1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመኑ ፕሪዝደንት የአፍሪቃ ጉብኝት

ሐሙስ፣ ጥር 3 1999

የጀርመኑ ፕሪዘደንት ሆርስት ኮለር ጋናን ለአራት ቀን ለመጎብኘት በዛሬዉ እለት ወደ አፍሪቃ ጉዞአቸዉን ያቀናሉ። ፕሪዝደንት ሆርስት ኮለር ከጋናዉ አቻቸዉ ከፕሪዝደንት ጆን ኩፎር እና ከጋና መንግስት ባለስልጣናት ጋር ይገናኛሉ

https://p.dw.com/p/E0hT
ፕሪዝደንት ሆርስት ኮለር እና መራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክል ለአዉሮፓዉያኑ 2007 አ.ም እንኳን አደረሰን የሰላምታ ልዉዉጥ
ፕሪዝደንት ሆርስት ኮለር እና መራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክል ለአዉሮፓዉያኑ 2007 አ.ም እንኳን አደረሰን የሰላምታ ልዉዉጥምስል AP

ሆርስት ኮለር ዘንድሮ ለሁለተኛ ግዜ በአክራ በሚካሄደዉ «የወዳጅነት ግንኙነት ከአፍሪቃ ጋር» በተሰኘ እርእስ በሚካሄደዉ ጉባኤ ላይ ተካፋይም ይሆናሉ። ኮለር በፕሪዝደንት የስልጣን ዘመናቸዉ አፍሪቃን ሲጎበኙ ይህ ለሶስተኛ ግዜ መሆኑ ነዉ። አዜብ ታደሰ ዝርዝር ዘገባ አላት

የፕሪዝደንትነት ስልጣናቸዉን ከመያዛቸዉ ቀደም ሲል የአለም አቀፉን የምንዛሪ ተቋም በአጽሮት IMF አስተዳዳሪ የነበሩት ፕሪዝደንት ሆርስት ኮለር የጋናዉን ፕሪዝደንት John Kufuor ን በአገራቸዉ ስለሚያደርጉት ጥሩ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እና የፖለቲካ ታህድሶ ለዉጥ አድናቆታቸዉን ገልጸዉላቸዋል። ጋና ባሳየችዉ የእድገት እንቅስቃሴ፣ እ.አ 2004 አ.ም ከ18 አፍሪቃ አገራት መካከል ከአለማቀፉ የምንዛሪ ተቋም እና ከአለም አቀፍ ባንክ ያለባትን ዕዳ ግማሹን ነጻ ለመሆን የበቃች አንዷ የአፍሪቃ አገር ነች። ሆርስት ኮለር የጋናዉን ፕሪዝደንት ምሳሌ በማድረግ John Kufuor በአገራቸዉ የተጠቀሙትን አይነት የታህድሶ ለዉጥ እና የኢኮኖሚ እድገት እንቅስቃሴ ለሌሎች አፍሪቃ አገሮችም ያስፈልጋል ባይ ናቸዉ። የአፍሪቃ አገሮች ይላሉ፣ ኮለር፣ የአፍሪቃ አገሮች ለለዉጥ እና ዲሞክራሲያዊ ለሆነ አመራር ፊታቸዉን ካላዞሩ እድገት ሊያመጡ አይችሉም ባይ ናቸዉ። የአፍሪቃ ወደጅ የሆኑት ኮለር፣ ባለፈዉ አመት የአፍሪቃ ጉዞዋቸዉ ቦትስዋናን፣ ሞዛንቢክን፣ ማዳጋስካርን የጎበኙ ሲሆን በመጀመርያ የአፍሪቃ ጉዞአቸዉ ደግሞ፣ ቤኒን፣ ኢትዮጽያን እንዲሁም በዉጥረት ላይ የምትገኘዉን ሴራሊዮንን መጎብኘታቸዉ የሚታወስ ነዉ። የአፍሪቃ አዉሮፓ የወዳጅነት ግንኙነት አሁንም ቢሆን ገና መጠናከር ያለበት ጉዳይ ነዉ ብለዉ የሚያምኑት ሆርስት ኮለር በአሁኑ ወደ ጋና ጉዞዋቸዉ ከአፍሪቃ ጋር የወዳጅነት ግንኙነት በሚል ርእስ ስር በአፍሪቃ መድረክ ስብሰባ ይቀመጣሉ። ከአንድ አመት በፊት እዚህ በቦን ከተማ በተካሄደዉ የአፍሪቃ መድረክ ስብሰባ ተገኝተዉ የተሰማቸዉን ጥሩ መንፈስ እንዲህ ሲሉ ነበር የገለጹት

