1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጋና እና የጀርመን አጋርነት

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 5 2010

አዶ ከመለመን ወይም የአውሮጳ ግብር ከፋዮችን ገንዘብ በቋሚነት ከመውሰድ ይልቅ ሁለቱን ወገኖች ተጠቃሚ የሚያደርግ አጋርነት እንዲፈጠር ይፈልጋሉ። ደጋግመው እንደሚናገሩት ጋና ወርቅ ካካዋ እና ነዳጅ ዘይት ብቻ አይደለም ያላት። ይልቁንም መሥራት የሚችሉ እና ሥራም በጥድፍያ የሚያስፈልጋቸው ወጣቶችም ጭምር እንጂ።

https://p.dw.com/p/2pMJf
Bundespräsident Steinmeier in Ghana
ምስል DW/Isaac Kaledzi

የጋና እና የጀርመን ትብብር

የጀርመን ፕሬዝዳንት ፍራንክ ሻልተር ሽታይንማየር በጋና ያካሄዱትን የሁለት ቀናት ጉብኝት አጠናቀው ዛሬ ጋምቢያ ገብተዋል። ሽታይንማየር በሁለት ቀናት የጋና ቆይታቸው ለጋና ታዳሽ የኃይል ምንጭ እና ለተግባረ እድ ስልጠና  የሚውል 100 ሚሊዮን ዶላር ብድር ስምምነት ተፈራርመዋል።  ስምምነቱ ሁለቱ ሀገራት የተፈራረሙት « የውረታ እና የለውጥ አጋርነት» ስምምነት አካል ነው። ጀርመን እና የጋና ፕሬዝዳንቶች ከዚህ ቀደም በተለያዩ ደረጃዎች ሲያገለግሉ ከ10 ዓመታት በላይ ይተዋወቃሉ። የቅርብ ጓደኞችም ነን ይላሉ ። በጋና ለጀርመን የሚሰጠው ክብር ከሌሎች የአፍሪቃ ሀገራት ከፍ ያለ ነው። የብሪታንያ ዜና ማሰራጫ ቢቢሲ ባካሄደው የዳሰሳ ጥናት ፣ ጀርመን በዓለም ላይ ካሉ ሀገራት ይበልጥ ተወዳጅዋ ናት በጋና። ሥልጣን በሰላማዊ መንገድ አራት ጊዜ የተሸጋገረባት ፣ ለህግ የበላይነት እና ለዴሞክራሲ መቆምዋን በግልጽ ያሳያችው ጋና ከአፍሪቃ ለመዋዕለ ንዋይ ፍሰት እጅግ የተሻለ ማዕቀፍ የምታቀርብ ሲሉ የጀርመን ፕሬዝዳንት ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር አወድሰዋታል። ሽታይንማየር አክራ ውስጥ ከትናንት በስተያ ከጋናው ፕሬዝዳንት አኩፎ አዶ ጋር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት ከጋና መንግሥት ጋር የተፈራረሙት ስምምነት ሀገሪቱ እስከዛሬ ላከናወነቻቸው ተግባራት ክብር የሚሰጥ ነው። 
«አሁን የተፈራረምነው የጋና እና የጀርመን «የለውጥ አጋርነት» ስምምነት  ሰነድ እዚህ ጋና ውስጥ ባለፉት ዓመታት የተሰራውን እና በመሠራት ላይ ያለውን በጣም እንደምናከብር እንዲሁም ጋና ከሌሎች የአፍሪቃ ሀገራት ጋር ስትነፃጸር በጥሩ ጎንዋ የምትለይ መሆንዋን የሚያሳይ ነው።»
