የኮሎኙ «ካርነቫል» እና የፀጥታ ጥበቃው
ሐሙስ፣ ጥር 26 2008እስከ ፊታችን ማክሰኞ በሚቀጥለው በዚሁ የአደባባይ ድግስ እና ፈንጠዝያ ወቅት ጀርመናውያኑ ባለስልጣናት የፀጥታ ጥበቃ ዋስትናውን እንዲያረጋግጡ ግዙፍ ግፊት አርፎባቸዋል። ይኸው የፀጥታ ስጋት የሕዝቡን የፈንጠዝያ ስሜት ይቀንሰው ይሆን?
«ካርነቫል» በሚከበርባቸው የራይን ወንዝን በሚያዋስኑ ኮሎኝ፣ ዱስልዶርፍ እና ማይንስን በመሳሰሉ ከተሞች የሚኖሩ ጀርመናውያን ፊታቸውን የተለያዩ ቀለማት በመቀባት፣ የተለያዩ አልባሳትን በማጥለቅ በአደባባይ ፣ በተለያዩ አዳራሾች እና ቡና ቤቶች በመሰብሰብ ዕለቱን በዘፈን እና በፈንጠዝያ ያሳልፉታል። የፊታችን ሰኞ ለሚከበረው እና «ሮዝንሞንታግ» ለሚባለው ዋናው የ«ካርነቫል»አደባባይ ድግስ እና ፈንጠዝያም ከአንድ ሚልዮን የሚበልጥ ሰው እንደሚጠበቅ ያካባቢው ባለስልጣናት አስታውቀዋል።
የተመ የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት፣ በምህፃሩ «ዩኔስኮ» ለብዙ የኮሎኝ ነዋሪዎች ትልቅ ባህላዊ ትርጓሜ የያዘውን ይህንኑ የራይን አካባቢ «ካርኒቫል»ን እጎአ በ2015 ዓም የተጠበቀ ቅርስ በሚል መዝግቦታል። የኮሎኝ ነዋሪዎች «ካርነቫል»ን ልክ እንደ ራይን ወንዝ እና በከተማቸው እንደሚገኘው ትልቁ የዶም ቤተ ክርስትያን፣ ልዩ የከተማይቱ መለያ አድርገው ይመለከቱታል። በዚህም የተነሳ የዘንድሮው የ«ካርነቫል» ድግስ ካላንዳች ጥቃት እንዲያልፍ የብዙዎች ፍላጎት ነው። የኮሎኝ ከተማ ከፍተኛ ባለስልጣናት በዓሉ አስተማማኝ በሆነ መንገድ የሚካሄድበት ሁኔታ የፀጥታ ኃይላቱ የጥበቃ ብቃታቸው የሚፈተንበት ተግባር አድርገው ማስቀመጣቸውን የኮሎኝ ፖሊስ ዋና ኢንስፔክተር ቮልፍጋንግ ባልደስ ገልጸዋል።
« በአዲስ ዓመት ዋዜማ የተፈፀመው ጥቃት በአሁኑ የ«ካርኒቫል» አከባበር ፀጥታ ጥበቃ እቅድ ላይ ተፅዕኖ አሳርፏል። በኮሎኝ ይህ ዓይነት ሁኔታ ተፈጥሮ አያውቅም። ቀደም ባሉት ጊዚያት በየዓመቱ የምናደርገው በከተማይቱ በበዓሉ ላይ የተሳተፉ ሰዎችን፣ የተፈፀሙ ወንጀሎችን እና የደረሱ ግጭቶችን በተመለከተ በቀዳሚው ዓመት ካገኘናቸው መረጃዎች በመነሳት ነበር እቅድ የምናወጣው። አሁን ግን ሁኔታው ለየት ያለ ነው። በመሆኑም፣ የፀጥታ ማስጠበቁን ርምጃችንን በጣም አጠናክረናል። ማለትም፣ በከተማይቱ ብዙ ኃይል አሰማርተናል። የፀጥታ ማስጠበቁን መመሪያ ማዘጋጀቱን በተመለከተም ከኮሎኝ ከተማ አስተዳደር እና የ«ካርኒቫል» አዘጋጅ ኮሚቴ ጋር በቅርብ ትብብር እየሰራን ነው። »
የፀጥታ ማስጠበቁ መመሪያን የሚመለከት ማንኛውም ሰው የከተማይቱ ባለስልጣናት ሁኔታው ምን ያህል እንዳሳሰባቸው ሊረዳ ይችላል። ድግሱ እና ፈንጠዝያው በሚደራባቸው ዋነኞቹ የኮሎኝ ከተማ አካባቢዎች ግዙፍ መብራቶች ከመተከላቸው ጎን፣ ሴት ፖሊሶች እና የስነ ልቡና ባለሙያዎች ምናልባት ድንገት የክብረ ንፅህና መደፈር ጥቃት ለሚደርስባቸው ሴቶች ሰለባዎች ርዳታ የሚሰጡበት አንድ ማዕከልም በመሀል ከተማ ተቋቁሞዋል።
ዳንየል ሀይንሪኽ /አርያም ተክሌ
ነጋሽ መሀመድ