1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የግብፅ እልቂትና ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 14 2005

ግብፅ ጥይት፥ አረር፥ እየዘራች፥ አስከሬን-አጭዳ በእሳት ትጋያለች።ያቺ አስከሬን ለዝንተ-ዓለም የሚቀመጥባት ሐገር ዛሬ የሰዉ አካል ይተለተልባታል።ያቺ የጥንታዊ ሥልጣኔ ጎተራ፥ ያቺ የታሪካዊ የቅርስ ቋት፥ ያቺ ሥልታዊት ሐገር ታወረች? ወይስ አበደች? እዉሩ ወይም እብዱስ ማነዉ?

https://p.dw.com/p/19SQD
epa03829974 Egyptians supportig ousted president Morsi take part in a gathering called for by the Muslim brotherhood in Giza, Egypt, 18 August 2013. The Muslim brotherhood had on 17 August called for new protests against the ousting of president Morsi. On 18 August afternoon, local media reported their cancelation for the one planned in Roxy located in the Heliopolis area of Cairo, but it was not clear yet whether all the other marches have been canceled.Army chief and Defence Minister Abdel-Fattah al-Sissi has warned Morsi's supporters to refrain from 'destroying the country and or the torching the nation and terrorizing the citizens. EPA/AHMED ASSADI
አደባባዩ-መቃወሚያም መገድያምምስል picture-alliance/dpa

የግብፅ ጦር ዘመን ባፈራዉ ዘመናይ ጦር መሳሪያ መግደል፣ መደብደብ ማሰሩን፣ ሙስሊም ወንድማማቾች እምነት፣ቁጭት ና እልሕ በወለደዉ ፅናት መፋለሙን እንደቀጠሉ ነዉ።የዘመኑ ፈርዖኖች ፍሊሚያ የፈረዕኖቹን ዉልድ እየፈጀ፣ የፈርዖኖቹን ታሪካዊ፣ ሥልታዊት ሐገርን እያወደመ-ቁል ቁል ያንደረድራታል።የጥፋት ዉድመቱ ሒደት፣ ዉጤት መዘዝ አረብ አይሁድን፣ አፍሪቃ እስያን፣ ከሁሉም በላይ አዉሮጳ አሜሪካን እያሳሰበ ግን አቋማቸዉን እያዋዠቀ ነዉ።የግብፅ እልቂት-ዉድመት መነሻ የሁለቱ ፈርዖኖች ደምሳሳ ቅኝት ማጣቀሻ፣ የተቀረዉ ዓለም አቋም መድረሻችን ነዉ ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ።

ግብፃዊዉ ታዳጊ መሐመድ ገማል አይ ፒ ኤስ በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ ዜና አገልግሎት እንደዘገበዉ ዘንድሮ አስረኛ ዓመቱ ነዉ።ሲወለድ ጀምሮ አይነ-ስዉር ነዉ።እናት ዲና ገማል ግን «ልጄ አካለ ጎደሎ አይደለም።» ይላሉ።«ልጄ አይደለም በጨለማ ዉስጥ የሚኖረዉ።የግብፅ ማሕበረሰብ አንጂ።ዓይን አላቸዉ ግን ከልጄ እኩል ማስተዋል አይችሉም።» እያሉ ቀጠሉ የአይነ-ሥዉሩ ልጅ እናት።

አብደል በድሪም ግብፃዊ ናቸዉ።አሳ አጥማጅ።የሐምሳ-ዓመት ጎልማሳ።ከትናንት በስቲያ ቅዳሜ እንዳሉት ለሳቸዉ እና በሚሊዮን ለሚቆጠሩ የካይሮና ያካባቢዉ ነዋሪዎች በተለይ ካለፈዉ ሮብ ወዲሕ «እየዬም ሲዳላ ነዉ።» አይነት በግብፅ ጦር የተገደለ ዉላጅ-ተወዳጅ፥ ዘመድ፥ወዳጅን አስከሬንን አግኝቶ አልቅሶ መቅበር በርግጥ መታደል ነዉ።

«የቅርብ ጓደኛዬ እዚያ (ራባ-አል አደዊጃ) ተገደለ።አስከሬኑን በእሳት አጋዩት።ሞኖፊያ አዉራጅ የምትገኝ የአዲት ትንሽ መንደር ተወላጅ ነኝ።ከኛ ቀበሌ እና ከያንዳዱ አጎራባቾቻችን ቀበሌዎች ቢያንስ ሁለት ሠዉ ተገድሏል።»

