የዓለም የሠራተኞች ማህበርና ኢትዮጵያ
ረቡዕ፣ ኅዳር 12 2005
ኢትዮጵያ ከአርጀንቲኒያና፣ ካምቦዲያ፣ ፊጂና ፐሩ ተርታ በግምባር ቀደምትነት የሠራተኞች መብት ከሚጣስባቸው አምስት ሀገራት አንዷ መሆኗን ዓለም አቀፉ የሠራተኞች ድርጅት ILO ባሳለፍነው ሐሙስ ባወጣው ዘገባው አመላክቷል። ብሔራዊው የአስተማሪዎች ማሕበር ከአራት ዓመት በፊት ህጋዊ እውቅና ለማግኘት የኢትዮጵያን መንግስት ቢጠይቅም እስካሁን በህጋዊነት እንዳልተመዘገበ የዓለም አቀፍ ሠራተኞች ማህበር አስታውቋል። በቤልጂዬም በሚገኘው "ኤጁኬሽን ኢንተርናሽናል" በተሰኘው ድርጅት ውስጥ የሰብዓዊና ንግድ ማህበራት መብት ዋና አስተባባሪ የሆኑት ዶሚኒክ ማርሌት ይህንን ጉዳይ በቅርበት ተከታትለዋል፣
«ብሔራዊ የአስተማሪዎች ማህበር የተሰኘው የመምህራን ማህበር በህጋዊ መንገድ ለመመዝገብ ከመንግስት ፈቃድ እየፈለገ ነበር። ለተከታታይ አራት ዓመታት ይህ ነው የሚባል ተጨባጭ ምክንያት ሳይሰጠው ለሲቪል ማህበራት ፈቃድ ከሚሰጥ የመንግስት አካል መልስ ሳያገኝ ቀርቷል።»
የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር እየተባለ ይጠራ የነበረውና በ2000 ዓ,ም በፍርድ ቤት ሥሙን እንዲቀይር የተገደደው ራሱን ብሔራዊ የአስተማሪዎች ማህበር ብሎ የሚጠራ አካል በህጋዊ መንገድ ለመመዝገብ እንቅስቃሴ ከጀመረ ዓመታት አልፈዋል። ብሔራዊ የአስተማሪዎች ማህበር በህጋዊ መልኩ ምዘገባ እንዲያገኝ ከተንተንቀሳቀሱት ውስጥ አቶ ገሞራው ካሳ ግንባር ቀደሙ ናቸው። አቶ ገሞራው ማህበሩ በህጋዊ መልኩ እንዲመዘገብ ለረዥም ጊዜ ያደረጉት ጥረት አልተሳካም።
ገመቹ በቀለ
አርያም ተክሌ