1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮ-ሱዳን ዉዝግብ

ሰኞ፣ ጥር 24 2013

ባለፉት ጥቂት ወራት ከአዲስ አበባና ከካርቱም የምንሰማዉ ግን 50 ዓመት የዘለቀዉን ዉል ማክበር ሳይሆን የዉጊያ ፉከራ ቀረርቶ ነዉ።የኢትዮጵያ መንግሥት ባለስልጣናት በተደጋጋሚ እንዳስታወቁት የሱዳን ጦር ድንበር አልፎ በርካታ አካባቢዎችን ተቆጣጥሯል።ሱዳን በዚሕ ወቅት የኢትዮጵያን ግዛት በኃይል የያዘችበት ምክንያት እንደየተመልካቹ የሚለያይ ነዉ።

https://p.dw.com/p/3ogVu
Afrikanische Union Gipfeltreffen
ምስል Manasse Wondamu Haalu/AA/picture alliance

የኢትዮ-ሱዳን ዉዝግብ፣ ምክንያትና መፍትሔዉ

የካርቱምና የአዲስ አበባ ገዢዎች ሲወዳጁ ሕዝባቸዉን ወድማማች እሕትማማች እያሰኙ ያስጨፍሩ-ያዘምሩታል።ዐሕዋን ዐሕዋን ኢትዮጵያ ወ ሱዳን እንደሚባለዉ።» ሲጋጩ «ታሪካዊ» ጠላትነታቸዉን እያስፈከሩ ሲያላትሙት ዘመናት አስቆጠሩ።ሐቻምና ይሔኔ የአዲስ አበባ መሪዎች ካርቱሞችን ሸምጋይ፣አስታራቂ፣ ለሱዳን ሕዝብ ችግር ደራሽ ነበሩ።ፍቅር፣ወዳጅነት፣ መደጋገፉ በሁለተኛ ዓመቱ ዘንድሮ በንንኖ ለዉጊያ የሚፈላለጉ ጠበኞች ሆኑ።ጠቡ መነሻ፣ ነባር ግንኙነታቸዉ ማጣቃሻ፤ መፍትሔዉ መድረሻችን ነዉ።

«እኛ ራሳችን ከባለሥልጣኖቹ ጋራ ተገናኝተን ቃል በቃል ብንነጋገር እንደሚሻል ኮሎኔል ሳንድፎርድና ቻፕማን አንድርዉስ ስለ ገለፁልን፣በሰኔ 25 ቀን 1932 ዓም ከዋዲ ሐልፋ በቡር ወደ ካርቱም ገባን---» አፄ ኃይለ ስላሴ፣ ሕይወቴና የኢትዮጵያ ርምጃ ገፅ 192።

ያኔ፣ ሱዳን የብሪታንያ ቅኝ ተገዢ፣ ኢትዮጵያ የኢጣሊያ ተወራሪ፣ ንጉሱም ስደተኛ ነበሩ።ንጉሱ ሐገራቸዉን በብሪታንያ ድጋፍ ከኢጣሊያ ነፃ ለማዉጣት ለሚያደርጉት ዉጊያ ዝግጅት ሱዳን ሲገቡ  ካርቱምን አወቋት።

ኢትዮጵያ ነፃ ወጥታ፣ ንጉሱ «ስዩመ እግዚአብሔርነታቸዉን» አጠናክረዉ፣ የካቲት 1967 (ከዚሕ በኋላ ያለዉ ዘመን በሙሉ እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር ነዉ) ካርቱምን ዳግም ግን ዘለግ ላለ ጊዜ ሲጎበኙ ሱዳን ከብሪታኒያ ቅኝ አገዛዝ ሙሉ በሙሉ ነፃ የወጣችበትን 10ኛ ዓመት አክብራ፣ ከቅኝ ገዢዋ የወረሰችዉን የድንበር ጉዳይ ማማተር ጀምራ ነበር።

ይሁንና የሱዳን የመጀመሪያ ጠቅላይ ሚንስትርና የኋላዉ ፕሬዝደንት ኢስማኤል ኤል አዝሐሪ፣ በአፍሪቃ አንድነት ድርጅት መመስረት ሰበብ በአፍሪቃዉያን ዘንድ ስም ዝናቸዉ የገነነዉን ንጉሰ ነገሠት በቀጥታ ከመጋፈጥ ይልቅ ሞቅ፣ ደመቅ ባለ መስተግዶ አባብሎ፣ በዲሞሎማሲዉ ቋንቋ ጉዳዩን ማንሳቱን ሳይፈቅዱ አልቀረም።

Äthiopien Sudan Premierminister Abiy Ahmed und General Abdel Fattah Al-Burhan Abdelrahman
ምስል Reuters/M. N. Abdallah