ጋና ከጀርመን ጋር የለውጥ አጋርነት ስምምነት በመፈራረም ሦስተኛዋ የአፍሪቃ ሀገር ናት። በ2017 ጀርመን ከኮትዲቯር እና ከቱኒዝያ ጋር ተመሳሳይ ስምምነቶችን ተፈራርማለች። ይህ ስምምነትም በቅርቡ ጀርመን ባስተናገደችው የቡድን ሀያ ጉባኤ ላይ ያስተዋወቀችው« ኮምፓክት ዊዝ አፍሪካ» የተባለው መርሃ ግብር አማራጭ ተደርጎ ሊታይ ይችላል። ትኩረቱም ታዳሽ የኃይል ምንጮች እና መሠረተ ልማት ነው። ጀርመን ለጋና የምትሰጠው ብድር 100 ሚሊዮን ዩሮ ነው። ከዚህ ውስጥ 85 በመቶው በጣም ዝቅተኛ ወለድ የሚያስከፍል ነው። ሀይደርን ለመሳሰሉ ከፍሳሽ ቆሻሻ ኤሌክትሪክ የሚያመነጭ ባዮጋዝ ለሚያመርት ድርጅት ባለቤቶች ይህ ትክክለኛ አሰራር ነው። ጋና ከጀርመን አጋሮችዋ እነዚህን የመሳሰሉ ውረታዎች እና የፋይናንስ አማራጮች ያስፈልጓታል። ምክንያቱም የሀገር ውስጥ ባንኮች ለሚያበድሩት ገንዘብ የሚያስከፍሉት ወለድ ከ30 እስከ 40 በመቶ ይደርሳል። ሀይደር  አነስተኛ ወይም መካከለኛ ከሚባሉ ድርጅቶች የትኛዎቹ ይህን መሰሉን የባንክ ብድር የመውሰድ አቅም ሊኖራቸው እንደሚችል አላውቅም ይላሉ።  እናም ከሽታይንማየር ጋር ወደ ጋና ከሄዱት 18 የትላላቅ የጀርመን ድርጅቶች መሪዎች ብዙ ነው የሚጠበቀው። በፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑዌል ማክሮ ጉብኝት ወቅት የጋናው ፕሬዝዳንት አኩፎ አዶ  «ጋና ከእርዳታ ባሻገር፣ጋና ከልማት እርዳታ ባሻገር የተሰኘውን ሀሳባቸውን ሲያብራሩ ነበር። አዶ ከመለመን ወይም የአውሮጳ ግብር ከፋዮችን ገንዘብ በቋሚነት ከመውሰድ ይልቅ ሁለቱን ወገኖች ተጠቃሚ የሚያደርግ አጋርነት እንዲፈጠር ይፈልጋሉ።  ደጋግመው እንደሚናገሩት ጋና ወርቅ ካካዋ እና ነዳጅ ዘይት ብቻ አይደለም ያላት። ይልቁንም መሥራት የሚችሉ እና ሥራም በጥድፍያ የሚያስፈልጋቸው ወጣቶችም ጭምር እንጂ። ይህ መንግሥታቸው በዋነኛነት የሚያሳስበው ጉዳይ መሆኑን ለሽታይንማየር ነግረዋቸዋል። 
«  እንደምታውቁት ትምሕርት መንግስቴ ቅድሚያ ትኩረት የሚሰጠው ጉዳይ ነው። የጋና የንግድ ተቋማት በትምሕርት ላይ በከፍተኛ ደረጃ እንዲወርቱ እንፈልጋለን።  ምክንያቱም የሠራተኛውን ኃይል አቅም እና ብቃት ለማሳደግ እንፈልጋለን።» 
የጋናው ፕሬዝዳንት የጀርመን ኤኮኖሚ ስኬት ምሶሶዎች፤ መካከለኛ ገቢ ያለው ጠንካራ ህብረተሰብ፣ በተለይ በታዳሽ የኃይል ምንጭ ዘርፍ እጅግ በጣም ጥሩ የሆነ ቴክኖሎጂ እና እጅግ በጣም ጥሩ የሙያ ትምሕርት መሆናቸውን ያስረዳሉ። እነዚህ ለጋናም በሚገባ ይሠራሉ ያሏቸው ተሞክሮዎች በርሳቸው አስተያየት ምናልባትም ከዓለም የተሻሉ ናቸው። አዶ  ጋና ውስጥ በሚገኙ 216 ወረዳዎችች ፋብሪካዎች የመገንባት እቅድ አላቸው። ከልማት እርዳታ ጥገኝነት ለመላቀቅ መነሳታቸው ደግሞ በጀርመናውያን እንግዶቻቸው ዘንድ ጥሩ ተቀባይነት አግኝቷል።

Afrika, Bundespräsident Steinmeier in Ghana
ምስል picture-alliance/dpa/B.von Jutrczenka
Bundespräsident Steinmeier in Ghana
ምስል picture-alliance/dpa/B. von Jutrczenka

ኂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