« ለኔ ይህ አዲስ እና በጣም አስፈላጊ ሆኖ የታየኝ በፈጣን መልክና በአስተማማኝ ሁኔታ መነጋገር መቻላችን ነዉ። መነጋገር ብቻም ሳይሆን ደግሞ ግልጽ በሆነ መልኩ ትችትን መቀበል እና መስጠት መቻላችን ነዉ። የትችት መቀበሉም ሆነ መስጠቱ ድርጊት አዲስ ነገር ነበር»

እንደ ጀርመኑ ፕሪዝዳንት በአፍሪቃ እና በአዉሮፓ መካከል መተማመንን ለማሳደር፣ የንግግር መድረክ መክፈት፣ ከአፍሪቃ ጋር ስለሚፈጠረዉ እድገት፣ ልማት እንዲሁም የፖለቲካ ግንኙነት፣ ቁልፍ እና መሰረት ነዉ ባይ ናቸዉ።

የሁለተኛዉ የአፍሪቃ መድረክ ስብሰባ በጋና መካሄዱ በእድገት እና ልማት እንቅስቃሴ ረገድ፣ ጋና ከሌሎች አፍሪቃ አገራት የበለጠ ጥረት ማድረጓ ጀርመን አተኩሮዋን እንዳጎለበተች የጀርመኗ የኢኮኖሚ ተራድኦ ሚኒስቴር ሃይደማሪ ቪቾሪክ ሶይል ይገልጻሉ። በያዝነዉ የአዉሮፕያኑ አመት መጀመርያ ጀርመን የአዉሮፓዉን ህብረት ርዕሰ ብሄርነት ስልጣኗ ለአፍሪቃ ለየት ያለ አተኩሮ ትሰጣለች ባይ ናቸዉ

«አዎ !በያዝነዉ አመት ጀርመን የአዉሮፓዉ ህብረት ምክር ቤት እና የቡድን ስምንት አገራት የርዕሰ-ብሄርነት ዘመኗ ለአፍሪቃ ለየት ያለ አትኩሮትን እንሰጣለን። አፍሪቃ ለኛ አጎራባች አህጉራችን ናት። ስለዚህም አለም እንዲገነዘብልን የምንፈልገዉ አፍሪቃ የችግር የድህነት እና የዉጥረት አህጉር ሳትሆን ወጣት እና ትኩስ ሃይል የሚኖርባት የተለያዩ ዘርፎች ከፍተኛ እድገት የሚታይባት አህጉር እንደሆነች ማሳየት እንፈልጋለን። እነዚህ ትኩስ ሃልሎች የእድገት መሰማርያ ዘርፎችን አግኝተዉ የወዲት ተስፋቸዉን እንዲገነቡ እንፈልጋለን። ሌላዉ ሰላም ጸጥታ እንዲሰፍን እና ዉጥረት በበዛባቸዉ አካባቢዎች ሁኔታዎች እንዲረጋጉ እንሻለን።

የኢኮኖሚ ተራድኦ ሚኒስቴሯ በተጨማሪ ይላሉ፣ በአህጉሪቷ ለእድገት መሰረት የሆኑ እንደ መንገድ ፋብሪካ ኢንዱስትሪ የእርሻ ምርቶችን በአህጉሪቷ ለማጎላበት የወቅቱ የቡድን ስምንት ርዕሰ ብሄር የአፍሪቃ መሪዎችን እና የአፍሪቃ መንግስታትን የጀርመን ፊደራል ሪፑብሊክ ጋብዞ መምከር አለበት ብለዋል።

የጀርመኑ ፕሪዝደንት ሆርስት ኮለር ዛሪ የሚጀምሩት የጋና የአራት ቀናት ጉብኝት የሁለቱን አገራት የወዳጅነት እና የልማት ትብብር መሳካት ያንጸባርቃል።