1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጊኒ ፕሬዚደንታዊ ምርጫ

ቅዳሜ፣ መስከረም 29 2008

በጊኒ ፕሬዚደንታዊው ምርጫ የፊታችን እሁድ ይደረጋል። በዚሁ ምርጫ ላይ ስድስት ሚልዮን መራጭ ሕዝብ በእጩነት ከቀረቡት ስምንት ተወዳዳሪዎች መካከል እንዲወስን ተጠርቶዋል።

https://p.dw.com/p/1GmAV
Guinea, Wahlplakat Präsident Alpha Condé
ምስል DW/B. Barry

[No title]

ከዋናው የተቃውሞ ፓርቲ መሪ እጩ ሴሉ ዳሌይን ዲያሎ እና ከቀድሞ ጠቅላይ ሚንስትር ሲዲያ ቱሬ በስልጣን ላይ ያሉት ፕሬዚደንት አልፋ ኮንዴ በተለይ ከፍተኛ ፉክክር እንደሚጠብቃቸው ይገመታል።

የሃገሪቱ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ መብቱን ለማስከበር ጉጉት ቢኖረውም፣ እአአ በ2010 ከተካሄደው ምርጫ በኋላ የተፈጠረው ዓይነት ሁከት እንዳይነሳ ሰግቶዋል። በወርቅ፣ አልማዝ እና ነዳጅ ብትታደልም ከግማሽ የሚበልጠው ሕዝቧ በድህነት የሚኖርባት ጊኒ ብዙ የሁከት ዓመታት አሳልፋለች። ጊኒ እአአ በ1958 ነፃነቷን ከተጎናፀፈች በኋላ የፕሬዚደንት ሴኩ ቱሬ ሃገሪቱን በጠንካራ አገዛዝ መርተዋል፣ ተከታያቸው ላናዛና ኮንቴም እርግጥ መድብለ ፓርቲ ቢያስተዋውቁም፣ ሕዝቡ በመንግሥት አንፃር ትችትም ሆነ ተቃውሞ የማሰማት መብት አልነበረውም። ኮንቴ በ2008 ከሞቱ በኋላ ሻለቃ ዳዲስ ካማራ ራሳቸውን ፕሬዚደንት ብለው በመሰየም ለአንድ ዓመት ሃገሪቱን ገዝተዋል። በኮናክሪ ስቴድየም ከ150 የሚበልጡ ተቃዋሚ ቡድናት ደጋፊዎች በመንግሥቱ ኃይላት ለተገደሉበት ድርጊት ካማራ ተጠያቂ ከተባሉ እና የግድያ ሙከራ ከተደረገባቸው በኋላ ወደ ጎረቤት ሃገር መሸሻቸው ይታወሳል። ከዚያ በ2010 ነበር ለረጅም ዓመታት በተቃዋሚነት ሲንቀሳቀሱ የነበሩት ፖለቲከኛው አልፋ ኮንዴ በሃገሪቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በተካሄደ ዴሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጡት። ይሁንና፣ የምርጫው ውጤት ይፋ ከተደረገ በኋላ በተፈጠረ ግጭት በመቶዎች የሚቆጠሩ ተገድለዋል፣ በርካቶችም ቆስለዋል።
አልፋ ኮንዴ በነገውም ምርጫ እንደገና የማሸነፍ ዕድላቸው ከፍ ያለ መሆኑ ይነገራል። ይሁንና፣ ግጭት ሊነሳ እንደሚችል ታዛቢዎች ጠቁመዋል። ሴሉ ዳሌን ዲያሎ እና አንዳንድ የተቃዋሚው ቡድኖች እጩዎች ዓለም አቀፍ ታዛቢዎች ዕድሜአቸው ያልደረሱ ህፃናትም በመራጭነት ተመዝግበዋል የሚሉ ምርጫውን ለማጭበርበር የተደረጉ ተመሳሳይ ጥረቶችን ማጣራት እንዲችሉ ምርጫው ወደሌላ ጊዜ እንዲተላለፍ በድጋሚ ቢጠይቁም፣ ፕሬዚደንት ኮንዴ ዕለቱ እንደማይቀየር በማስታወቃቸው፣ በምርጫው እንደማይሳተፉ እና ውጤቱንም እንደማይቀበሉ ዝተዋል። ለውዝግቦች የመፍትሔ ሀሳብ የሚጠቁመው ዓለም አቀፍ ድርጅት ፣ ክራይስስ ግሩፕ ተንታኝ ቨንሶ ፉሼ እንደሚሉት፣ የምርጫው ዕለት ቢተለለፍ አንዳንድ ችግሮች በርግጥ ሊወገዱ ይችሉ ይሆናል።
« በተለይ፣ በምርጫው ሰበብ ባለፉት ወራት በሃገሪቱ የተካሄደው ብርቱ ክርክር እና ተቃውሞ ሰልፎች፣ ይህም ያስከተለው የኃይል ተግባር እና እስራት ሲታሰብ፣ ምርጫውን በጥቂት ቀናት እንዲተላለፍ ጥያቄ መቅረቡ ስህተት አይመስለኝም።»
ግን፣ ባጠቃላይ ተቃዋሚዎች ምርጫውን በተመለከተ አንድ አቋም ያልያዙበት ድርጊት ዕድላቸውን እንዳጠበበው ነው ተንታኙ ፉሼ የገለጹት።
« የተቃዋሚ ቡድኖች እአአ በ2010 ም ሆነ በ2013 ዓም የምርጫውን ውጤት አሳማኝ ሆኖ አላገኙትም። የአውሮጳ ህብረት እና የአፍሪቃ ህብረት የምርጫ ታዛቢዎች ያወጡዋቸውን ዘገባዎች ሲንመለከታቸው በርግጥ፣ ስለምርጫው ትክክለኝነት ብዙ ጥያቄዎች ሊነሱ ይችላሉ። »
ለነገው ፕሬዚደንታዊ ምርጫ ዘመቻው ካለፉት ምርጫዎች ከታዩት ሁሉ ሰላማዊ ቢባልም፣ ሁከት አላጣውም። በዚህ ሳምንት በመዲናይቱ ኮናክሪ በትልቁ የመዲና ገበያ በፕሬዚደንቱ እና በተቃዋሚ እጩዎች ደጋፊዎች መካከል በተፈጠሩ ግጭቶች ሁለት ሰዎች ሲገደሉ ከ35 የሚበልጡ ቆስለዋል፣ መኪኖች በእሳት ጋይተዋል። በንዜሬኮሬ ግዛት ም አንድ ሰው ሲገደል፣ 80 ቆስለዋል። ምርጫውን የሚታዘበው የአውሮጳ ህብረት ቡድን መሪ ፍራንክ ኤንግል ምርጫው ነፃና ትክክለኛ ፡ እንዲሁም፡ ከሁከት ነፃ እንደሚሆን ተሰፋቸውን ገልጸዋል።

Wahlkampf in Guinea 2015 Cellou Dalein Diallo
ምስል DW/B. Barry
Wahlkampf Guinea 2015
ምስል DW/B. Barry


አርያም ተክሌ
ልደት አበበ