የጀርመን ሕገ-መንግሥት 65ኛ ዓመት
ዓርብ፣ ግንቦት 15 2006የጀርመን ሕገ-መንግሥት የፀደቀበት ሥልሳ-አምስተኛ ዓመት ዛሬ ጀርመን ዉስጥ ታስቦ ዉሏል።ሕገ-መንግሥቱ ከናትሲ አምገነናዊ ሥርዓት የተላቀቀችዉ ጀርመን የዜጎች መብት የተከበረባት፤ ፍትሕና ዴሞካራሲያዊ ሥርዓት የፀናባት ሐገር እንድትሆን ጠንካራ መሠረት የጣለ መሆኑ በሰፊዉ እየተነገረ ነዉ።የጀርመን የሕግ-መምሪያ እና የሕግ-መወሰኛ ምክር ቤት አባላት ዕለቱን በጋራ አክብረዉታል።የሕግ-መወሰኛዉ ምክር ቤት ( Bundeserat) ፕሬዚዳንት፤ የኒደርዛክሰን ሚንስትር ፕሬዝዳንት ሽቴፋን ቫይል እንዳሉት ሕገ-መንግሥቱ ከፀደቀበት ጊዜ ጀምሮ የተቆጠሩት 65 ዓመታት በጀርመን ታሪክ አቻ የማይገኝላቸዉ ድሎች የተመዘገበበት ጊዜ ነዉ።የሕግ-መምሪያዉ ምክር ቤት (Bundesetage) ፕሬዚዳንት ኖርበርት ላሜርት በበኩላቸዉ እንዳሉት ሕገ-መንግሥቱ ከጀርመን አልፎ ለሌሎች ዴሞክራሲያዊ ሥራዓትን ለሚገነቡ ሐገራትም አብነት ነዉ።
« ከዓለም ትላልቅ ሕገ-መንግሥታት አንዱ ከሆነ ቆየ።ለታዳጊ ዴሞክራሲዎች አቅጣጫን የሚያመላክት፤ በሐገር ደረጃም ለሌች ሕገ-መንግሥቶች እንደ ማጣቃሻ ምሳሌ የሚያገለግል ነዉ።»
የፌደራል ጀርመን ሪፐብሊክ እስካሁን የሚሠራበት ሕገ-መንግሥትን በይፋ ያፀደቀችዉ ከሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት አሸናፊዎች ቀጥታ ቁጥጥር በተላቀቀች ማግሥት እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር በ1949 ነበር።
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