1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የድንበር ላይ ግንብ በኬንያ

ረቡዕ፣ የካቲት 28 2010

የኬንያ መንግሥት የሸባሪዎችን ጥቃት ለመከላከል ድንበር ላይ ግንብ ማስገንባት ያቀደዉ ከዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካዉ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ብዙ ቀደም ብሎ ነዉ። ይህን የወሰነዉም በጋሪሳ ዩኒቨርሲቲ ከባድ ጥቃት በደረሰበት ወቅት ነዉ። ኬንያ ድንበር እየጣሰ ጥቃት የሚያደርስባትን የሶማሊያ ፅንፈኛ አሸባሪ ቡድን ባለበት አግዳ ማስቀረት ፈልጋለች።

https://p.dw.com/p/2tnUu
Kenia Polizisten an der Grenze zu Somalia 05.12.2014
ምስል Reuters/G. Tomasevic

ዕቅዱ የአሸባብን ጥቃት ለመከላከል ያለመ ነው፤

በሶማሊያ እና ኬንያ መካከል ከ700 ኪሎ ሜትር በላይ በሚሆነዉ የድነበር አካባቢ፤ እስካሁን የተጠናቀቀዉ ስምንት ኪሎ ሜትሩን ብቻ የሚሸፍነዉ አጥር ነው። በስተሰሜን ራቅ ባለዉ ማንዴራ ከተማ አካባቢ። የከተማይቱ ነዋሪዎች ግን ፕሮጀክቱ ጠቃሚነ ነው የሚል አመለካከት የላቸውም። ጀማል በከተማዋ የምግብ ሸቀጣ ሸቀጥ ሻጭ ነው። የፕላስቲክ ሣህኖች፣ ቅርጫቶች እና ሌሎች ሸቀጦች በሞሉበት ሱቁ ዉስጥ መንም መፈናፈኛ የለም።
«ሁሉንም ነገሮች በሚባል ደረጃ የምናገኘዉ ከዚያ ነው። 90 በመቶ የሚሆነዉን የምናገኘዉ ከሶማሊያ ነው። በሶማሊያ ላይ ጥገኖች ነን  ።»
ማንዴራ ሶማሊያ ድንበር ላይ የምትገኝ ከተማ ናት። ገበያዉ ላይ ሆኖ የሚወረወር ድናጋይ የሚያርፈዉ እዚያ ነው። 
«አሁን ድንበሩ ክፍት ነው። ወደ ሶማሊያ የሚሄዱ አህዮች አሉን፤  የምንፈልገዉን ሁሉ የምናገኘው ከሶማሊያ  ነዉ። ሌላዉ ቀርቶ ምግብ እንኳን ከዚያ ነዉ የሚመጣዉ። ከኬንያ የሚመጣ ምንም ነገር የለም።»
እንደ ኬንያ መንግሥት ፍላጎት ከሆነ ከቀረጥ ነፃ የሆኑ ዋጋቸዉ የረከሱ ዕቃዎች ንግድ በቅርቡ ማክተሙ አይቀርም። ከሶማሊያ ጋር የሚያገናኘዉን ድንበር ባጠቃላይ  መዝጋት ይፈልጋል። የአሸባብን አሸባሪዎች ለማገድ ያቀደዉ የአጥር ፕሮጀክት 1,4 ቢሊየን ዶላር ይገመታል። 

«ድንበራችን ክፍት ነዉ። በተለይም በእዚህ ጊዜ የሽብር ችግሮች አሉ። ይህ ደግሞ በዓለም ደረጃ ሆነ በእኛ አካባቢ የሚቋጭ ጉዳይ አይመስልም። ሌላዉ ቀርቶ መተኛት አንችልም። ይህን አጥር መገንባቱ የፀጥታዉን ይዞታ ያሻሽላል።»
ሆኖም መሐመድ አብዲ ሳኒ ከዚህ አስተያየቱ ጋር ማንዴራ ዉስጥ ብቻዉን የቆመ ይመስላል። የማንዴራዉ አዛዉንት ሁሴን ይህ አጥር በሁለቱ ወገን በሚኖሩ ሕዝቦች መካከል አለመተማመንን የሚያመጣ ነዉ። ከድንበር ወዲያም ሆነ ወዲህ የሚኖሩት ወገኖች ጎሳቸዉ ሶማሌ ነዉ።
«ያገባሁት ከወዲያኛዉ አካባቢ ነዉ፤ ቤተሰቦች እና ዘመዶቼ እዚያ ናቸዉ። እንዴት አጥር እዚህ እንዲገነባ እፈቅዳለሁ? አማቼ ቢሞቱ ለመሻገር አልችልም።»
ድንበሩን ተሻግረዉ መሄድ የሚችሉት ወደ ትምህርት ቤት የሚሄዱ ልጆች ናቸዉ። በብቸኛዉ የመቆጣጠሪያ ኬላ ፓስፖርት እያሳዩ። ከቦታ ቦታ የሚዘዋወሩት አርብቶ አደሮች ለከብቶቻቸዉ ግጦሽ ለማግኘት ርቀዉ መጓዝ አለባቸዉ። እናም ከፍተኛ ቁጥጥር በሚደረግበት የድንበር አካባቢ ተከማችተዋል። ይህ ደግሞ አሳፋሪ ነዉ ይላሉ ሀሰን።
«አጥር ሲገነቡ ከፍተኛ ፍርሃት ነዉ በእኛ ላይ ስለሚያመጡ በቃ እኛ ተሸናፊዎች ሆነናል። አጥር በማጠር ዓላማቸዉ ግቡን መታ ማለት ነው? እኔስ ተንኮታኩቶ እንደሚጠፋ ተስፋ አደርጋለሁ፤ ይህ አጥር የሚሆን አይመስለኝም።»
የተጠናቀቀዉ ስምንት ኪሎ ሜትር የሚሸፍነዉ የድንበር አጥር በሁለት ረድፍ ቋሚዎች ተዘርግተዉ በመካከሉ የሽቦ አጥር ተዘርግቶበታል። ከእሱ ቀጥሎ ደግሞ ጥልቀቱ ሦስት ሜትር የሆነ ጉድጓድ አለ፤ ተሽከርካሪዎችን ለማስቆም። 
«ይህ ለረዥም ጊዜ የአሸባሪ ጥቃት የደረሰባትን የማንዴራን ግዛት ለመከላከል የተደረገ ነው። ስምንት ኪሎ ሜትር አጥሩን ከሰራን በኋላ የማንዴራ ነዋሪዎች በከተማዋ ጥቃት የለም ብለዉናል።»
ይላሉ የአካባቢዉ የፀጥታ ጉዳይ ተጠሪ መሐመድ ሳልህ በኩራት። ግን ደግሞ አጥሩ በሽቦ መቁረጫ ሊቆረጥ የሚችል እና በዚያም ላይ በቋሚነት የሚጠበቅ አይደለም። ከሦስት ዓመት በፊት የኬንያ መንግሥት ድንበሩን ያልተጠበቁ ጠላቶች እያለፉ የሚያደርሱትን ጥቃት ለመከላል በግንብ ለማጠር ነበር የወሰነዉ። አሁን ግንቡ ወደ አጥር ተለዉጧል። እሱም የሁሉም የድንበር አካባቢ ኗሪዎች ይሁንታ ያገኘ አይመስልም። 

Kenia Sicherheitskontrollen an der Grenze zu Somalia 08.12.2014
ድንበር ለመሻገር ፍተሻምስል Reuters/G. Tomasevic

ሸዋዬ ለገሠ/ሊንዳ ሽታዉደ 

አርያም ተክሌ