖ ነበር ሲሉ አስተያየታቸዉን የሚጀምሩት ፅጌሬዳ ተበጀ፤ የተባሉ የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ተከታታይ ናቸዉ። በእስረኞች መፈታት አዝኜ ነበር ግን ለመልካም ይሆናል እያልኩ እራሴንም አጽናና ነበር።ከንግግሮት እንደተረዳሁት ዳያስፖራው ዘረኝነትን እንዲጸየፍ አሳስበዋል። እርስዎንም በአክብሮት የምለምኖት መንግስት የአማራ፤የኦሮሞ፤ የትግሬ ክልል የሚለውን ስያሜ በህግ እንዲቀር እንዲያውጁልን ነው።  አንቀጽ 39ንም እንዲሰርዙልን ነው። በብሄር የተመሰረተ አገዛዝ ነው ኢትዮጵያን ያስበላብን። ለምን ለዚህ ውሳኔዎ ዘገዬብን? ኢትዮጵያን ያድኑልን:: እግዚአብሔር ይባርክዎ ሲሉ አስተያየታቸዉን ደምድመዋል።

ሱራፊል ተፈራ በበኩላቸዉ፤ ከእኛ በላይ እግዚአብሔርን ስለምትሰማ ደስ ብሎኛል። እስክትናገር ብዙ ይባላል ከተናገርክ በኃላ ልባችንን ተረጋግቷል። ንግግርህን እስከመጨረሻው ሰምቼዋለው ጠቢብ መሪ መሆንህን አረጋግጫለው። ምንም አድርግ አትራፊ ነህ ይሔንን በተግባራ አሳይተህናል ደስ ብሎናል መሪያችን ብለዋል።

ሚሻኤል አበበ የተባሉ የፌስቡክ ተከታታይ፤ ይገርማል እኮ ... ሲሉ አስተያየታቸዉን ይጀምራሉ። ከዚህ ሁሉ አጨብጫቢ ዲያሰፓራ ተብዬ ስንቱ ነው የዐብይ ንግግር ገብቶት የሚያጨበጭበው? ዘመናዊ ነን ባዮች ከሆናችሁ ዐብይን በተግባሩ ወይም በአመጣው ውጤት ለኩት በወሬና ሰብከት በቻ አትዘናጉ። ይህ መልክት ለጥቅም የተጉዋዙትን አይጥቅምም፤ ሲሉ ነዉ አስተያየታቸዉን የደመደሙት።

ከቴዎድሮስ ታደሰ የተባሉ የፌስቡክ ተከታታይ ወዳጄ አስተያየታቸዉን ሲጀምሩ ወዳጄ ... የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከብርሃን በበለጠ ፍጥነት ነው የሚለዋወጠው። "ዘላቂ ወዳጅ እንጂ ዘላቂ ጠላት ብሎ ነገር የለም!" የሚሏት ፈሊጥ በጦቢያ የትርምስ ፖለቲካ ውስጥ ስር የሰደደች መርህ ናት። እናም ይህንን ዜና ጠብቀህ ካልነበር አንተ በእውነት የዋህ ነህ። ብትችል ለሚሆነው ብቻ ሳይሆን ለማይሆነውም ተዘጋጅ። ነገ ደሞ "ዕርቅና ምህረት" በሚል ደብረፂዮን የማዕድንና ምናምን ሚኒስትርነት ሆኖ "አገራችን ኢትዮጵያ በዘንድሮ የበጀት ዓመት ... " የሚል መግለጫ በ ETV ሲሰጥ ልታየው ትችላለህ። ጌታቸው ረዳንም በኢትዮጵያ ፖርላማ ውስጥ በተወካይነት ገብቶ ስለፌዴራሊዝም ሲያብራራ ልታየው ትችላለህ።  አስቀድመህ እንዲህ ራስህን ስታዘጋጅ ብቻ ነው ተከትሎ ከሚመጣ የጨጓራ ህመም የምትድነው። በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወደ 80 ሺ ወጣት ሕይወት ተቀጥፏል። ከዚህ መራር እና ትርጉም አልባ ግጭት ሃያ ዓመት በኃላ ኢትዮጵያና ኤርትራ እንደአዲስ በፍቅር ክንፍ ሲሉ አይተናል። በሸገር ጎዳናዎች ላይ "ኢሱ ! ኢሱ ! " ተብሏል። አስመራ ላይ ዐብቹ "ፏ ! ብትን !" ብሎባታል። በቅርቡ ሸገር ወይም አስመራ ላይ  "ደፂ ! ደፂ !" የሚል ነገር ላትሰማ  ትችላለህ ። ግን ከሆነ ዓመት በኃላ የሆነ ተመሳሳይ ዐይነት ነገር የሆነ ቦታ ላለማየት ዋስትና የለህም ?! ይህ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ነው።