አዝሓሪ ንጉሱን ካርቱም አዉሮፕላን ማረፊያ ሲቀበሉ «ርዕሠ-ከተማችን ካርቱም በመምጣትዎ በጣም ደስ ብሎናል።ስለ ካርቱም ጥሩ ትዉስታ እንደሚኖርዎት እርግጠኞች ነን----» እያሉ ዉለታችንን እንዳይረሱ ዓይነት ዘወርዋራ መልዕክታቸዉን ቀጠሉ ፕሬዝደንቱ።

የንጉሱ አፀፋም ያኔ የሰሙ እንደፃፉት የዲፕሎማሲ ብስለት፣ጥንቃቄ፣ ብልሐትንም የቀየጠ ነበር።

«----የሁለቱ ሐገሮቻችን ወዳጅነት፣ በጦርነትም በሰላምም ጊዜ በደም የተሳሰረ በመሆኑ ከወዳጅነትም የበለጠ ነዉ።-----የማንተፈታዉ ችግር አይኖርም።»

ችግሩ በተለይም የብሪታንያ ቅኝ ገዢዎች ያወሳሰቡት የድንበርና የዉኃ አጠቃቀም ጉዳይ ዛሬም ድረስ መፍትሔ አለማግኘቱ በርግጥ የመሪዎቹን ብልጠት፣ብስለት ጥረቱንም ከንቱ የሚያስቀር ምናልባም አሳዛኝ ነዉ።የኢትዮጵያ የስትራቴጂ ጥናት ማዕከል የበላይ ኃላፊ ሙከረም ሚፍታሕ እንደሚሉት እስካሁን ከተደረጉት ጥረቶች ሁሉ የተሻለዉ ግን ያዉ በአፄ ኃይለ ስላሴ ዘመን በ1972 የተደረገዉ ዉል ነዉ።

ባለፉት ጥቂት ወራት ከአዲስ አበባና ከካርቱም የምንሰማዉ ግን 50 ዓመት የዘለቀዉን ዉል ማክበር ሳይሆን የዉጊያ ፉከራ ቀረርቶ ነዉ።የኢትዮጵያ መንግሥት ባለስልጣናት በተደጋጋሚ እንዳስታወቁት የሱዳን ጦር ድንበር አልፎ በርካታ አካባቢዎችን ተቆጣጥሯል።ሱዳን በዚሕ ወቅት የኢትዮጵያን ግዛት በኃይል የያዘችበት ምክንያት እንደየተመልካቹ የሚለያይ ነዉ።

የሶማሊያ የፖለቲካ ተንታኞች እንደፃፉት የሶማሊያ የጦር አበጋዞች የገጠሙት ጦርነት ሐገራቸዉን በሚያወድምበት በ1990ዎቹ የመጀመሪያ አጋማሽ የአዲስ አበባና የካይሮ ገዢዎች ተቃራኒ ኃይላትን ይረዱ ነበር።በግብፅና በግብፅ በኩል በዩናይትድ ስቴትስ ከሚደገፉት ከዓሊ መሕዲ መሐመድ ጋር የሚቀናቀኑት የቀድሞዉ ጄኔራል፣ ዲፕሎማትና የኋላዉ የጦር አበጋዝ መሐመድ ፋራሕ ሐሰን አይዲድ በ1994 ግድም ለተከታዮቻቸዉ ባደረጉት ንግግር «ከእንግዲሕ ለአባይ ዉኃ የሶማሌዎች ደም መፍሰስ የለበትም» ብለዉ ነበር።ቃላቸዉ ገቢር መሆን አለመሆኑን አናዉቅም።ሱዳኖችስ?

Grenze Äthiopien Sudan
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

የዉጪ ጉዳይ ሚንስቴር ቃል አቀባይ ዲና ሙፍቲ ቀጥተኛ መልስ የላቸዉም።የዛሬ ሁለት ሳምንት ግድም እንዳሉት ግን ካርቱሞች የኢትዮጵያን ዉጥረት ዓይተዉ የሌሎችን ተልዕኮ እያስፈፀሙ ነዉ።

የሱዳን ባለስልጣናት ጦራቸዉ የሱዳንን ግዛት ከመቆጣጠር ባለፍ የኢትዮጵያን ግዛት አልነካም ባይ ናቸዉ።የሱዳኖች ምክንያት ለዶክተር ሙከረም ሚፍታሕ እንቆቅልሽ አይነት ነዉ።የፖለቲካ ተንታኙ እንደሚሉት ሱዳን ከኢትጵያ ይልቅ ሰፊ ግዛት ይዛብኛለች የምትለዉ ግብፅን ነዉ።የካርቱም ገዢዎች ግብፅን ትተዉ ኢትዮጵያን መተናኮላቸዉ ዶክተር ሙከረም እንደሚሉት አስገራሚ ነዉ።

