የወልቃይት ነዋሪዎች ወቀሳ
ዓርብ፣ መጋቢት 16 2008ማስታወቂያ
ከወልቃይት ህዝብ የአማራ ማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት አቶ ሊላይ ብርሃነ በመጥፋታቸው በዳንሻ አካባቢ የተቃውሞ ሰልፍ ተካሂዷል። ከኮሚቴው አባላት መካከል አንዱ የሆኑት ኮሌኔል ደመቀ ዘውዴ ለዶይቼ ቬለ እንደተናገሩት የወልቃይት ህዝብ ባነሳው የማንነት ጥያቄ ምክንያት በአካባቢው ማህበረሰብ ተቀባይነት ያላቸው ግለሰቦች በጸጥታ ሃይሎች ታፍነው እየተወሰዱ ነው።
«ጥያቄያችንን ለማዕከላዊ መንግስት አቅርበን ምላሽ እየጠበቅን ነው» የሚሉት ኮሌኔል ደመቀ ዘውዴ የአካባቢው ነዋሪዎች የጸጥታ ኃይሎች በሚፈጽሙት ወከባ እና እንግልት ምክንያት የመኖሪያ ቀያቸውን ጥለው መሰደድ ጀምረዋል ይላሉ።
በወልቃይት ወረዳ በዳንሻ ከተማ በንግድ ሥራ ይተዳደሩ የነበሩት አቶ ሊላይ ብርሃነ የአካባቢውን ነዋሪ ጥያቄ ለማዕከላዊ መንግስት በማቅረባቸው በጸጥታ ኃይሎች ሳይታፈኑ አሊያም ሳይገደሉ አይቀርም የሚል ስጋት ተፈጥሯል። ከዚህ ቀደምም ተመሳሳይ ጥያቄ ያነሱ የነበሩ ወደ 116 የሚደርሱ ሰዎች መጥፋታቸውንና አሁንም አስር ወጣቶች በሁመራ በእስር ላይ እንደሚገኙ ኮሌኔል ደመቀ ዘውዴ ተናግረዋል።
በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የጠየቅናቸው የኢትዮጵያ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ባልደረባ ጥያቄው ተቋማቸውን እንደማይመለከት ተናግረዋል።
እሸቴ በቀለ
ሒሩት መለሰ