ግብፅ ጥይት፥ አረር፥ እየዘራች፥ አስከሬን-አጭዳ በእሳት ታጋያለች።ያቺ አስከሬን ለዝንታ-ዓለም የሚቀመጥባት ሐገር ዛሬ የሰዉ አካል ይተለተልባታል።ያቺ የጥንታዊ ሥልጣኔ ጎተራ፥ ያቺ የታሪካዊ የቅርስ ቋት፥ ያቺ ሥልታዊት ሐገር ታወረች? ወይስ አበደች? እዉሩ ወይም እብዱስ ማነዉ? ጄኔራል አብዱል ፈታሕ አል ሲሲ፥ ወይስ መሐመድ ባድይ።መሐመድ ሙርሲ ወይስ ዓድሊ መንሱር? አናዉቅም።

ያዩ ግን ያዩ የሚያዉቁትን-ይነግሩናል።ሮይተር ዜና አገልግሎት እንደዘገበዉ ግን የካይሮ ሆስፒታሎች የአስከሬን ማስቀመጫዎች ከአፍ እስከ ገደፋቸዉ ሥለሞሉ ከየአየደባባዩ የሚለቀመዉ የሰዉ አካል ቁርጥራጭ፥ እና አስከሬን በየመሳጂዱ ታጭቋል።እና ለገሚስ ግብፆች የሟች አስከሬን አግኝቶ፥ አልቅሶ መቅበር ዛሬ መታደል ነዉ።

የአስር ዓመቱ አይነ-ሥር ወጣት የሐገሩን ምሥቅልቅል ለማወቅ ዓይኑ ሳይሆን ዕድሜዉ በርግጥ አይፈቅድለትም።ሙዚቃ ይወዳል።በልዩ ኮምፒተሩ እየታገዘ ድረ-ገፆችን ማገላበጥ ይችላል። ፊደላት እየደረደረ ቃላት፥ ቃላት እየገጣጠመ ዓረፍተ-ነገራት ይሠራል።እንደማንኛዉም ሕፃን «ስታድግ ምንድ ነዉ መሆን የምትፈልገዉ?» ተብሎ ሲጠየቅ ፈጥኖ ይመልሳል።«ጋዜጠኛ ብሎ።»

የጋዜጠኞቹ ታሪክ።ቅዳሜ ነዉ።ወደ አስከሬን ማከማቻነት ያልተቀየሩት መስጊዶች ወደ መሸሸጊያነት ተለወጡ።የአልጀዚራዉ ጋዜጠኛ ካይሮ መስጊድ ዉስጥ የነበረች ረዳቱን ወይም መረጃ አቀባዩን በሥልክ ጠየቃት።ምን እየሆነ ነዉ-የመጀመሪያዉ ጥያቄ ነበር።

«ባሁኑ ጊዜ ወደ መስጊዱ ዉስጥ እየተኮሱ ነዉ።»

«ከኛ ጋር ለመነጋገር-እንዴዉ ለመሆኑ ደሕና ቦታ ነሽ?»

«በጭራሽ፥ በጭራሽ እዚሕ መስጊድ ዉስጥ ማንም ሰዉ ዋስትና የለዉም። እየተኮሱብን ነዉ።ተኮሱ።-----»

የዋሁ አይነሥዉር ሕፃን-እናቱ «ዓይን እያለዉ የታወረ ባለችዉ ሐገር ጋዜጠኛ መሆን ይፈልጋል።

የፆም ፀሎት ማዘዉትሪያ ቅዱሳን መስጊዶች፥ከቅድሱ ኢድ አልፈጢር በሕዋላ፥ ከሸዋል ኢድ ዋዜማ ጀምሮ አንድም ወደ አስከሬን ማከማቻነት፥ አለያም ወደ ሰዎች መግደያ ቄራነት ተለዉጠዋል። ለወትሮዉ በፍልሰታ ጷሚዎች የሚጨናነቁት፥ የፈጣሪ መማፀኛ ቅዱስ አቢያተ-ክርስቲያናት ይጋያሉ። አደበባዮች፥ የሰላማዊ ሠልፍ ማዕከላት የነበሩ አደባባዮች በተቦጫጨቀ፥ የሰዉ አካል፥ በሰዉ ደም ጎድፈዋል።በንዳጅ ቀርንተዋል።

