1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አቅምና መጪው ምርጫ

እሑድ፣ የካቲት 30 2006

አነሰም በዛም ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሃገር ውስጥ የተቃውሞ ድምጻቸውን ማሰማታቸውን የሚደግፉ ቢኖሩም መንግሥት ለመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ቆሜያለሁ ለማለት እንዲመቸው የማስመሰያ መጠቀሚያ ሆነዋል የሚሏቸውም አልጠፉም ።

https://p.dw.com/p/1BM2k

በኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ህጋዊ እውቅና ተሰጥቷቸው በይፋ መንቀሳቀስ ከጀመሩ ከ20 ዓመት በላይ እድሜ አስቆጥረዋል ። በነዚህ ዓመታት አዳዲስ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሲደራጁ ፤ አንዳንዶቹ ሲቀናጁና ሲዋሃዱ እንዲሁም ሲለያዩ ቆይተዋል ። ጥቂት የማይባሉም በሂደት ከስመዋል ። ባለፉት 23 ዓመታት የኢትዮጵያ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ሲቃኝ ከጥንካሬው ድክመቱ የጎላ መሆኑን የሚናገሩ የመኖራቸውን ያህል ከተጨባጩ ሁኔታ አንፃር የአቅማቸውን ያህል እየሰሩ ነው ብለው የሚከራከሩላቸውም አሉ ። ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ተባብሮ ከመሥራት ይልቅ የተናጠል ጉዞ መምረጣቸው ፣ በህብረት መሥራት ቢጀምሩም ብዙም ሳይራመዱ መለያየታቸው በየፓርቲዎቻቸው ውስጥም መከፋፈል መናቆራቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎችን የሚተቹ ወገኖች በድክመትነት ከሚያነሷቸው ውስጥ ይጠቀሳሉ ። ተቃዋሚዎች በበኩላቸው ለእንቅስቃሴያቸው መገደብ መንግሥት ይፈፅምብናል የሚሉትን ወከባ ደጋግመው በምክንያትነት ያቀርባሉ ። አነሰም በዛም በሃገር ውስጥ የተቃውሞ ድምጻቸውን ማሰማታቸውን የሚደግፉ ቢኖሩም መንግሥት ለመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ቆሜያለሁ ለማለት እንዲመቸው የማስመሰያ መጠቀሚያ ሆነዋል የሚሏቸውም አልጠፉም ። በኢትዮጵያ ምርጫ ሊካሄድ አንድ ዓመት የሚጠጋ ጊዜ በቀረበት በአሁኑ ወቅት ትልቁ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥምረት የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ዋና አባሉ የሆነውን አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲን አግዷል ። የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ና አቅም እንዴት ይመዘናል ? የዛሬው እንወያይ የመነጋገሪያ ርዕስ ነው ። በዚህ ርዕስ ላይ የሚወያዩ እንግዶች ጋብዘናል ። ዶክተር መረራ ጉዲና የኢትዮጵያ ፊደራላዊ ዲሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ሊቀመንበር ፣ ኢንጅነር ግዛቸው ሽፈራው የእንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ሊቀመንበር ፣ ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ አሥራት አብርሃ የቀድሞ የአረና አባልና ደራሲ ናቸው ።

ሂሩት መለሰ

ልደት አበበ