1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዛምቢያ ፕሬዚደንት ማይክል ሳታ ዜና ዕረፍት

ሐሙስ፣ ጥቅምት 20 2007

የዛምቢያው ፕሬዝዳንት ማይክል ሳታ ህክምናቸውን በሚከታተሉበት እንግሊዝ ሃገር ትናንት ማክሰኞ ምሽት ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። እአአ ከ2011 ዓም ጀምሮ በስልጣን የቆዩት ፕሬዝዳንት ሳታ ባለፈው ሳምንት የተከበረውን የዛምቢያ 50ኛ የነፃነት በዓል በጤና መታወክ ምክንያት መታደም አልቻሉም ነበር።

https://p.dw.com/p/1De8e
Michael Sata Sambia Präsident Obit
ምስል picture-alliance/EPA/Jason Szenes

ስራ ሲጀምሩ የፖሊስ መኮንን ነበሩ። በባቡር ድርጅት እና በነጋዴዎች ማህበር ውስጥ ተቀጥረው ሰርተውም ያውቃሉ-ትናንት ህልፈተ ህይወታቸው የተሰማው የ77 አመቱ የዛምቢያ ፕሬዝዳንት ማይክል ሳታ።

ፖለቲካን የጀመሩት ዛምቢያ እአአ ከእንግሊዝ ቅኝ ነጻ ስትወጣ ሃገሪቱን ያስተዳድር በነበረው የኬኔት ካውንዳ የተባበሩት ብሄራዊ የነጻነት ፓርቲ ውስጥ ነበር። የዋና ከተማዋ ሉሳካ አስተዳዳሪ በነበሩባቸው 1980ዎቹ መንገድ እስከ መጥረግ በደረሰ ተግባራዊ ስራዎቻቸው ተቀባይነትን አግኝተዋል።

McDonald Chipenzi aus Sambia
ፕሬዚደንት ሳታ ከሚንስትሮቻቸው ጋርምስል AFP/Getty Images

ትንሽ ቆይተው ከኬኔት ካውንዳ ፓርቲ በመልቀቅ የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ ንቅናቄን (Movement for Multiparty Democracy) ተቀላቀሉ። አዲሱ ፓርቲያቸው እአአ 1991 የተካሄደውን አገራዊ ምርጫ ካሸነፈ በኋላ በሃገር ውስጥ ጉዳይ አስተዳደር ስራና ጤና ሚኒስትርነት አገልግለዋል።

እአአ 2001 የመሰረቱት የሃገር ወዳዶች ግንባር (Patriotic Front) የተሰኘ ፓርቲ በ2011 የተካሄደውን ሃገራዊ ምርጫ ሲያሸንፍ የዛምቢያ ፕሬዝዳንትነት መንበር ከእጃቸው ገባ።

ፕሬዝዳንት ማይክል ሳታ በስልጣን ላይ በቆዩባቸው ዓመታት ራሳቸውን የድሆች ጠበቃ አድርገው ይቆጥሩ ነበር። ደከመኝ የማይሉ ፖለቲካኛ ነበሩ የሚባልላቸው እኚህ ሰው በስልጣን በቆዩባቸው ዓመታት ለዛምቢያ ዜጎች የገቡትን ቃል ማሳካት ባለመቻላቸው ይወቀሳሉ።ማክዶናልድ ቺፐንዚ በዴሞክራሲ፤የሰብዓዊ መብትና መልካም አስተዳደር ላይ የሚሰራ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ሃላፊ ናቸው። ማይክል ሳታ 'ቀልድ አዋቂ ' ነበሩ የሚሉት ማክዶናልድ ቺፐንዚ በስልጣን ዘመናቸው ግን የነበሯቸውን መልካም አጋጣሚዎች እንዳልተጠቀሙባቸው ይናገራሉ።