የቀድሞዉ ፕሬዝዳት መሐመድ ሙርሲና መንግሥታቸዉ የሚጠበቅባቸዉን ያሕል አለመስራታቸዉ፥ ባለመስራታቸዉ የሕዝብ ተቃዉሞ የገጠማቸዉ መሆኑ ይታወቅ ነበር።ሙርሲ እና የሙርሲን የፖለቲካ ማሕበር የነፃነት እና የፍትሕ ፓርቲን የወከሉት የምክር ቤት አባላት በታሪካዊቱ ሐገር የምዕተ-ዓመታት ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሕዝብ ድምፅ መመረጣቸዉ ግልፅ ነዉ።

የነፃነት እና የፍትሕ ፓርቲ-የሙስሊም ወንድማማቾች ማሕበረሰብ የፖለቲካ ክንፍ መሆኑም እርግጥ ነዉ።የሙስሊም ወንድማማቾች ማሕበረሰብ ወይም የነፃነትና የፍትሕ ፓርቲ አባላት ሥልጣን ላይ በነበሩበት አንድ ዓመት ጊዜ ተቃዋሚዎቻቸዉ የሚተቹ፥ የሚወቅሷቸዉን ያክል በሕዝብ ድምፅ የተመረጡ የግብፅ መሪዎች ነበሩ።

ኮሎኔል ገማል አብድናስር የመሯቸዉ የግብፅ የጦር መኮንኖች ንጉስ ፋሩቅን ከሥልጣን አስወግደዉ ሥልጣን ከያዙበት ከ1952 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ጀምሮ ሙርሲ እስከተመረጡበት ጊዜ ድረስ የግብፅ ጦር ከስልጣን ተለይቶ አያዉቅም።የግብፅ ሁለንተናዊ ሒደት በያኝም ነዉ። አንድ የፖለቲካ ተንታኝ ጦሩን የተቋማት ሁሉ የበላይ ተቋም ይሉታል።

ጀርመናዊዉ የፖለቲካ ተንታኝ ሽታይንባሕ እንደሚሉት ደግሞ ፕሬዝዳት ሆስኒ ሙባረክ በተወገዱ ማስግሥት ሥልጣኑን የወረሱት ፊልድ ማርሻል ተንታዊ እና ጄኔራል አልሲሲን የመሳሰሉ ተከታዮቻቸዉ ጦሩ የፖለቲካ ሥልጣኑን ቢያጣ እንኳን ምጣኔ ሐብቱን እንደያዘ ግብፅን እንደተቆጣጠረ ይቀጥላል የሚል ተስፋ-እምነትም ነበራቸዉ።

«ጦሩ ምጣኔ ሐብቱን እና ማሕበራዊዉን መስክ እንደተቆጣጠረ ለመቀጠል ትልቅ ፍላጎት ነበረዉ ማለት ይቻላል።ጦሩ በሐገሪቱ ምጣኔ ሐብት ትልቅ ተሳትፎ ካላቸዉ ሐይላት ግንባር ቀደሙ ነዉ።ይሕንን አጡት።ሙርሲ የያኔዉን ማርሻል ታንታዊን ስልጣን ሲያስለቅቁ ጦሩ የሚፈልገዉን አጣ።»

በናስር እምነት፥ አላማ ከተቀረፁት አዳዲሶቹ ናስሮች ወይም ፈርዖኖች ጄኔራል አብዱል ፈታሕ አል ሲሲ ብቸኛዉ ፈርዓንነታቸዉን ለማረጋገጥ አስር ወር ጠብቀዉ፥ ተቃዉሞን ተተግነዉ ፕሬዝዳት መሐመድ ሙርሲን በሐይል ከስሥልጣን አስወገዱ።ነሐሴ-ሰወስት።አል-ሲሲ ሕገ-መንግሥት ሽረዉ፥ ምክር ቤት ዘግተዉ፥ ሌላ መሪ ሲሾሙ እኒያ በግብፅ ሕዝብ ተመርጠዉ ግብፅን ሲመሩ የነበሩት ወገኖች በሕዝብ የተጠሉ፥ ግብፅን ለዉድቀት የዳረጉ ሙስሊም ፅንፈኞች ተብለዉ ተወነጀሉ።ታሠሩ። ተገደሉም።