Symbolbild I BigTech I Social Media
ምስል Jakub Porzycki/NurPhoto/picture alliance

የትግራይ ተቃዋሚዎች የሽግግር መንግስት ምስረታ ጥያቄ

በትግራይ የሽግግር መንግስት እንዲመሰረት ሁለት በትግራይ የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች መጠየቃቸዉ ከወደ ትግራይ ሰሞኑን የተሰማ ዜና ነዉ። በትግራይ የሚንቀሳቀሱት ሳልሳይ ወያነ ትግራይ እና የትግራይ ነፃነት ፓርቲ የተሰኙ እነዚህ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ህወሓት በስልጣን እንዲቀጥል የሚያስችል የሕግ አግባብ የለም ባይ ናቸዉ።

ቴድሮስ ወርቁ የተባሉ የፌስቡክ ተከታታይ ፤ ትግራይ ውስጥ ተቃዋሚ ፓርቲ ቢኖር ኖሮ ጦርነቱ አልቆ ነበር። የህውሃት ተቃዋሚ ነን ብለው ተመስርተው ህውሃት ሲጎዳ ስቅስቅ ብለው የሚያለቅሱ ፓርቲዎች ነን ባዮች እራሳቸው ህውሃት ናቸው። ሲሉ አስተያየታቸዉን ይደመድማሉ። ኑራ ማጎኞ የተባሉ የፌስቡክ ተጠቃሚ የተጋሩን አንድነት ለመሸርሸር የተደረገ ተራ ፓለቲካ ነው። ትግራይን እንዴት እንደሚያስተዳድሩ እነርሱ እራሳቸው ያውቃሉ። ትግራይን መሽወድ አይቻልም ሲሉ አስተያየታቸዉን ጽፈዋል። ጀማል ሃሰን በበኩላቸዉ አጀንዳ አትለውጡ በላቸው ወንጀለኞችን ያቅርቡ ቅድሚያ የሃገሪቷን መንግሰት በሃይል ለመጣል የሄዱበትን በህግ ወይም በሌላ መፍትሄ እሰከለተገኘ ድረስ ምንም ማድረግ አይችሉም ፤ ይልቅ ተባባሪ ከመሆን ይቆጠቡ ሲሉ አስተያየታቸዉን ይደመድማሉ።

ብሌን አስፋዉ የተባሉ ሌላዋ አስተያየት ሰጪ ሲጀመር ትግራይ ተቃዋሚ የላትም ሲቀጥል እነኝህ የተባሉ ድርጅቶች የትግራይ ብልጽግና እንደሆኑ ይታወቃል። ከነዚህ ምንም አይጠበቅም። የትግራይ ህጻናት በመድሃኒት እጥረት እንደ ቅጠል እየረገፉ የሽግግር መንግስት ማለት ቀልድ ነው። ሲሉ አስተያየታቸዉን ደምድመዋል።

