1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጋና ፕሬዚደንት በአንድ ዓመት ሥልጣናቸው ምን ሠሩ?

ቅዳሜ፣ ኅዳር 30 2010

በጋና ለብዙ ዓመታት በሀገሪቱ ምክር ቤት የተቃዋሚነቱን ቡድን ይዞ የነበረው ቡድን መሪ ናና አኩፎ አዶ ፕሬዚደንት ሆነው ከተመረጡ ባለፈው ማክሰኞ፣ ህዳር አምስት፣ 2017 ዓም አንድ ዓመት ሆናቸው። ፕሬዚደንቱ በምርጫ ዘመቻ ጊዜ እፈጽመዋለሁ በሚል የገቡት ቃላቸው ዛሬ ከአንድ ዓመት በኋላ ምን ላይ ደርሷል?

https://p.dw.com/p/2p2p5
Afrika Ghana - Nana Akufo-Addo übernimmt das Amt des Präsidenten
ምስል Reuters/L. Gnago

መንግሥት የገባውን ቃል በተግባር ለመተርጎም እየሰራ ነው። 

በየወረዳው አንድ ፋብሪካ፣ ነፃ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት፣ ተጨማሪ የውጭ ባለሀብቶችን ወረት ወደ ሀገሪቱ መሳብ፣ ሙስናን መታገል። ይህን ሁሉ እንደሚያደርጉ ነበር ናና አኩፎ አዶ ከአንድ ዓመት በፊት ለሶስተኛ ጊዜ ለፕሬዚደንትነት በተወዳደሩበት ጊዜ ቃል የገቡት።  አኩፎ አዶ በፕሬዚደንታዊው ምርጫ ቀንቷቸው፣ ያኔ ስልጣን ላይ የነበሩትን ተፎካካሪያቸውን ጆን ድራማኒ ማሀማን 53% የመራጭ ድምፅ በማግኘት አሸንፈዋቸዋል። ድራማኒ ማሀማ 44% የመራጭ ድምፅ ብቻ ነበር ያገኙት።
ያኔ ታድያ ብዙ የጋና ዜጎች የአኩፎ አዶ ድል መቀዳጀት ጥሩ የልማት ሁኔታ ላይ ለማትገኘዋ ሀገራቸው አዲስ አነቃቂ  ጅምር ይሆናል ብለው  ተስፋ አድርገው ነበር። የኤኮኖሚ እድገቱ ወደ 3,6% ዝቅ ሲል፣፣ የዋጋ ግሽበቱ እና የስራ አጡ መጠን ግን በጣም ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሶ ነበር፣ ብዙ የጋና ወጣቶችም የተሻለ እድል ፍለጋም ሀገራቸውን ለቀዋል። እና በዚሁ ጊዜ ፕሬዚደንታዊው እጩ አኩፎ አዶ ለወጣቱ የስራ ቦታ ለመፍጠር የገቡት ቃላቸው የብዙዎችን ድጋፍ ሊያስገኝላቸው ችሏል።  
እርግጥ፣ ጋና ለአራተኛ ጊዜ በተከታታይ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ማድረጓ በዓለም አቀፍ ደረጃ አድናቆትን አትርፎላታል፣ ይሁንና፣ ብዙዎች ትልቅ ተስፋ የጣሉበት አዲስ ጅምር እስኪነቃቃ ድረስ ብዙ መጠበቅ ነበረባቸው። ካቢኔ የመመስረቱ እና የመንግሥት ባለስልጣናትን የመሰየሙ ተግባር አዲሱን ፕሬዚደንት ወደ ስድስት ወር ገደማ ወስዶባቸዋል። 
ከዚያን ጊዜ ወዲህ ግን ፕሬዚደንት አኩፎ አዶ የሚመሩት መንግሥት  በምርጫ ዘመቻ ጊዜ የገባውን ቃል ቀስ በቀስ በተግባር ለመተርጎም እየሰራ ነው።  ካለፈው መስከረም ወር ወዲህ በጋና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ነፃ ሆኗል።  ሙስናንም ለመቀነስ ጥረቱን መጀመሩን መታዘባቸውን በጋና መዲና አክራ የሚገኘው ከጀርመናውያኑ የክርስትያን ዴሞክራቶች ህብረት፣ በምህፃሩ፣ ሴዴኡ  ፓርቲ ጋር ቅርበት ያለው   የኮንራድ አድናወር ተቋም የተባለው የፖለቲካ ጥናት ድርጅት ኃላፊ ቡርክሀርት ሄልማን አስታውቀዋል። ይሁንና፣ ሙስናን በተሻለ ሁኔታ ለመታገል ይቋቋማል የሚባለው አዲስ የልዩ መርማሪ መስሪያ ቤት ስልጣን ገና ግልጽ አለመሆኑን ሄልማን አክለው አመልክተዋል።
« በአስተዳደሩ ውስጥ ተፈጽሟል የሚባለውን ሙስና የሚመረምረው የመንግሥቱ ዓቃቤ ሕግ ገለልተኛነትን በየትኛው ባለስልጣን መስሪያ ቤት ስር ይሁን ወይም ትዕዛዙን ከማን መቀበል አለበት የሚሉት ጥያቄዎች መስሪያ ቤቱ በሚቀጥለው ጥር ወር ሲቋቋም መልስ ያገኛሉ። »
በትምህርቱ ዘርፍ መንግሥትያደረጋቸውን ለውጦች ሕዝቡ ቢያሞግስም፣ ርምጃዎችን ስራ ላይ ለማዋል ያደረገው ጥረቱ ታዛቢዎች እንደሚሉት፣ አንዳንድ እክሎች አላጡትም። ለምሳሌ፣ ትምህርት ቤቶች  ጉልህ ጭማሪ ላሳየው የአዳዲስ ተማሪዎች ቁጥር አልተዘጋጁም ነበር። ትምህርት ቤቶቹ  ብቃት ያላቸውን መምህራን እና በቂ የትምህርት መሳሪያ አላቀረቡም፣ ባንዳንድ ትምህርት ቤቶች እንዳውም ጠረጴዛ እና ወንበሮች እንኳን  ሳይቀር ተጓድሏል። ይህ ሁሉ የገቡትን ቃል መጠበቅ አዳጋች መሆኑን ለመንግሥቱ ግልጽ አድርጎለታል ይላሉ ሄልማን።
« የጋና መንግሥት በሀገሪቱ ሁኔታዎችን ለማስተካከል አዲስ ኃይል እና በጎ ፈቃድ ይዞ የተነሳሳ ይመስለኛል። ይሁን እንጂ፣ ያለፉት ስምንት ዓመታትን የተቃዋሚውን ሚና ይዞ የቆየው እና አሁን ስልጣን ላይ የወጣው ቡድን  ሀገር መምራት፣ በተቃዋሚነት ዘመኑ እንዳሰበው፣ ቀላል አለመሆኑን በኋላ ተረድቶታል። »
ቡርክሀርት ሄልማን እንደሚሉት፣ የጋናን መሰረተ ልማት ለማሻሻል የተያዘው የመንግሥቱን ዓላማ በተመለከተ በተጨባጭ  የተዘጋጀ እቅድ የለም። 
« እንደማስበው፣ አኩፎ አዶ በመጀመሪያው የስልጣን ዓመት ለህዝባቸው አንዳንድ ውጤቶች ለማቅረብ እንደሚችሉ ለማሳረጋገጥ ፈልገው ነበር። በምርጫ ዘመቻ ወቅት እንደሚፈጽሟቸው ቃል ከገቡዋቸው ጉዳዮች መካከልም  አነሰም በዛ አንዳንዱን በተግባር ለመተርጎም ዝግጁነታቸውን አሳይተዋል። ይህ አካሄዳቸው በብዙው የሀገሪቱ ሕዝብ ዘንድ፣ ቃላቸውን መጠበቅ መቻላቸውን በጥርጣሬ በተመለከቱት ዘንድ ጭምር፣ ተቀባይነትን አግኝቶላቸዋል። ለዚሁ የሚያስፈልገውን በጀት የማዘጋጀቱ ጉዳይ አሁን መልስ ያገኘ ይመስላል፣ ጥያቄው ግን የጋና መንግሥት በጀት ምን ያህል ጊዜ አስተማማኝ ሆኖ በዘላቂነት ይቀጥላል የሚለው ነው። ይህ በጎርጎሪዮሳዊው 2018 እና 2019 ዓም የሚታይ ይሆናል። »
ፕሬዚደንት ናኖ አኩፎ አዶ ከርሳቸው በፊት ከቀድሞው መንግሥት የተረከቡት ግዙፍ የውጭ እዳ የበመንግሥታቸውን ስራ አዳጋች አድርጎባቸዋል። የሀገሪቱን ኤኮኖሚ ማሳደግ እና ግብሩን ከፍ ማድረግ ጋናን ከምትገኝበት ችግር ለመውጣት የሚረዳ ጥሩ መፍትሔ በመሆኑ፣ የውጭ ባለሀብቶችን ወደ ሀገራቸው ለመሳብ  እንደ እውን መሆኑን ርዕሰ ብሔሩ ጠቁመዋል። ይህን እቅዳቸውን ባለፈው ሳምንት በፓሪስ ከፈረንሳይ ፕሬዚደንት ኤማኑዌል ማክሮ ጋር በተገናኙበት ጊዜ በድጋሚ አረጋግጠዋል።  ይሁንና፣ የውጭ ሀገር ባለሀብቶች ገንዘባቸውን በጋና ለማሰራት እስካሁን ያን ያህል ፍላጎት እንዳላሳዩ ጀርመናዊው የፖለቲካ ተንታኝ ቡርክሀርት ገልጸዋል።
«  የምጣኔ ሀብቱን ለማሳደግ የሚያስችል፣ በተለይ፣ ዓለም አቀፍ ተቋማት ገንዘባቸውን በጋና እንዲያሰሩ የሚያበረታታ መርህ መዘርጋት አስፈላጊ ነው። አሁን እንደሚታየው ግን የጋና መንግሥት ለዚህ የሚያስፈልገው ሁኔታ ለማመቻቸት ጠንክሮ እየሰራ አይደለም።  እስካሁን በሀገሪቱ የተሰራባቸው ሕጎች የውጭ ባለሀብቶችን በመሳብ ፈንታ ተጻራሪውን ሁኔታ ነው የፈጠሩት። በዚሁ ረገድ ብዙ ሊሰራ ይችላል ብዬ አስባለሁ። »
በጋና የሚታየውን የወጣቱን ስራ አጥነት ለመቀነስ ለሀገር ውስጥ እና ለውጭ ሀገራት ባለተቋማት አስተማማኝ አማላይ የኤኮኖሚ ሁኔታ መፍጠር ወሳኝ ይሆናል።

Ghana Emmanuel Macron und Nana Akufo-Addo
ምስል Getty Images/AFP/Pool/P. Wojazer
Ghana Fischereiverbot
ምስል DW/D. Agborli
uteinghana03_btq.jpg
ምስል Ute Walter

አርያም ተክሌ/ያን ፊሊፕ ቪልሄልም

ማንተጋፍቶት ስለሺ