ለሙስሊም ወድማማቾች ግን አዲስ ነገር አይደለም።ሼኽ ሐሰን አሕመድ አብዱረሕማን መሐመድ አል-ባና በ1928 ሲመሠርቱት የብሪታንያ ቅኝ ገዢዎችን የሚቃወም፥ የሙስሊሞችን ሐይማኖት፥ የአረቦችን ባሕል የሚጠብቅ፥ ድሆችን የሚረዳ ማሕበረሰብ ነበር።ባጭር ጊዜ ዉስጥ በርካታ አባላት አሰባስቦ፥ በ1936 የፍልስጤሞችን የነፃነት ጥያቄ ለመጀመሪያ ጊዜ በአደአደባባይ ሠልፍ ለዓለም ሲያሳዉቅ ሠልፈኛዉ በብሪታንያ ቅኝ ገዢዎች ጦር ተደፈለቀ።

በ1948ቱ የአረብ እስራኤሎች ጦርነት ወቅት አባላቱን አዝምቶ እሲኪዋጋ ድረስ ከግብፁ ንጉስ ፋርቁ መንግሥት ጋር ወዳጅ ባይሆኑ ጠላት አልነበሩም።የጦርነቱ ሽንፈት ያስቆጣዉ ግብፃዊ የንጉሱን ሥርዓት እየተቸ ሙስሊም ወድማማቾች ማሕበረሰብን ማሞጋገስ ሲጀምር ፋሩቅ ማሕበረሰቡን አገዱ።ንብረቶቹን ወረሱ።አብዛኛ መሪዎቹን አሠሩ።

የፋሩቅን አገዛዝ በተለይም በሙስሊም ወድማማቾች ላይ የተወሰደዉን የሐይል እርምጃ የሚቃወም አንድ ተማሪ ጠቅላይ ሚንስትር መሐመድ አን ኑክራሺ ፓሻን በጥይት ደብድቦ ገደላቸዉ።ወዲያዉ የሙስሊም ወንድማማቾች መስሯችና የመጀመሪያዉ መሪ አል-ባና ባደባባይ ተረሸኑ።

ሙስሊም ወድማማቾች በድፍን የዓረብ አለም ተዘርቷል።ግን ንጉስ ለሚጠሉት በተለይ የሳዑዲ አረቢያ ገዢዎችን ለሚያወግዙት ለቀድሞዉ የሊቢያ መሪ ለኮለኔል ሙዓመር ቃዛፊም፥ ለንጉስ ፈሕድ ወይም ለንጉስ አብደላሕም እኩል ጠላት ነዉ።ናስር እና ተከታዮቻቸዉ የፋሩቅን መንግሥት ማስወገዳቸዉን ደግፎ ነበር።ናስር ሥልጣናቸዉን ካደላደሉ በሕዋላ የሙስሊም ወድማማቾች መሪ-አባላትን የሚገድሉትን ገድለዉ ሌላዉን በየእስር ቤቱ አጎሩ።

የአል-ቃኢዳ መስራች ኦስማ ቢላን የሙስሊም ወድማማቾችን መርሕ ያወግዝ ነበር ይባላል።የኦስማ ቢን ላንደን ቀንደኛ ጠላቶችን ዩናይትድ ስቴትስና እስራኤልም ሙስሊም ወድማማቾችን ይቃወማሉ። በዚሕም ይሁን በሌላ ምክንያት ጄኔራል አል ሲሲ የመሩትን መፈንቅለ መንግሥት ያወገዘ ቀርቶ «መፈንቅለ መንግሥት» ለማለት እንኳን የደፈረዉ አፍሪቃ ሕብረት ብቻ ነዉ።