ወዲ ጁንታ የተባሉ አስተያየት ሰጪ የስልጣን ጥም ያላቸው ስለሆኑ ወደ ብልፅግና ቢጠጉ ሃሳብ ብንሰጣቸው ጥሩ ነው። ትግራይ ግን 100%ተቃዋሚ ፓርቲ የላትም ብለዋል። 

የጋዜጠኞች ከእስር መፈታት ጥያቄ

የጋዜጠኞች መታሰር በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ሲያነጋግር የሰነበተ ጉዳይ ነዉ። ከቀናቶች በፊት ጋዜጠኛ መዐዛ መሐመድ ከእሥር መለቀቋን ወንድሟ አቶ የሱፍ መሐመድ አረጋግጦአል። ጋዜጠኛ ኢያስፔድ ተስፋዬ መፈታቱን ኡቡንቱ ቲቪ በትዊተር ገፁ አብስሮአል። የጋዜጠኛ ታምራት ነገራ እንዲፈታ እየተጠየቀ ነዉ።

መርሻ ተሰማ የሆኑ የፌስቡክ ተጠቃሚ ፍትህ የባለስልጣናት የበዓል ገጸ በረከት ወደመሆን ወርዶ ሰዎች በሀሳባቸው ብቻ ታስረው የበዓል ማግስት በምሽት ይለቀቁልናል ሲሉ አስተያየታቸዉን ደምድመዋል። ሲስ ቦስ በፃፉት አስተያየት ጀግናው  ጋዜጠኛ ታምራት ነገራን ፍቱት።  እንደሱ አይነት ደፋር ጋዜጠኛ 10 ቢኖረን ኖሮ ኢትየዮጵያ ከዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ ትድን ነበር ሲሉ ጽፈዋል።

Symbolbild Indien Twitter
ምስል Diptendu Dutta/AFP

ዳግም ወ ታደሰ የተባሉ ደግሞ አሁን  እኛ ሀገር ችግር የሆነው መናገርና መፃፍ መከልከል ሳይሆን ማንንም ቲፎዞ ለመሰብሰብና በሰበቡ "ለመክበር" ለሚፅፈዉና ለሚናገረው ገደብ አለማድረጉ ነው። አብዛኞቹ "እሰሩኝ" ብለዉ አፍ አዉጥተዉ መጠየቅ ነው እኮ የሚቀራቸው፤ ሲሉ አስተያየታቸዉን አስቀምጠዋል። የኢትዮጵያ ሰላም ሲረጋገጥ የምትፈልጉት ትፅፋላቹ ። አሁን ግን አገራችሁ የምትፈልገውን ብቻ ስጧት ሲሉ አስተያየት የፃፉት ሙኒር አብዶ ናቸዉ። ዮሲ በሃይሉ ፤ የተባሉ የፌስ ቡክ ተከታታይ ፤ ጋዜጠኞች እንደፈለጉ መጻፍ አገርን አደጋ ላይ እንደሚጥል ማወቅ አለባችው። ምክንያቱም ለመናቆር ሰበብ የምንፈልግ ሰዉች ነን። የሰለጠኑ ህዝቦች ለምን እንዴት ወዴት የሚለው ያመዛዝናሉ። እኛ በዘር የተከፋፈልን ህዝቦች ነን ጥንቃቄ ያስፈልጋል ባይ ናቸዉ። ሚሚ ኦርያም ክ የተባሉ የፊስ ቡክ ተጠቃሚ መአዚ ለተገፉ ለተበደሉ ድምጽ የሆነች። ባለስልጣናትን ሳይሆን ተበዳዮችን እየተከተለች አብራ እያነባች ፣እያጽናናች መከራቸውን የተካፈለች ትንታግ ጋዜጠኛ ነችና ክብር ይገባታል። እንኩዋንም እግዚአብሔር ጣልቃ ገባና ለቤትሽ በቃሽ።

ሙሉ ዝግጅቱን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ

 

አዜብ ታደሰ\

ሸዋዬ ለገሠ