Sambia Landwirtschaft Vizepräsident Guy Scott
ማክዶናልድ ቺፐንዚምስል privat

''በአመራራቸው በስኬታማነት እንዲታወሱ የሚያስችሏቸውን መልካም አጋጣሚዎች ሳይጠቀሙባቸው ቀርተዋል። ይህም ለዛምቢያውያን አዲስ ህገ-መንግስት መስጠት ነበር። ሁለተኛ ከገቧቸው ቃል ኪዳኖች አብዛኞቹን ማሳካት አልቻሉም። አንዳንዶቹ ድሆችን ተጠቃሚ የሚያደርጉና የዛምቢያውያንን ገቢ የሚያሳድጉ፤የስራ እድል የሚፈጥሩና የገጠር አካባቢ የሚታየውን ድህነት መቀነስ ነበሩ።ቢሆንም የመንገድ መሰረተ ልማትን በማስፋፋትና ሃገሪቱን በግዛት በመከፋፈል ብዙ ሰርተዋል። ሰዎች በተቃዋሚነት ከሚያውቋቸው ማይክል ሳታ፤የዛምቢያን ንጽህና ለማሳደግ ቃል ሲገቡ ከነበሩት ማይክል ሳታ ብዙ ይጠብቁ ነበር። ይህንን ሁሉ ማሳካት አልቻሉም። በመሆኑም ሁኔታው እንደ ግለሰብ ለራሳቸውና ብዙ ይጠብቁባቸው ለነበሩት ደጋፊዎቻቸው አሳዛኝ ነው።''

ማይክል ሳታ በሃገራቸው በሚገኙ የቻይና እና የምዕራባውያን ባለወረቶች ደስተኛ ባለመሆናቸው በነገር ሸንቆጥ ያደርጓቸው ነበር። በቁጡ ንግግራቸው የአደገኛው የእባብ ዝርያ ኮብራ ንጉሥ (King Cobra) እየተባሉ ይጠራሉ። የዛምቢያ 50ኛ የነፃነት በዓል በተከበረ ማግስት የተሰማው መርዶ በዛምቢያ የውስጥ ጉዳይና በቀጠናው ላይ ስለሚፈጥረው ተጽዕኖ የተጠየቁት ማክዶናልድ ቺፐንዚ የሳታ ካቢኔ ጉዳዩን የሚያስተናግድበት መንገድ እንደሚወስነው ይናገራሉ።

''የዛምቢያ መረጋጋት፤ የውጭ ግንኙነት እና በሃገሪቱ ያሉ ባለወረቶች ጉዳይ የማይክል ሳታ ካቢኔ የስልጣን ሽግግሩን የሚያከናውንበት መንገድ ይወሰናል። ይፕሬዝዳንቱ ሞት በደቡባዊ አፍሪካ ቀጠና አስደንጋጭ ዜና ነው። ቢሆንም በቀጠናው ይህን ያህል ተሳትፎ አልነበራቸውም። ፕሬዝደንቱ በሞት የተለዩት ፓርቲያቸው በተከፋፈለበት እና የዛምቢያ ዜጎች አዲስ ህገ-መንግስት በሚጠብቁበት ወቅት ነው። እና ከዚህ ሁኔታ የምንወጣበትን መንገድ ፈጣሪ እንዲመራን እንጸልያለን።''

Guy Scott Sambia Präsident Übergang Vize
ተጠባባቂ ፕሬዚደንት ጊ ስኮትምስል Reuters/AP Photo

የዛምቢያ ምክትል ፕሬዝዳንት ትውልደ ስኮትላንድ የሆኑት ጊ ስኮት በዘጠና ቀናት ውስጥ ምርጫ እስኪካሄድ ሃገሪቱን እንዲመሩ ካቢኔው ወስኗል። የ77 አመቱ ፕሬዝዳንት ሞት በፓርቲያቸውና መንግስታቸው ውስጥ የስልጣን ሽኩቻ እንዳያስከትል ስጋት ፈጥሯል።

እሸቴ በቀለ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