1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓለም ባንክ ፕሬዚዳንትና አፍሪቃ

ዓርብ፣ መጋቢት 14 2004

የዓለም ባንክ ፕሬዚዳንት፣ ሮበርት ዞሊክ፤ ከ 5 ዓመት አገልግሎት በኋላ ፣ ሰኔ 23 ቀን 2004 ዓ ም ሥልጣናቸውን ያስረክብሉ። ዞሊክ፣ ዓላማዬ ብለው ያነሱት የነበረው ጉዳይ፤ በተለይ በአፍሪቃ ፣ረሀብና ማስወገድና ድህነትን መቅረፍ ነበሩ።

https://p.dw.com/p/14Qcg
ሮበርት ዞሊክምስል AP

እስከምን ድረስ ተሳክቶላቸዋል?መለስ ብለን እንመርምር።ዞሊክና አፍሪቃ በሚል ርእስ የዶቸ ቨለ ባልደረባ ዩሊያ ሃን ያቀረበችውን ዘገባ ተክሌ የኋላ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል።

ሮበርት ዞሊክ፤ ባለፈው መስከረም፤ በጉጉት ይጠባበቁ ለነበሩ ጋዜጠኞች፤ መድረክ ላይ በመውጣት አንድ ዐቢይ መግለጫ ማቅረባቸው ይታወሳል። ዞሊክ ፣ ያኔ እንዲህ ሲሉ ነበረ የተናገሩት።

«በበለጸጉት ሃገራት የተፈጠረው ቀውስ፣ በአዳጊ አገሮች ቀውስን ሊያስከትል ይችላል። ለቀሪው ዓለም ከዚያ የከፋ ችግር ከማስከተሉ በፊት፣አውሮፓ፣ ጃፓንና ዩናይትድ እስቴትስ፤ የደረሰውን ዐቢይ የኤኮኖሚ ችግር ለማስወገድ እርምጃ መውሰድ ይጠበቅባቸዋል። ያን አለማድረጉ ከኀላፊነት ነጻ አያደርግም።»

ዞሊክ፣ ያኔ ያነሱት ውዝግብም ሆነ ቀውስ፤ፈቀቅም አለ፤ በይበልጥ የተጎዱት ደግሞ የአፍሪቃ ሀገራት ናቸው። ወረቱ እየደረቀ ፤ ልማቱም እየተሰናከለ ነው። ቀደም ባለው ጊዜ እንደነበረው ሁሉ፣ በዓለም ውስጥ እጅግ የደኸዩ ከሚሰኙት 79 አገሮች መካከል 39ኙ ከአፍሪቃ ናቸው። ዞሊክ እ ጎ አ፤ በ 2007 ዓ ም፤ የዓለም ባንክ ፕሬዚዳንት ይሆኑ ዘንድ በቡሽ አስተዳደር መመረጣቸው ያከራከረ ጉዳይ ነበር። ከእርሳቸው በፊት በዚያው የሥልጣን ቦታ ላይ እንደነበሩት ፖል ዎልፎዊትዝ(ቮልፎቪትዝ)ሁሉ፣ የቀድሞው የፖለቲካ ሰው ሮበርት ዞሊክም፤ እ ጎ አ በ 2003 ዓ ም በተካሄደው የኢራቅ ጦርነት ኀላፊነቱ ከሚመለከታቸው መካከል አንዱ ናቸው። መጀመሪያ ላይ ፤ ያን ያህል ተቀባይነት ያላገኙት ዞሊክ፤ ውሎ አድሮ ፤ በለንደን፣ Africa Business Magazine የተሰኘው መጽሔት አዘጋጅ ኬንያዊው አንቨር ቨርሲ እንደሚሉት፣ በብዙ አፍሪቃውያን ዘንድ አዎንታዊ አስተያየት ነው የተቸራቸው።

«እንደሚመስለኝ፤ አቶ ዞሊክ፣ በአመዛኙ የሚታወሱት የዓለምን ባንክ ትክክለኛ የአብዝሃ መንግሥታት ተቋም በማድረጋቸው ነው። እርሳቸው ያደረጉት እንደሚመስለኝ፤በአብዛኛው ከአሜሪካ የኤኮኖሚና የፖለቲካ አወቃቀር ጥላ ሥር አላቀው በትክክል ዓለም አቀፋዊ ማድረግ ነው።»