የግብፅ ጦር መፈንቅለ መንግሥቱን የተቃወሙ የሙስሊም ወንድማማቾችን አባላትና ደጋፊዎችን በጅምላ ሲያስር፥ አምስት፥ አስር፥ ሃያ፥ ሠላሳ እያለ ሲገድል ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች መጮኸቸዉ አልቀረም።አንዳድ የሐያሉ ዓለም ፖለቲከኞች ጥንቃቄ እንዲደረግ መጠይቃቸዉ ካይሮ እየደረሱ መመለሳቸዉም እዉነት ነዉ።የጀርመኑ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጊዶ ቬስተርቬለ ባለፈዉ ሳምንት ያሉትን ከሳምንታት በፊት ብለዉት ነበር።

ከዚሕ ባለፍ በገዳዮች ላይ ቆንጣጭ እርምጃ ለመዉሰድ የሞከረ፥እንዲወሰድ የጠየቀ ሐያል መንግሥት የለም።ጋዜጣኛዉ አዉቆም፥ የሚያዉቁ በትክክል ያሉት እየመሰለዉም «ኢስላሚስት ወይም እስላማዉያን፥ ሙስሊማዉያን» የሚላቸዉ ሙስሊም ወንድማማቾች ከሥልጣን በመወገዳቸዉ የሙስሊሞች የበላይ ጠባቂ ከሚባሉት ከሳዑዲ አረቢያ ገዢዎች እኩል የተደሰተ የለም።

የሳዑዲ አረቢያ፥ የባሕሬን፥ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ነገስታት፥ አሚሮች ወይም ሱልጣናት የሕዝብ አመፅ፥ ተቃዉሞንም፥ በሕዝብ የተመረጠ መንግሥትንም፥ በመፈንቅለ መንግሥት ሥልጣን የያዘ-የጦ መኮንኖችንም እኩል ይፈራሉ፥ ይጠላሉም።ጄኔራል አል-ሲሲ የሙስሊም ወድማማቾቹን መንግሥት በሐይል በማስወገዳቸዉ ግን ለግብፅ ጦር የአስራ-ሁለት ቢሊዮን ዶላር ርዳታ አስታቅፈዉታል።

የሳዑዲ አረቢያ ገዢዎችና ተባባሪዎቻቸዉ፥ ምናልባት ምዕራባዉያን ለግብፅ የሚሰጡትን ድጋፍ ቢያቋርጡ በሚጎድለዉ ለመሙላት ዛሬ ቃል ገብተዋል። ሐያሉ ዓለም ይሕን ያዉቃል። አልተቃወመዉም። አል-ሲሲ የሚያዙት ጦር ከአየር በሔሊኮብተር፥ ከፎቅ ባነጣጥሮ ተኳሽ፥ ከመሬት በታክ መትረየስ ሠላማዊ ሠልፈኞችን መግደሉን ፕሬዝዳት ባራክ ኦቦባ አዉግዘዋል።ዩናይትድ ስቴትስ በየዓመቱ ለግብፅ ጦር የምታስታጥቀዉን የአንድ ነጥብ ሰወስት ቢሊዮን ዶላር ጦር መሳሪያ ለማቆም ግን አልቃጡም።

ከመራሒተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል እስከ ፍራንሷ ኦሎንድ፥ ከጠቅላይ ሚንስትር ቶኒ ብሌር እስከ ካትሪን አሽተን የሚገኙ የአዉሮጳ መሪዎች ግድያዉን ተቃዉመዋል።በግብፅ ጦር ላይ ማዕቀብ ለመጣል ግን እስካሁን አንዳቸዉም አልደፈሩም።የአዉሮጳ ሕብረት የዉጪ ጉዳይ ሚንስትሮች ገና በጉዳዩ ላይ ለመምከር ለሮብ ቀጠሮ አላቸዉ።ግብፅ በርግጥ ዚምባቡዌ አይደለችም።

የእስራኤል ሠላም በካይሮ ደሕንነት ላይ የተመሠረተ ነዉ።ከአራት ከመቶ የሚበልጠዉ የዓለም ሸቀጣሸቀጥ፥ ከስምንት ከመቶ የሚበልጠዉ የዓለም ነዳጅ ዘይት የሚተላለፈዉ በሲዊስ ቦይ ነዉ።ሐያሉ ዓለም «ከመርሕ ወይም ከሞራል» ይልቅ «ጥቅም»ን አስቀድሞ ሲያለምጥ ያቺ ለጥቅሙ የሚጓጓላት ሐገር፥ የሚሳሳለትን ጥቅም ጨርሶ ወደሚያጣበት አዘቅት እንዳትደፋ በርግጥ ያሰጋል።

