የኢትዮጵያ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አቅምና መጪው ምርጫ
እሑድ፣ የካቲት 30 2006በኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ህጋዊ እውቅና ተሰጥቷቸው በይፋ መንቀሳቀስ ከጀመሩ ከ20 ዓመት በላይ እድሜ አስቆጥረዋል ። በነዚህ ዓመታት አዳዲስ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሲደራጁ ፤ አንዳንዶቹ ሲቀናጁና ሲዋሃዱ እንዲሁም ሲለያዩ ቆይተዋል ። ጥቂት የማይባሉም በሂደት ከስመዋል ። ባለፉት 23 ዓመታት የኢትዮጵያ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ሲቃኝ ከጥንካሬው ድክመቱ የጎላ መሆኑን የሚናገሩ የመኖራቸውን ያህል ከተጨባጩ ሁኔታ አንፃር የአቅማቸውን ያህል እየሰሩ ነው ብለው የሚከራከሩላቸውም አሉ ። ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ተባብሮ ከመሥራት ይልቅ የተናጠል ጉዞ መምረጣቸው ፣ በህብረት መሥራት ቢጀምሩም ብዙም ሳይራመዱ መለያየታቸው በየፓርቲዎቻቸው ውስጥም መከፋፈል መናቆራቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎችን የሚተቹ ወገኖች በድክመትነት ከሚያነሷቸው ውስጥ ይጠቀሳሉ ። ተቃዋሚዎች በበኩላቸው ለእንቅስቃሴያቸው መገደብ መንግሥት ይፈፅምብናል የሚሉትን ወከባ ደጋግመው በምክንያትነት ያቀርባሉ ። አነሰም በዛም በሃገር ውስጥ የተቃውሞ ድምጻቸውን ማሰማታቸውን የሚደግፉ ቢኖሩም መንግሥት ለመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ቆሜያለሁ ለማለት እንዲመቸው የማስመሰያ መጠቀሚያ ሆነዋል የሚሏቸውም አልጠፉም ። በኢትዮጵያ ምርጫ ሊካሄድ አንድ ዓመት የሚጠጋ ጊዜ በቀረበት በአሁኑ ወቅት ትልቁ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥምረት የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ዋና አባሉ የሆነውን አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲን አግዷል ። የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ና አቅም እንዴት ይመዘናል ? የዛሬው እንወያይ የመነጋገሪያ ርዕስ ነው ። በዚህ ርዕስ ላይ የሚወያዩ እንግዶች ጋብዘናል ። ዶክተር መረራ ጉዲና የኢትዮጵያ ፊደራላዊ ዲሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ሊቀመንበር ፣ ኢንጅነር ግዛቸው ሽፈራው የእንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ሊቀመንበር ፣ ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ አሥራት አብርሃ የቀድሞ የአረና አባልና ደራሲ ናቸው ።
ሂሩት መለሰ
ልደት አበበ