ከዚህም ጋር ፤ የኤኮኖሚ ጉዳዮች ተንታኝ፣ ቨርሲ እንዳሉት፣ ከአዳጊ አገሮችና ከእነርሱም አንድ እመርታ ካሳዩት መንግሥታት ሥራ አስፈጻሚዎችን መርጠዋል። የሆነው ሆኖ፣ ከ 24 ቱ የባንኩ የምክር ቤት መናብርት 3ቱ በአሁኑ ጊዜ የተያዙት በአፍሪቃውያን ነው። በዓለም አቀፉ የፋይናንስ ውዝግብ ወቅት፣ዞሊክ ከልማት ባንካቸው፣ የሥራ ማንቀሳቀሻው ወረት መጠን፣ በቢሊዮኖች በሚቆጠር ዶላር ከፍ እንዲል አድርገዋል። ይህም በ 20 ዓመታት ውስጥ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑ ነው። በበለጸጉት አገሮች፤ ግምጃ ቤቱ የማያወላዳ መሆኑ ቢታወቅም፤ ዞሊክ 70 ቢልዮን ዶላር ያህል ገንዘብ፣ በዓለም አቀፉ የልማት ድርጅት (IDA) በኩል የተመደበው ገንዘብ፣ በዓለም ውስጥ እጅግ ለደኸዩት አገሮች እንዲሰጥ አድርገዋል።

Jahrestagung von IWF und Weltbank in Istanbul Flash-Galerie
የዓለም ባንክና የዓለምአቀፉ የገንዘብ ድርጅት(IMF)ዓመታዊ ጉባዔምስል AP

4«ብዙዎቹን የአፍሪቃን መሪዎች ስታናግሯቸው፣ አውሮፓ ከ 40,50 ም ሆነ 60 ዓመታት በፊት ያከናወኑትን እነርሱም ተጋባራዊ ለማድረግ ፍላጎቱ አላቸው። ለምሳሌ ያህል መሠረተ-ልማት ይሻሉ። የኃይል ምንጭ--ከዓለም አቀፉ ገበያ ጋር የሚያገናኝ፣ አካባቢያዊ ትሥሥር፣ እንዲሁም የግሉን የኤኮኖሚ ዘርፍ መደገፍ ይፈልጋሉ።ስለዚህ እንደ ጥገኞች ብቻ ሳይሆን፣ ማየት ያለብን፣ ለመጪው ጊዜ ዕድገትም መሠረት እንዲጣልላቸው እንሻለን።»

እ ጎ አ በ 2010 ዓ ም፤ ዶቸ ቨለ ባደረገላቸው ቃለ-ምልልስ ነበረ ፣ ዞሊክ ይህን ያሉት። የልማት ስልታቸው፣ ከሀገራቱ ጋር በ,ተባበር የኤኮኖሚ ዕድገትን መቀየስ መሠረተ ልማትን መገንባት፤ ባለሃብቶችን ማማለል፣ የሚበጅ መሆኑን ነበረ የተናገሩት። የጀርመን የልማት ፖለቲካ ተቋም(DIV)ባልደረባ ዩሊያ ላይኒንገር ፤ ይህ ማለት፤ ድህነትን ለመቀነስ ይበጃል ማለት አይደለም ሲሉ ያስገነዝባሉ። የቅርብ ጊዜውን የኦለም ባንክ መዘርዝር ጥናትም በመጥቀስ፣ እጅግ አስከፊው ድህነት በአዳጊ አገሮች እ ጎ አ ከ 1990-2010 ግማሽ በግማሽ ቀንሷል መባሉን ያስታውሳሉ። በዚህ ውጤት መሠረት፣ የተባበሩት መንግሥታት የዓእማቱ ዓላማ ከታሰበው 5 ዓመት ቀደም ብሎ ግቡን ይመታ ነበር ማለት ነው። እንደ ዩልያ ላይኒንገር ፤ የድሆች ቁጥር የቀነሰው በቻይና ብቻ ነው።

«ወደ አፍሪቃ ፊቱን የሚመልስ ማንኛውም ሰው፤ የወጤቱ አዎንታዊነት አነስተኛ መሆኑን ይገነዘባል። በዚያ የድሆች ቁጥር ጨመረ እንጂ አልቀነሰም። ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ በጣም አሉታዊ ይዞታን አመላካች ሆኗል። ይህ ማለት፤ የዓለም ባንክ የተሣካ ውጤት ተገኘ ያለው ፣ ገሐዳዊውን ይዞታ እንደሚያንጸባርቅ ያረጋግጣል ማለት ነው።»

ባለፉት 20 ዓመታት ዩልያ ላይኒንገር እንደሚሉት፣ በአፍሪቃ የድሆች መጠን የ 26 ሚልዮን ጭማሪ አሳይቷል። ሮበርት ዞሊክ ለተተኪያቸው እጅግ ከባድ የሆነ ኀላፊነት አሸክመው ነው የሚሰናበቱት።

ተክሌ የኋላ

ሒሩት መለሰ