ብዙዎች ጠይቀዋል።የኢትዮጵያ መንግስግት ባለስልጣናት ካሜራ ማይክራፎን ፊት በግልፅ አይናገሩት እንጂ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ «ሌሎች» ያሉት፣ ከካርቱሞች ጀርባ ካይሮዎች መኖራቸዉን አመልካች ነዉ።

የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት የካይሮ መሪዎች ካርቱሞችን በዚሕ ሰዓት «ጃስ» የሚሉበት ምክንያት ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ ማስገንባቷን ለማሰናከል፣ ወይም እነሱ የሚፈልጉትን አዲስ አበባ እንድትፈፅም ለማስገደድ ሊሆን ይችላል።ሕዝባዊ አመፅ ያየለባቸዉን የሱዳንን የረጅም ጊዜ ገዢ ዑመር ሐሰን አልበሽርን ከስልጣን ያስወገዱት የጦር ጄኔራሎች በኃይል የያዙትን ስልጣን እንደያዙ እንዲቀጥሉ የካይሮ ገዢዎች ከፍተኛ ግፊት ሲያደርጉ ነበር።

የካይሮዎችን ግፊት ኤምባሲያቸዉ ድረስ በመሔድ በአደባባይ ሠልፍ አክሽፎ ተጣማሪ መንግስት እንዲመሠረት ያደረገዉ የሱዳን ሕዝብ ነዉ።በሱዳን ሕዝብ የሕይወት፣ደም አካል መስዋዕትነት፣ በኢትዮጵያ አደራዳሪነት ስልጣን የተጋሩት የሱዳን የሲቢል ፖለቲከኞች አሁን ለካይሮዎች ግፊት «ሸብረክ» የማለታቸዉ ሚስጥር አሁንም ለብዙዎች ሚስጥር ነዉ።

ዶክተር ሙባረክ ግን የሱዳንን ሁለንተናዊ ሁነትና ሒደት የሚዘዉረዉ ጦሩ ነዉ ባይ ናቸዉ።የሱዳን ጦር፣ መለዮቸዉን  ባወለቁት ጄኔራል የምትገዛዉ ግብፅ «ጉዳይ አስፈፃሚ» ቢሆን ብዙ አይደንቅም።የሱዳን የጦር ጄኔራሎች፣ ከመቶ ዓመት የበለጠዉን የኢትዮ-ሱዳን የድንበር ጉዳይ በዚሕ ሰዓት ለሐገራቸዉ «ብሔራዊ  ደሕንነት» አስጊ አድርገዉ የሚያራግቡበት ሌላ ምናልባትም የግብፅን ተልዕኮ ከማስፈፀምም የበለጠ ምክንያት አላቸዉ።

ዶክተር ሙከረም እንደሚሚሉት የሱዳን ተጣማሪ መንግስት የአልበሽርን ሥርዓት ከስልጣን ያወረደዉን ሕዝብ ጥያቄን እስካሁን አልመለሰም። የአፍሪቃ ሕብረትና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሠላም አስከባሪ ሠራዊት (ዩናሚድ) ከዳርፉር መዉጣቱ ዳርፉሮችን ለከፍተኛ ሥጋትና ተቃዉሞ ዳርጓል።የጦር ኃይሉና የሲብል አስተዳደሩ የሰከነ አመራር መስጠት አልቻሉም።እና በተንታኙ እምነት የሕዝብን የትኩረት አቅጣጫ ለማስቀየር ኢትዮጵያን አገኙ።

BG Sudan Proteste
ምስል Getty Images/AFP/E. Hamid

ኢትዮጵያ በጎሳና በፖለቲካ ቀዉሶች መታበጥዋ።በሁለቱም ሐገራት የተያዘዉ ሽግግር በተፈለገዉ መንገድና ፍጥነት አለመቀጠሉና በሁለቱም ሐገራት በቅጡ ያልጠኑትን መንግሥታት እጆች  የሚጠመዝዙ ኃይላት መጠናከር አል ፋሽጋ ላይ የሆነዉ እንዲሆን ምክንያት ሆኗል።

መፍትሔ ነዉ ናፋቂዉ።የከፋ ደም መፋሰስን ለማስቆም ብዙዎች እንደሚያምኑት አብነቱ ድርድር ነዉ።ድርድሩ ጋ ለመድረስ፣ ጠቡን የሚያባብሱ ቃል-እርምጃዎችን መግታት።

የኢትዮጵያ ባለስልጣናት እንደሚሉት ለመደራደርም ሆነ ድንበሩን ለማካለል የነበረዉ፣ ወደነበረበት መመለስ አለበት።የሱዳኑ የዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሰሞኑን አሉት እንደተባለዉ ግን ጦራቸዉ የያዘዉ ሥፍራ የሱዳን በመሆኑ፣ መንግስታቸዉ የሚደራደርበት ምክንያት የለም።

ነጋሽ መሐመድ 

ማንተጋፍቶት ስለሺ