1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓለም እግር ኳስ ግጥሚያ 30.06.2014

ማክሰኞ፣ ሰኔ 24 2006

።«አፍሪቃዉያን ጥሩ ይፋለማሉ» ፃፈ ኦ ግሎቦ የተሰኘዉ የብራዚል ዕለታዊ ጋዜጣ በዛሬ እትሙ «ግን ይሸነፋሉ» እያለ ቀጠለ ጋዜጣዉ።የናጄሪያ ሽንፈትም ከአልጄሪያዉ ብዙ የተለየ አይደለም።ጥሩ ተጫዉተዋል።በፈረንሳይ ሁለት ለዜሮ ከመሸነፍ ግን አላመለጡም።ጥሩ ፍልሚያ ግን ሽንፈት።ለምን?

https://p.dw.com/p/1CTs4
ምስል Reuters

የአፍሪቃ ብሔራዊ ቡድናት ብራዚል ከተያዘዉ የዓለም የእግር ኳስ የዋንጫ ግጥሚያ ሙሉ በሙሉ ተሠናበቱ።በዉድድሩ ከተሠለፉት አምስት የአፍሪቃ ቡድናት ለጥሎ ማለፍ ያለፉት የናጄሪያና የአልጄሪያ ቡድናት ትናንት በፍረንሳይና በጀርመን ቡድናት ተሸንፈዉ ከዉድድሩ ለመዉጣት ተገድደዋል።ይሁንና በፈረንሳይ የተሸነፈዉ የናጄሪያ ቡድንም ሆነ በጀርመን የተሸነፈዉ የአልጄሪያ ቡድን ያሳዩት ጠንካራ ፉክክር የብዙዎችን አድናቆት አትርፏል።በተለይ የአልጄሪያ ተጫዋቾች ማሸነፍ ባይችሉም በቡድንንም በግልም ያሳዩት የጨዋታ ጥበብ ለብዙዎቹ እንደ ምሳሌ እየተጠቀሰ ነዉ።

ለጥቂት ተረፍን» ይላል ሠፊ ስርጭት ያለዉ የጀርመን ዕለታዊ ጋዜጣ ቢልድ-የትናንት ማታ ግጥሚያን በገመገመበት መጣጥፉ።«ጀርመን በአልጀሪያ ብዙ ተጨንቃ ነበር» ይሕን ባዩ ዕዉቁ የጀርመን መፅሔት ነዉ።ዴር ሽፒግል።«በጠርዝ ላይ መራመድ» አከለ መፅሔቱ።ዙድ ዶች ሳይቱንግ የተሰኘዉ ጋዜጣ ደግሞ «አልቆልን ነበር---» የሚል ርዕሥ ሰጥቶታል ለዘገባዉ።

WM 2014 Achtelfinale Algerien Deutschland
ምስል Reuters

ብዙ ሌሎችም ብዙ ሌላ-ብለዋል።የሰሜን አፍሪቃዎችን ድፍረት፤ብልሐት፤ ሥልት ያበለ ግን የለም።ቼክ ሪፐብሊክ የሚኖሩት የዕግር ኳስ አሰልጣኝ ዶክተር ተስፋዬ ጥላሁን ደግሞ በሙያዊ አመክንዮ ይገልፁታል።

በመደበኛዉ ዘጠና ደቂቃ ኳስና መረብ አልተገናኙም።ሰላሳ ደቂቃ ተጨመረ።ለጀርመን ቡድን ተቀይሮ የገባዉ አንድሬ ሹርለ-የመጀመሪያዋን ጎል አስቆጠረ።መስዑት ኦዚል ሁለተኛዋን።ለአልጄሪያ ተለዉጦ የገባዉ አብደልሞመን ጃቡ ባለቀ ሰዓት አንድ ጎል አስቆጥሮ ነበር።ለዉጥ ግን አላመጠም።ጀርመን 2-አልጀሪያ 1።

«እንደሚመስለኝ መጨረሻ ላይ ያገኘ ነዉ ድል፤ ድል ለማድረግ አለቅጥ የመጓጓትና ጉጉቱ የፈጠረዉ ሐይል ነዉ።» የጀርመኑ ብሔራዊ ቡድን አሠልጣኛ ዮአኺም ሎቭ።የድሮዉ የዓለም ምርጥ እግር ኳስ ተጫዎች ዴጎ ማራዶን ግን አልጄሪያዎች የተሸነፉት «እራሳቸዉን በማሠራቸዉ ነዉ።» ይላል።እንጂ ባአካላዊ አጨዋወታቸዉ ላይ ድል ለማድረግ መንፈሳዊ ዝግጅት ቢኖራቸዉ ኖሮ ዉጤቱ ሌላ በሆነ ነበር።

ያም ሆን ይሕ ተሸነፉ።«አፍሪቃዉያን ጥሩ ይፋለማሉ» ፃፈ ኦ ግሎቦ የተሰኘዉ የብራዚል ዕለታዊ ጋዜጣ በዛሬ እትሙ «ግን ይሸነፋሉ» እያለ ቀጠለ ጋዜጣዉ።የናጄሪያ ሽንፈትም ከአልጄሪያዉ ብዙ የተለየ አይደለም።ጥሩ ተጫዉተዋል።በፈረንሳይ ሁለት ለዜሮ ከመሸነፍ ግን አላመለጡም።ጥሩ ፍልሚያ ግን ሽንፈት።ለምን?

WM 2014 Achtelfinale Algerien Deutschland
ምስል Reuters

ካሜሩን፤ጋና፤ ኮትዲቯር-አሁን ደግሞ ናጄሪያና አልጄሪያ ሁሉም ከዉድደሩ ወጡ።

ነጋሽ መሐመድ

ተክሌ የኋላ