የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚ
ረቡዕ፣ ጥቅምት 17 2008በ2003 ዓ.ም. በተወሰኑ ኢትዮጵያውያን ሣይንቲስቶች በጎ ፈቃድ ተፀንሶ በሒደት ሕጋዊ ፍቃድ ያገኘው የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚ እንቅስቃሴ ምን ይመስላል?
ለአንድ ሀገር እድገት እና ብልፅግና በተግባር የታገዘ የሣይንስ እና ሥነ-ቴክኒክ ዕውቀት ሽግግር ወሳኝነቱ የሚያጠራጥር አይደለም። ያም በመሆኑ ሣይንሳዊ ምርምሮችን እንዲያግዙ እና እንዲያፋጥኑ በሚል ሃገራት የሣይንስ አካዳሚዎችን ያቋቁማሉ፤ ያበረታታሉ፤ በነፃነትም እንዲሠሩ ድጋፍ ያደርጋሉ።
በ49 ኢትዮጵያውያን ምሁራን የግል ተነሳሽነት እንደተቋቋመ ይነገርለታል፤ የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚ። ተቋሙ «የምሁራን ተቀራርቦ በህብረት መሥራት አስፈላጊ ነው፤ ያን ማድረግም ይገባናል» በሚሉ ኢትዮጵያውያን ከተቋቋመ አምስት ዓመት ግድም አስቆጥሯል። እንደ ሳይንስ ተቋሙ ግምገማ ከሆነ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በጣም ዝቅተኛ የምርምር ኃይል ያላት ሀገር ናት። ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ፤ የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚ የሥራ አስፈፃሚ ዳይሬክተር ናቸው፤ ይህን ያብራራሉ።
ከዛሬ 40 ዓመታት በፊት ኢትዮጵያም የሣይንስ አካዳሚ ያስፈልጋታል በሚል የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚን የጠነሰሱት ያበጁት እነ ዶክተር አክሊሉ ለማ ናቸው። ዶክተር አክሊሉ ለማ ከ50 ዓመት በፊት የቢልሃርዚያን በሽታ በእንዶድ ቅጠል መከላከል እንደሚቻል ለመጀመሪያ ጊዜ የደረሱበት ተመራማሪ ሣይንቲስት ናቸው።
የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚ የኢትዮጵያ ሣይንስና ቴክኖሎጂን ይደግፋል ተብሎ ስለታመነበት በአዋጅ እንደተቋቋመ ይነገርለታል። የሳይንስ አካዳሚው በይፋ ከተቋቋመ በኋላ በጤናው ዘርፍ፣ በሥነ-ቴክኒክ፣ በተፈጥሮ እና ማኅበራዊ ሣይንስ ዘርፍ እንዲሁም በሌሎች ጉዳዮች ላይ ጥናት እና ምርምር ማድረጉን ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ ያብራራሉ።
የኢትዮጵያ የሣይንስ አካዳሚ አራተኛ አጠቃላይ ጉባኤውን ቅዳሜ፤ ጥቅምት 13 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.ያኪያሄደ ሲሆን፤ ከአንድ ወር በኋላ ደግሞ «የከፍተኛ ትምህርት እና ምርምር ደረጃ» በሚል ርእስ ከፍተኛ ጉባኤ ያኪያሂዳል። በዚህ የሣይንስ አካዳሚው ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ በዋናነት ትኩረት ተሰጥቶት ውይይት የሚኪያሄድበት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የጥራት ደረጃ እንደሆነ ተገልጧል። ተቋሙ የመነሻ ሐሳብ እንዲሆን በሚል በድረ-ገጹ ያወጣው ጽሑፍም ይህንኑ ይገልጣል።
«በአሁኑ ወቅት በበርካታ ዩኒቨርሲቲዎች በጥልቀት የሚያጠይቅ አዕምሮን ማነጹ እንዲሁም ለዕውቀት እጅግ ጉጉነትን ማነሳሳቱ ቀዳሚ ሥፍራ የተሰጠው አይመስልም» የሚል ሐረግ ተቋሙ አስፍሯል። ከዚያም ባሻገር፦ «የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ቁጥር መጨመር የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጥራትን ማረጋገጫ አይደለም» የሚል ሌላ ሐረግም በድረ-ገጹ አክሏል።
በኢትዮጵያ የከፍተኛ ትምኅርት ተቋማት ቁጥር ከሃያ እና ዐሥር ዓመታት በፊት ከነበረው በከፍተኛ ደረጃ ጨምሯል። ይህ የከፍተኛ ተቋማት ቁጥር መጨመር ለሀገር እድገት ወሳኝ የሆነው ዕውቀት፤ በተለይም በሣይንስ እና ሥነ-ቴክኒክ ዘርፍ እንዲዳብር ትኩረት ሊደረግበት ይገባል።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