1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የከተሞች ፎረም በጅግጅጋ እየተከበረ ነው

ቅዳሜ፣ የካቲት 9 2011

በሀገሪቱ ያሉ ችግሮችን በተገቢው ጊዜ ለመፍታት ኢትዮጵዊ አንድነትን ከምንግዜውም በላይ አጠናክሮ መረባረብ እንደሚገባ በ8ኛው የከተሞች ፎረም መክፈቻ ላያ የተገኙት የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ አስገነዘቡ። የክልሉ መንግስት ዝግጅቱ የጠፋውን የአካባቢው መልካም ገፅታ ይቀይራል የሚል እምነት እንዳለው የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/3DW2O
Jijiga - Feier zu 4th Ethiopian Cities Forum
ምስል DW/M. Teklu

8ኛው የከተሞች ፎረም

 “መደመር ለሀገራችን ከተሞች ብልፅግና” በሚል መሪ ሀሳብ ዛሬ በጅግጅጋ ከተማ የተጀመረውን የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም በይፋ የከፈቱት የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ የምንገኝበት ጊዜ ያሉብንን ችግሮች በፍጥነትና በጥራት ከመስራት ውጭ አማራጭ የሌለበት ነው ብለዋል።

ፕሬዝዳንቷ ያሉብንን ችግሮች ለመፍታት ጊዜ እንደሌለን በመገንዘብ ኢትዮጵያዊ አንድነታችንን አጠናክረን መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል በንግግራቸው።

Jijiga - Feier zu 4th Ethiopian Cities Forum: Präsidentin Sahle-Work Zewde
ምስል DW/M. Teklu

ክብርት ፕሬዝዳንት ሳሕለወርቅ ከረዥም ጊዜ በፊት እንደሚያውቋት በገለፇት ጅግጅጋ ከተማ ባዩት ሁለንተናዊ ለውጥ መደሰታቸውን ጠቁመው ፎረሙን በይፋ ከፍተዋል።

የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚንስቴር ሚንስትር አቶ ጃንጥራር አባይ በበኩላቸው ፎረሙ በሀገሪቱ በቁጥር እያደጉ የሚገኙ ከተሞች ልምድ የሚለዋወጡበት ከመሆን ባለፈ በሚንስቴሩ የተቀመጠውን ራዕይ ለማሳካት ይረዳል ብለዋል ፡፡

የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፋ መሀመድ በስነ ስርዓቱ ላይ እንዳሉት 8ኛው ከተሞች ፎረም በዓል ህዝቡ በክልሉ በነበረው አምባገነን ስርኣት ሲፈፀሙ የነበሩ የአስተዳደር ፣ የመልካም አስተዳደር በደልና ሌሎች ችግሮች ታግሎ በለወጠበት ማግስት የመጣ ድርብ ድል ነው።

Jijiga - Feier zu 4th Ethiopian Cities Forum
ምስል DW/M. Teklu

አቶ ሙስጠፌ በቅርቡ ተፈጥሮ የነበረውን ጠባሳ በመሻር ህዝቡ የሚታወቅበትን ደግ፣ እንግዳ ተቀባይና ሀይማኖተኛነቱን የሚያሳይበት እንደሚሆንም አረጋግጠዋል።

አንድ መቶ ስልሳ ዘጠኝ የኢትዮጵ ከተሞችና ከተጎራባች ሀገራት የጅቡቲ ፣ የሶማሌ ላንድ ከተሞች ሀርጌሳ እና በርበራ በዚሁ ፎረም ላይ ተሳታፊ ሆነዋል ፡፡ የተሌዩ የፌደራልና የክለል ስራ ሀላፊዎች በተገኙበት የተጀመረው ፎረም በኤግዚብሽን በፓናል ውይይት እና መሰል ዝግጅቶች እስከ መጪው ሀሙስ የሚቀጥል ይሆናል።

መሳይ ተክሉ

እሸቴ በቀለ