የኢትዮጵያውያን ስደተኞች ስቃይ በሊቢያ
ሐሙስ፣ ነሐሴ 8 2006ቤንጋዚ ሊቢያ የሚገኝ አንድ ኢትዮጵያዊ ስድተኛ አሁን በሊቢያ ስደተኞችከቀድሞው ይልቅ ለከፋ አደጋ መጋለጣቸውን ለዶቼቬለ ተናግሯል ። የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽነር «ዩኤንኤችሲአር» በሊቢያ የፀጥታ ችግር በመባባሱ የውጭ ዜጎች አስፈላጊውን የጥንቃቄ እርምጃ እንዲወስዱ እያሳሰበ ነው ። የሊቢያው ውጊያ ዜጎችን ብቻ ሳይሆን በዚያ በሥራ ፣በጥገኝነትም ሆነ በስደት የሚኖሩ የውጭ ዜጎችን ከፍተኛ ችግር ውስጥ ከቷል ። ከአንድ ወር በፊት ውጊያው እንደገና ባገረሸባቸው የሊቢያ ከተሞች የውጭ ዜጎች እንደሚገደሉ እንደሚታሰሩና እንደሚታገቱ በዚያ የሚገኙ ስደተኞች ይናገራሉ ።ዶቼቬለ ያነጋገረው በሊቢያዋ 2 ተኛ ትልቅ ከተማ ቤንጋዚ የሚገኝ አንድ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ እንዳለው እሱና ሌሎች ኢትዮጵያውን አደገኛ ሁኔታ ውስጥ ነው ያሉት ።
ከሱዳን በሰሃራ በረሃ በኩል አድርጎ ከ10 ወር በፊት ሊቢያ መግባቱን የሚናገረው ኢትዮጵያዊው ስደተኛ «ዩኤንኤችሲአር» እውቅና እንዲሰጠው ለማመልከት ቢሞክርም በውጊያው ምክንያት የቤንጋዚ ቢሮአቸው ስለተዘጋ ህጋዊ ወረቀት ማግኘት አልቻለም ። ርሱም ሆነ ሌሎች ስደተኞች ወደ ሌላ ከተማ ለመሄድ ቢፈልጉም የፀጥታው ችግር ሊያንቀሳቅሳቸው አልቻለም ። ደፍረው ለመሄድ ቢሞክሩ እንኳን አደጋው የከፋ ሊሆን ይችላል።እናም የከፋ ችግር ውስጥ የሚገኘው የሊቢያው ስደተኛ ለዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ተምፅኖውን አቅርቧል ።ሊቢያ ስለሚገኙ ስደተኞች ሁኔታ ዶቼቬለ ያነጋገራቸው በሊቢያ የ«ዩኤንኤችሲአር» መሥሪያ ቤት ተጠባባቂ ሃላፊ ሰአዶ ኮል በቤንጋዚ የፀጥታው ችግር በጣም አሳሳቢ እንደሆነ ነው የሚናሩት። ካሉበት ከቱኒዝያ በስልክ ያነጋገርናቸው ኮል የሊቢያ መንግስት አሁን በርካታ የውጭ ዜጎችን ስደተኞችንና ተገን ጠያቂዎችን በማቆያ ጣቢያዎች ውስጥ መያዙን መሥራያ ቤታቸውም የታሰሩ ስደተኞች እንዲለቀቁ ለመንግሥትም ሆነ ጉዳዩ ለሚመለከታቸው አካላት ጥሪ እያቀረበ መሆኑን አስታውቀዋል ።
« አሁን በሊቢያ ያለው የፀጥታ ሁኔታ ሊቢያውያን በሊቢያ የሚገኙ የውጭ ዜጎች ስደተኞችና ተገን ጠያቂዎች በነፃነት እንዲንቀሳቀሱ አይፈቅድም ። በተለይ በቤንጋዚ ና በሊቢያ በሚካሄደው ውጊያ ምክንያት ሊቢያውያንም ጭምር እንደልባቸው ወዲያ ወዲህ ማለት የማይችሉበት ሁኔታ ነው ያለው ። በበኩላችን የነዚህ ሰዎች ነፃ እንቅስቃሴ እንዲጠበቅ በተቻለን መጠን ማሳሰባችንን እንቀጥላለን ። »የ«ዩኤንኤችሲአር»የሊቢያ ተጠባባቂ ሃላፊ ሰአዶ ኮል ከዛሬ ነገ እንገደላለን ወይም እንታሰራለን እንታገታለን የሚል ስጋት ውስጥ የሚገኙት ስደተኞች ሊቢያ ውስጥ እንዴት መቆየት እንደሚችሉ መወሰን ያለባቸው ራሳቸው መሆናቸውን አስረድተው ሆኖም ባሉበት በጥንቃቄ እንዲንቀሳቀሱ መክረዋል ።
«የት መቆየት እንደሚችሉ በየተኛው የተሻለ ቦታ መኖር እንደሚችሉ መወሰን የሚችሉት እነርሱ ናቸው ። «ዩኤንኤችሲአር» አሁን በሊቢያ ባለው የፀጥታ ችግር እዚያ ለሚገኙ ሰዎች በከተሞች ውስጥም ቢሆን እንዲንቀሳቀሱ ምክር መስጠት አያስችለውም ። እኛ ልናደርግ የምንችለው የተሻለ ነገር የተያዙ ሰዎች እንዲለቀቁ ድምጻችንን ማሰማት ብቻ ነው ።ለታሰሩት ከምግብ ውጭ ሌሎች እርዳታዎች ለመስጠት እንሞክራለን ። የተባባሰውን ውጊያ ከግምት ውስጥ በማስገባት ሁኔታው ተለዋዋጭና አደገኛ በመሆኑ በጥንቃቄ እንዲንቀሳቀሱ እንሳስባለን »
ኂሩት መለሰ
ተክሌ የኋላ