የግብፅ ገዢዎች ግን «ያበጠዉ-ይፈንዳ» አይነት እልሕ የተጋቡ ይመስላሉ።ዛሬ ከወደ ካይሮ እንደተሰማዉ በሕዝብ አመፅ ከሥልጣን የተወገዱት እና ፍርድ ቤት የተበየነባቸዉ ሆስኒ ሙባረክ እንደሚፈቱ ተዝግቧል። ጠመንጃ የታጠቁት ፈርዖኖች፥ እልሕና ፅናት ከሰነቁት ተቃዋሚዎቻቸዉ ጋር የገጠሙት ፍልሚያ እንደቀጠለ ነዉ።

ባለፈዉ ሮብ ናሕላ አደባባይ የጀመረዉ ግድያ መሳጂዶችን፥ አብያተ-ክርስቲያናትን፥ ወሕኒ ቤቶችን በደም፥ አካል፥ በእሳት ከሰል አልብሶ ድፍን ካይሮን አዳርሶ፥ አሌክሳንደሪያን፥ ኢስማኢሊያን፥ እያለ ዛሬ ሲና በረሐ-ወርዷል።ግብፅ ታዉራለች፥ ወይስ አብዳለች? ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

Reporters run for cover during clashes between Muslim Brotherhood supporters of Egypt's ousted president Mohamed Morsi, and police in Cairo on August 14, 2013, as security forces backed by bulldozers moved in on two huge pro-Morsi protest camps, launching a long-threatened crackdown that left dozens dead. The clearance operation began shortly after dawn when security forces surrounded the sprawling Rabaa al-Adawiya camp in east Cairo and a similar one at Al-Nahda square, in the centre of the capital. AFP PHOTO / MOSAAB EL-SHAMY (Photo credit should read MOSAAB EL-SHAMY/AFP/Getty Images)
ምስል Mosaab El-Shamy/AFP/Getty Images
REFILE - ADDING VERB Army soldiers react inside a room of al-Fath mosque when supporters of deposed Egyptian President Mohamed Mursi exchanged gunfire with security forces inside the mosque in Cairo August 17, 2013. The gunmen opened fire on security forces from a second floor window in the Fath mosque, where hundreds of Mursi supporters have been taking refuge since protests turned violent on Friday. REUTERS/Muhammad Hamed (EGYPT - Tags: POLITICS CIVIL UNREST RELIGION MILITARY TPX IMAGES OF THE DAY)
መስጊዱ-መግደያ ነዉምስል Reuters
A picture taken on August 18, 2013 shows the Amir Tadros coptic Church in Minya, some 250 kms south of Cairo, which was set ablaze on August 14, 2013. Egypt's Christians are living in fear after a string of attacks against churches, businesses and homes they say were carried out by angry supporters of ousted Islamist president Mohamed Morsi. As police dispersed Morsi supporters from two Cairo squares on August 14, attackers torched churches across the country in an apparent response. AFP PHOTO / VIRGNIE NGUYEN HOANG (Photo credit should read VIRGINIE NGUYEN HOANG/AFP/Getty Images)
ቤተ-ክርስቲያኑ ዉደመምስል AFP/Getty Images
Looters walk away with goods as smoke billows from the riot-hit Abu Zaabel prison in the Egyptian capital Cairo after a mass breakout by convicts amid a nationwide revolt on January 30, 2011. AFP PHOTO/STR (Photo credit should read -/AFP/Getty Images)
ሕንፃዉ-ይጋያልምስል AFP/Getty Images
A general view shows the Port Said prison in the Egyptian Suez Canal city on January 25, 2013. A court verdict is due on January 26 in the trial of dozens of defendants over the worst football disaster in Egyptian history. More than 70 people were killed in Port Said last February during clashes between fans of home side Al-Masry and diehard supporters of Cairo's Al-Ahly, known as Ultras. Al-Ahly supporters have warned of violent protests and a "new revolution" if the verdict goes against them. AFP PHOTO/STR (Photo credit should read STR/AFP/Getty Images)
እስር ቤትም-መግደያምምስል STR/AFP/Getty Images

ነጋሽ መሐመድ

ተክሌ የኋላ









ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