የኬንያ ፓርላማ በICC ስምምነት ላይ ተከራከረ
ረቡዕ፣ ነሐሴ 29 2005በመጪዎቹ ሳምንታት የኬንያ ምክትል ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ የክስ ሂደት ደን ሀግ ላይ በዓለም ዓቀፉ የጦር ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት (ICC) ይታያል። ባለስልጣኑ እኢአ በ2007 ዓ ም ከተካሄደው ምርጫ በኋላ ደም የተፋሰሰበት አመፅ እንዲካሄድ አነሳስተዋል በሚል 3 ወንጀሎች ክስ ተመስርቶባቸዋል። በተጨማሪም ፕሬዝዳት ኡሑሩ ኬንያታ ላይ የቀረበዉ ክስ ቀነ ቀጠሮዉ ደርሷል። ህዳር 3 2006 ዓ,ም። የተከሰሱት አስገድዶ መድፈርን ጨምሮ፣ በግድያ እና ህዝብን ከኖረበት ቀየ በማፈናቀል ነው። ምንም እንኳን ሀገሪቱን ከICC ዉል ፈራሚነት ለማዉጣት ትናንት ፓርላማው ሲከራከር ቢውልም፤ በፍርድ ቤቱ የተጀመረዉ የክስ ሂደት ላይ ለዉጥ አይኖርም። ይህን ሀሳብ በናይሮቢ የሲቪል እና የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ጋሺሂ ጋቼኬ ይጋራሉ፤
«ፊርማቸዉን ለማንሳት ማመልከቻ ቢያስገቡም ኬንያን ከICC ስምምነት ለማዉጣት ቢያንስ አንድ ዓመት ሊወስድ ይችላል። በዚያ ላይ የስምምነቱ ዉል እስኪያበቃ ድረስም ሌላ ጉዳይ ካልመጣ በቀር ፍርድ ቤቱ የቀረበለትን ጉዳይ አያስቆምም።»
የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ጋቼኬ በኬንያ ምርጫ በተካሄደ ቁጥር ግጭት ሲነሳ እንደቆየ ያስታውሳሉ። የተባበሩት መንግስታት እና ICC ከሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጋ በመተባበር ጥፋተኞች ለፍርድ መቅረብ ጀመሩ እንጂ ይህ መንግስት በዚህ ረገድ ምንም አስተዋፅዎ አላደረገም ባይ ናቸው።
«ይህ መንግስት በኃይል ነው ስልጣን የያዘው። የራሳቸውን ጎሳ አባላት ለድጋፍ እንዲነሳሱ ሰፊ ቅስቀሳ አድርገዋል። ጥምረቱ እንዴት እንደተመሠረተም የሚታወቅ ነው። እናም ለማህበራዊ ፍትህ ፍላጎት ያላቸው አይመስለኝም። ምክንያቱም ታሪካቸዉን እንኳ ብንመለከት የኡሑሩ ኬንያታም ይሁን የዊሊያም ሩቶን ታሪክ ስንመለከት በ1992 እና በ1997 የት ነበሩ? ካኖ አካባቢ ነበሩ። ነገር ግን ግድያ ሲፈፀም አንዴ እንኳን ለምን ብለዉ ጥያቄ አላቀረቡም። ስለዚህ ለኬኒያውያን ፍትህ በግንባር ቀደምትነት ቆማዋል ለማለት ያስቸግራል።»
በአንጻሩ ኬንያ ዉስጥ እንደ እሳቸዉ ሁሉ ለሲቪል እና ለሰብዓዊ መብቶች የሚሟገቱ አካላት በምርጫ ጊዜ ሀገሪቱ ዉስጥ የታየው አይነት በደል በሰዎች ላይ እንዳይከሰት ስላደረጉት ጥረት ሲገልጹ፤
« ባለፈው አርብ ደብዛቸው የጠፋበት ሰዎች በአለም አቀፍ ደረጃ በሚታሰቡበት ዕለት መግለጫ አዉጥተናል፤ በዚህም ለተከሰተዉ ታሪካዊ የፍትህ ጉድለትና ለተፈጸመዉ ግድያ ተጠያቂዎች ለፍርድ እንዲቀርቡ ጥሪ አቅርበናል። በተጨማሪም ለፍትህ ስንታገል እንደነበረው ዘመቻችንን እንቀጥላለን፣ ኬንያውያንን በማስተባበርም፣ ምክር ቤቱ የሚያካሂደዉ ክርክር ለሀገሪቱ ሳይሆን የግለሰቦችን ፍላጎት ለማሳካት ብቻ እንደሆነ እናስረዳለን።»
የኬንያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውሳኔ የICCን ውል ማፍረስ ከሆነ ኬንያ የመጀመሪያዋ የዚህ ውል አፍራሽ ሀገር ትሆናለች። የኬንያ ፓርላማ ምክትል ፕሬዚዳንት ጆይስ ላቦሶ ትናንት እንዳሳወቁት የምክር ቤት አባላቱ በጉዳዮ ላይ መክረው ውሳኔያቸውን ነገ እንዲያሳውቁ ቀጠሮ ተይዟል። እስካሁን ምክር ቤቱ የደረሰበት ዉሳኔ ይፋ ባይደረግም፤ ጉዳዩ ግን ከፍተኛ ክርክር እንደሚያስነሳ ተገምቷል።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሰ