1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ኤኮኖሚ

Merga Yonas Bula
ሰኞ፣ መጋቢት 18 2009

ለመንግስት ሰራተኞች ከጥቂት ጊዜ በፊት የደሞዝ ማስተካከያ ከተደረገ በኋላ በአዲስ አበባ የሚገኙ ነጋዴዎች ዘይት፣ ስኳር እና ፍራፍሬ በመሳሰሉ መሰረታዊ ሸቀጦች ላይ የዋጋ ጭማሪ ማድረጋቸዉ ተሰምቶዋል።ይህን ተከትሎ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍትሃዊ የሸቀጦች ስርጭት እንዲኖር ለማድረግ ተጠቃሚዎች ሸቀጦቹን የሚገዙበት ኩፖን አዘጋጀቶዋል።

https://p.dw.com/p/2a3vL
Addis Ababa (Äthiopien)
ምስል picture alliance/landov

Addis Prepares Coupon for Consumers - MP3-Stereo

ኩፖኑ ተጠቃሚዎች የኢትዮጵያ ሸማቾች ማኅበር ወደ ከፈታቸዉ ሱቆች በመሄድ ሸቀጦቹን እንዲገዙ ያስችላቸዋል።

በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ንግድ ቢሮ የንግድ ግብይት ማስፋፊያ ዋና የስራ ሂደት መሪ አቶ ሰሎሞን በቀለ እነዚህ «ያልተገባ ጥቅም ፈላጊ ነጋዴዎች» የመንግስት ሰራተኞች የደሞዝ ማስተካክያን «ተገን» በማድረግ ያደረጉት የዋጋ ጭማሪ ምክንያት ስለሌዉ እንደምያስቀጣ ተነግሯቸዉ ወደ ነበረበት እንዲመለስ ተደርገዋል ብለዋል።

ኩፖኑን ለማህበረሰቡ በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንት ዉስጥ ይደርሳቸዋል የሚሉት አቶ ሰሎሞን ሸማቾች መሰረታዊ ሸቀጦችን መሸመት ከፈለጉ ኩፖኑን በቀላሉ እንደሚያገኙም ተናግረዋል።

ለመንግስት ሰራተኞች የደሞዝ ጭማሪዉ ብዙም ለዉጥ እንዳላመጣ መስማት ችያለዉ ያሉን የአዲስ አበባ ነዋር ናቸዉ።

ከአዲስ አበባ ለግል ስራ ወደ ሃዋሳ መሄዳቸዉን የተናገሩት፣ ግን ስማቸዉ እንዳይገለፅ የፈለጉ ግለሰብ፣ የኑሮ ዉድነቱም ይሁን የሸቀጦች ላይ ወጋ መጨመር ከአዲስ አበባ ይልቅ ክልል ላይ ይብሳል ብለዋል።

ነጋዴዎች ያደረጉትን የዋጋ ጭማሪ እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ይህንን ችግር ለመቀነስ ያስተዋወቀዉን የኩፖን ስርዓት እንዴት ትመለከቱታላችሁ ብለን የፌስቡክ ድረ ገፅ ተከታታዮችን አስተያየት ጠይቀን ነበር። አስተያየታቸዉን ካጋሩን መካከል «ኩፖኑ የሚያገለግለው በሱቆቹ ሸቀጥ ሲኖር» እንደሆነ፣ «ችግሩ የሚፈታው አቅርቦትንና ፍላጎትን ያጣጣመ የሸቅጥ ክምችት ሲኖር እንጂ፣ የማያገለግል ወረቀት በማደል አይደለም» ብለዋል። «አይደለም ኩፖን ብር ቢታተም ምንም ለውጥ አይመጣም» ያሉት ደግሞ ሌላዉ አስተያየት ሰጭ ፣ «ነጋዴው የእብድ ላም በሽታ ከያዘው 20 ዓመት አልፎታል»፣ ስለዚህ «የኢትዮጵያን ነጋዴ ልክ የሚያስገባው ኩፖን ሳይሆን ሸቀጥም ይሁን ሰብል ፍራፍሬ በገፍ የማምረት ባህል ሲስፋፋ ነው» ሲሉ ትችታቸዉን ሰንዝረዋል።

መርጋ ዮናስ

አርያም ተክሌ