1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የደቡብ ሱዳን የተኩስ አቁም ስምምነት

ሐሙስ፣ ጥር 15 2006

ሁለቱ የደቡብ ሱዳን ተፋላሚ ወገኖች፤ በፕሬዚደንት ሳልቫኪር የሚመራው የጁባው መንግስት እና የቀድሞው የኣገሪቱ ምክትል ፕሬዚደንት ሪክ ማቻር የሚመሩት ኣማጺ ቡድን አዲስ ኣበባ ላይ ማምሻውን የተኩስ ኣቁም ስምምነት ተፈራርመዋል።

https://p.dw.com/p/1AwF9
Flüchtlinge Südsudan
ምስል Reuters

በምሥራቅ ኣፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለሥልጣን በምህጻሩ ኢጋድ ኣደራዳሪነት ሲካሄድ የነበረው ጥረት በሁለቱም ወገኖች በኩል በቀረቡ ቅድመ ሁኔታዎች ምክንያት ሳይሳካ መቆየቱ ይታወቃል ።

ፕሬዚደንት ሳልቫኪር ከሁሉ በፊት ኣማጺያኑ ተኩስ ኣቁመው ወደ ድርድሩ መቅረብ ይኖርባቸዋል ሲሉ ቆይቷል። የኣማጺያኑ መሪ ሪክ ማቻር በበኩላቸው የታሰሩት ፖለቲከኞች እንዲፈቱ እና የኡጋንዳ ጦር ኣገሪቱን ለቆ እንዲወጣ ይፈልጋሉ።

አዲስ ኣበባ ላይ የኢጋድ መሪዎች ለደቡብ ሱዳኑ ቀውስ መፍትሄ ለመሻት ያላሰለሰ ጥረት እያደረጉ ባሉበት በኣሁኑ ወቅት የኣማጺያኑ መሪ ሪክ ማቻር ያሰሙት ዛቻ በእርግጥ ያልተጠበቀ ጋሬጣ ፈጥሮ ነበር። የታሰሩ ፖለቲከኞች መፈታትን እንደ ቅድመ ሁኔታ ይዘው የቆዩት ማቻር ይህንን ዛቻ ያሰሙት ትላንት ከደ/ሱዳን ድረገጽ ጋር ባደረጉት ቃ/መጠይቅ ሲሆን ለዚህ ችግር መፍትሄ የሚገኘው ኣሉ እንዲያውም፤ ሳልቫኪር የፕሬዚደንትነቱን መንበር ሲለቁ ብቻ ነው። ፕሬዚደንት ሳልቫኪር በበኩላቸው ከሁሉ በፊት ዓማጺያኑ ተኩስ ኣቆመው ወደ ድርድሩ መቀረብ ይኖርባቿል የሚል ኣቐም ነበራቸው። የተኩስ ኣቁም ስምምነት መደረሱ ኣፋጣኝ ተግባር ይሁን እንጂ ኣሁንም ቢሆን የዓለም ዓቀፍ ጸጥታ ጥናት ተቋም ተንታኝ አቶ ሃሌሉያ ሉሌ እንደሚሉት የኡጋንዳ ጣልቃ መግባትን ጨምሮ ሌሎች ግጭቱን ውስብስብ እንዲሆን ያደረጉት ምክንያቶች ደግሞ ኣሉ።

Südsudans Präsident Kiir und Ugandas Präsident Museveni
ምስል Tony Karumba/AFP/Getty Images

በኡጋንዳ ወታደሮች ጭምር የሚታገዘው የፕሬዚደንት ሳልቫኪር ጦር ኣማጺያኑን በማጥቃት ቦር እና ማላካላል የተባሉ ከተሞችን ማስለቀቁን ኣስታውቆ ነበር። የዓማጺያኑ መሪ ማቻር እንደሚሉት ግን ጦራቸው ጥቃቱን መክቶ መልሶኣቿል። በተመሳሳይ ሁኔታ ማቻር በርካታ የኡጋንዳ ወታደሮችን መደምሰሳቸውን ገልፀዋል። ኡጋንዳ እስከ ኣሁን ያመነችው ግን 9 ሞተው 12 መቁሰላቸውን ብቻ ነው። ኡጋንዳ በደ/ሱዳ ውጊያ ተንደርድራ ጣልቃ መግባትን ኣስመልክቶ አቶ ሃሌሉያ ሉሌ ሁኔታውን ከህግ፣ ከፒለቲካ፣ ከዲፕሎማሲ እና ከምስራቅ ኣፍሪካ ቀጠና ኣኩዋያ ማጤን ያስፈልጋል ባይ ናቸው።

Südsudan Kämpfe Riek Maschar ARCHIVBILD 2007
ምስል Al-Haj/AFP/Getty Images

ፕሬዚደንት ሳልቫኪር ተመድ በደ/ሱዳን የሚጫወተውን ሚና በመውቀስ የሰላ ትችት መሰንዘራቸውም ሌላው ኣነጋጋሪ ጉዳይ ሆኗል። ኣሁንም አቶ ሃሌሉያ ሉሌ።

የደቡብ ሱዳን ፖለቲከኞች ከወራት በፊት አዝማሚያቸው እንደታየ ኣፋጣኝ መፍትሄ ቢፈለግላቸው ኖሮ ሁኔታው ወደ ቀውስ ባላመራ ነበር የሚሉት የጸጥታ ጥናት ተቋም ተንታኙ፤ አቶ ሃሌሉያ ሉሌ፣ ኣሁንም ቢሆን ኣንዳች መቋጫ ካልተበጀለት መዘዙ ለቀጠናውም ጭምር ሊተርፍ እንደሚችል ስጋት ኣላቸው። ካለፈው ወር ኣጋማሽ ኣንስቶ ተጋግሎ በቀጠለው የደ/ሱዳን ጦርነት እስከ ኣሁን 10 ሺህ ያህል ሰዎች ተገድለዋል። ከግማሽ ሚሊየን የማያንሱ ደግሞ ተፈናቅሏል።

ጃፈር አሊ

ኂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